November 25, 2019 |

Posted by: ዘ-ሐበሻ

ወጣት ተከስተ አያሌው፣ የአዲስ አበባ ወጣቶች ማህበር ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት

• የአዲስ አበባ ወጣት የሚያስቀድመውም እንዴት አድርጌ ራሴን፣ ቤተሰቤንና አገሬን መጥቀም አለብኝ የሚለውን ጉዳይ ነው።

• አዲስ አበባ ከሌሎች ክልሎች በተሻለ መንገድ ሰላማዊ የሆነ እንቅስቃሴ የሚታይበት ከተማ ናት። የከተማዋ ሰላም መሆን ግን ወጣቱ ሁሉ ነገር ተመልሶለታል ማለት አይደለም።

• የከተማዋ ወጣት ነገሮችን የሚያይበት፤ ችግሮችም እንዲፈቱለት የሚሰራበት አግባብ የተሻለ መንገድ ስለሆነ ነው።

•ስንዴ የሚለምን ድንጋይ ሲወረውር ስለማያምርበት የመጀመሪያ ጉዳይ መሰረታዊ ፍላጎቶቻችንን ማሟላት ላይ መሆን መቻል አለበት።

• ማህበሩ 120 ሺህ ያክል አባላት ያሉት እንደመሆኑም ወጣቶች በምን መንገድ ጥያቄዎቻቸውን ማቅረብ አለባቸው፤ ጥያቄዎቻቸውስ በምን መንገድ ሊመለሱላቸው ይገባል የሚለው ላይ ትኩረት በመስጠት የከተማዋን ሰላም ከማስጠበቅም ሆነ ወጣቱ የለውጡ አጋዥ እንዲሆን ከማድረግ አንጻር እየሰራ ነው።

• እኛም ችግሮች እንዲፈቱ በከተማዋ ውስጥ በሚፈጠሩ በእያንዳንዳቸው ጉዳዮች ላይ ከአባላቶቻችንም ሆነ ከሚመለከተው የመንግስት አካል ጋር ውይይት እናደርጋለን።

• አዲስ አበባ ወጣቶች ማህበር መደመርን አንድ ሆኖ በመስራት መበልጸግ በሚል ነው የምንገልጸው።

• የመደመር እሳቤ ለሆነ አካል ተብሎ የተቀመጠ ሳይሆን ለኢትዮጵያ የተቀመጠ፤ እንዴት አድርገን ይህችን አገር እናሳድጋት፤ እንዴት አድርገን ወደተሻለ ነገር እናሸጋግራት፤ የሚለውን ማሰላሰል የሚጠይቅ ነው።

• ለውጡን ሁሉም ሰው ይቀበለዋል ማለት ባይቻልም፤ ልዩነታችንን አጥብበን ወደ አንድ የምንመጣበትን ነገር ካመቻቸን ውጤታማ የማንሆንበት ምክንያት አይኖርም።

• አንድ ለውጥ ሲመጣ በአንዴ ውጤታማ ይሆናል አይቻልም። ስለዚህ በመደመር እሳቤ ውስጥ ሆኖ ለውጡን የሚቀበል አካል አለ፤ ለውጡን የማይቀበሉ አካላትም ይኖራሉ።

• ለውጥ መደገፍ ማለት ፖለቲከኛ መሆን ማለት ሳይሆን ከተማ አስተዳደሩ የጀመራቸውን ስራዎች ማገዝ ማለት ስለሆነ እያንዳንዱ ሰውም ለውጡን የመደገፍ ሃላፊነት አለበት ብዬ ነው የማስበው።

• እያንዳንዱ አካል በሰላሙም፣ በጸጥታው፣ በማህበራዊው ጉዳይ ይመለከተኛል ብሎ ከሰራ የለውጥ አጋዥነቱ ማሳያ ነው። ከዚህ አኳያ የክረምት የወጣቶች የበጎ ፈቃድ ስራ እንደማሳያ የሚወሰድ ነው።

• ምክንያቱም አንድ ላይ ስንሆን ያምርብናል፤ አንድ ስንሆን እናድጋለን፤ አንድ ስንሆን እንበለጽጋለን፤ በሚል እሳቤ ነው የምንወስደው።

• መንግስት ለወጣቶች የስራ እድል ፈጠራ ልዩ ትኩረት መስጠት አለበት የሚል እምነት አለኝ፤

• የሚፈጠረው የስራ እድልም ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ለሚመለከታቸውና ለትክክለኛው ወጣት ከማድረስም አኳያ ውስንነት አለበት።

• በልዩነታችን ውስጥ አንድነታችንን ማሰቡ የተሻለ ስለሆነም ከመገናኛ ብዙሃን ጀምሮ ትንንሽ ነገሮች እየጫሩ ለህዝብ ከማድረስ ይልቅ ይህች አገር የነበራትን አንድነትና ታሪክ፤ እንዲሁም እንዴት ተቻችሎ አብሮ መኖር እንደሚቻል ማሳየቱ ላይ ትኩረት ሊያደርጉ ይገባል።

• እንደ ቀደሙት አባቶቻችን ሁሉ የውስጥ ሰላምን ማስጠበቅን፤ እኔ ከማለት ይልቅ እኛነትን ማስቀደምን ይጠይቃል።

• ከዚህ ባለፈም አዲስ አበባ ሽግግር የሚደረግባት፤ ከየክልሉ መጥተው የሚሰሩባትን እድል የፈጠረች፤ እኛም ወደሌሎች ክልሎች ሄደን የምንሰራበትን አቅም የሰጠች፤ የፌዴራሉ መንግስት መቀመጫም ናት።

• እኛም በዋነኝነት እየሰራን ያለነው በአዲስ አበባ ያለውን ተቻችሎ በአንድ የመኖር እሴት እንዴት ወደሌሎች ቦታዎች እንውሰደው የሚለው ላይ ሲሆን፤

• ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ከሁሉም የአገሪቱ ክፍሎች የተውጣጡ ወጣቶች የልምድ ልውውጥ እንዲካሄድ ተደርጓል።

• ወጣቱ ሰላምን አስጠብቆ ወደ ብልጽግና ከመራመድ ይልቅ ብሔርና እምነት እየጠቀሰ ወደኋላ ማለት የለበትም፣

• አዲስ አበባ እንዳላት ታሪክና እድሜ አይደለም እየሄደች ያለችው። ለዚህ ደግሞ ችግሩ በየወቅቱ የነበሩ ሥርዓቶች፣ አመራሮችና ህብረተሰቡ እንዲሁም እኛም ወጣቶች ሃላፊነት አለብን።

• ከእኔ በፊት አገሬ የሚል እሳቤ ከመጣ ያሰብናትን ኢትዮጵያ መፍጠር እንችላለን።
• በተለይ ወጣቶች ደግሞ ከስሜታዊነት በመውጣትና ሚዛናዊ በመሆን ለአገራችን በየተማርንበት የሙያ መስክ አስተዋጽዖ ማድረግ አለብን።

• ከተማዋ ሰላማዊና የለማች እንዲሁም የቱሪዝም መዳረሻ እንድትሆን ከማድረግ አኳያ በተለይ ወጣቱ አዲስ አበባን መጠበቅ፤ በአዲስ አበባ ላይ የራሱን አሻራ ማስቀመጥ አለበት።