ሐራ ዘተዋሕዶ

March 31, 2019 t

kaletsidek mulugeta sacked

***

***

ቋሚ ሲኖዶስ፣ ከትላንት በስቲያ ዓርብ፣ መጋቢት 20 ቀን 2011 ዓ.ም. በአካሔደው ሳምንታዊ መደበኛ ስብሰባው፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የውጭ ጉዳይ መምሪያ ዋና ሓላፊ ‘መልአከ ሰላም ቆሞስ አባ’ ቃለ ጽድቅ ሙሉጌታ፣ ከቦታው እንዲነሣ ወስኗል፤ በጠቅላይ ጽ/ቤቱ ቦታ ተፈልጎለትና ደረጃው ተጠብቆ እንዲመደብም ትእዛዝ ሰጥቷል፡፡

ቋሚ ሲኖዶሱ ውሳኔውን የሰጠው፣ የውጭ ጉዳይ መምሪያው የበላይ ሓላፊ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ፣ ዋና ሓላፊው ‘አባ’ ቃለ ጽድቅ ተነሥቶ በሌላ ሓላፊ እንዲተካ፣ ከኹለት ወራት በፊት ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በጽሑፍ በማመልከታቸውና ይህም ቅዱስነታቸው በአቀረቡት አቤቱታ በመጠናከሩ ነው፡፡

qaletsidek1

ሲኖዶሳዊ አንድነቱ መመለሱን ተከትሎ የውጭ ግንኙነት መምሪያው፣ በማዕከል ለሚመራው የቤተ ክርስቲያን ዓለም አቀፋዊ ተልእኮ በርካታ ተግባራትን ማከናወን እንደሚጠበቅበት፣ የበላይ ሓላፊው ጳጳስ፣  ባለፈው ጥር 1 ቀን ለቅዱስነታቸው በጻፉት ማመልከቻ ጠቅሰዋል፤ ሥራውን በአግባቡ ለማከናወን ይረዳ ዘንድም፣ ‘አባ’ ቃለ ጽድቅ ሙሉጌታ ከቦታው ተነሥቶ በምትኩ መ/ር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል እንዲመደቡላቸው ጠይቀዋል፡፡  

የውጭ ጉዳይ መምሪያው ተጠሪነት፣ አንድ ጊዜ ወደ ፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ሌላ ጊዜ ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት እየኾነ ቢዋዥቅም፣ በዚህ ወቅት ጉዳዩ ከቅዱስነታቸው ወደ ዋና ሥራ አስኪያጁ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ተመርቶ ስለነበር፣ የጠቅላይ ጽ/ቤቱ [የሠራተኛ]አስተዳደር መግለጫ እንዲያቀርብበት ተሰጥቶታል፡፡ የ‘አባ’ ቃለ ጽድቅ ሙሉጌታን ማኅደር የመረመረው የአስተዳደር መምሪያው በበኩሉ፣ ግለሰቡ በውጭ ጉዳይ መምሪያ ሓላፊነት የተመደበው በቋሚ ሲኖዶሱ እንደነበረ አስታውሶ፣ የቀረበው የይነሣልኝ ጥያቄም በዚያው በቋሚ ሲኖዶሱ በኩል ቢታይ የተሻለ እንደሚኾን ለብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ መግለጫ አቅርቧል፤ ብፁዕነታቸውም፣ መግለጫውን በመሸኛ ለቅዱስነታቸው አቅርበው አመራር እንዲሰጡበት በመጠየቃቸው፣ ቋሚ ሲኖዶሱ፣ ባለፈው ረቡዕ እና ዓርብ ባካሔዳቸው ስብሰባዎቹ ተነጋግሮበታል፡፡

qaletsidek2

ይነሣልኝ ከሚለው የውጭ ጉዳይ መምሪያው ጥያቄ በቀር ስለ ግለሰቡ በዝርዝር የቀረበ ምክንያት አለመኖሩን የገመገመው ቋሚ ሲኖዶሱ፣ የበላይ ሓላፊውን ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አረጋዊን ጠርቶ ማብራሪያ ጠይቋል፡፡ የመምሪያው የበላይ ሓላፊ እንደመኾናቸው በሥራቸው ያሉትን ማስተባበር፣ መምራትና መቆጣጠር እንደሚጠበቅባቸው ለቋሚ ሲኖዶሱ የገለጹት ብፁዕነታቸው፣ ‘አባ’ ቃለ ጽድቅ ሙሉጌታ እንደማይታዘዛቸው አስረድተዋል፤ ርእሰ መንበሩም፣ ሳያስፈቅዳቸው ወደ ውጭ መጓዝ እንደሚያዘወትር በመጥቀስ የብፁዕነታቸውን ማብራሪያ አጠናክረዋል፡፡ ‘አባ’ ቃለ ጽድቅ በበኩሉ፣ ኹለቱንም ተቃውሞ በመከራከሩ ለውሳኔ አስቸጋሪ እንዳደረገው ተገልጿል፡፡ በመጨረሻም ጉዳዩ፣ “እርስ በርስ አለመግባባት” የሚል ምክንያት ተሰጥቶት ከዋና ሓላፊነቱ እንዲነሣ ተወስኗል፤ ወደ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ ተዛውሮና ደረጃው ተጠብቆ እንዲመደብም ትእዛዝ ተሰጥቷል፡፡

qaletsidek3

ከሦስት ዓመት በፊት፣ በፓትርያርኩ በኩል ከአሜሪካ የተጠራው ‘አባ’ ቃለ ጽድቅ ሙሉጌታ፣ በቋሚ ሲኖዶስ ውሳኔ የውጭ ጉዳይ መምሪያ ዋና ሓላፊ ኾኖ የተመደበው፣ ታኅሣሥ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ነበር፡፡ ከዘመኑ ትምህርት በአይ.ሲ.ቲ የበርክሌይ ዩኒቨርስቲ ምሩቅ፣ ከአብነቱም የቅኔና ቅዳሴ ዐዋቂ እንደ ኾነ ተነግሯል፤ የውጭ ቋንቋ ተናጋሪ ነው፤ ይረዳዎታል በሚል አግባቢነት ለፓትርያርኩ ተልኮላቸው በቀጥታ በውጭ ጉዳይ መምሪያ ዋና ሓላፊነት እንዲመደብ አድርገዋል፡፡ ኾኖም፣ ሓላፊነቱን ተገን በማድረግ በቤተ ክርስቲያናችን የውጭ ግንኙነት ሥራ ላይ ሲፈጽም ከቆየው ደባ፣ ከዚያም በፊት ባለበትና በኋላም በቀጠለበት የመናፍቅነት ዝንባሌና የሥነ ምግባር ችግር አንጻር፣ በቀኖና እና በሕግ ሊጠየቅና ሊታረም እንጂ ዳግም የምደባ ዕድል ሊሰጠው የሚገባ ሰው አልነበረም፡፡

“አሜሪካም አውሮጳም ሔዶ ያተራመሳቸው ነገሮች አሉ፤ ገንዘብም ተቀብሏል፤” ያሉት አንድ የቋሚ ሲኖዶሱ አባል፦ በጅቡቲ ምሥራቀ ፀሐይ ቅዱስ ገብርኤል፣ በጆሐንስበርግ ጽርሐ ጽዮን መድኀኔዓለም ካቴድራል፣ በአቴንስ ኪዳነ ምሕረት እና በኦስትርያ ተክለ ሃይማኖት አቤቱታዎች ማጣራትና የውሳኔዎች አተገባበር፣ አስተዳደሩን ከምእመናን፣ ምእመናንን ከምእመናን በሚለያይ አድሏዊነት ጠብንና ዓምባጓሮን በማበረታታት የፈጸማቸውን በደሎች በአስረጅነት ጠቅሰዋል፡፡


ይነሣልን ተብሎ ሲጠየቅ፣ ቀደም ተብሎ የተረጋገጠውን የሃይማኖትም የምግባርም ሕጸጾቹን፣ በተለያዩ ጊዜያት ከየክፍላተ ዓለሙ በምእመናን ከቀረቡበት አቤቱታዎች ጋራ በዝርዝርና በጥልቀት ፈትሾ የተጠያቂነት ሥርዓትን የሚያረጋግጥና ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅም ኹነኛ ውሳኔ ማሳለፍ እየተቻለ አልተደረገም፡፡ ይህም፣ የበላይ ሓላፊው ጳጳስም ይኹን የፓትርያርኩ ጥያቄ መነሻ፣ ግላዊ አለመግባባት መስሎ ብቻ እንዲታይ አድርጎታል፡፡ ይብሱኑ፣ ‘አባ’ ቃለ ጽድቅ፣ ተዛውሮና ደረጃው ተጠብቆ ይመደብ የሚል ውሳኔ እንዲተላለፍ ምክንያት እንደኾነ ግንዛቤ ተወስዷል፡፡  

ለየሥራ ዘርፉ ተገቢውን ሰው ከመፈለግ ይልቅ ለሰው ሥራ በሚፈለግበት፤ የበደለኛ ሰው ትልቁ ቅጣት የሕግ ተጠያቂነት ሳይኾን ዝውውር ተደርጎ በሚታይበት ቤተ ክህነታችን፥ ሻጥረኛው፣ ጥቅመኛው፣ መናፍቁና ምግባረ ቢሱ ‘አባ’ ቃለ ጽድቅ ሙሉጌታ፣ ተዛውሮና ደረጃው ተጠብቆ እንዲመደብ መወሰኑ፣ አሳዛኝ ባይኾን ኖሮ አስገራሚ አይደለም፡፡ የውሳኔው አፈጻጸም፣ ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ የሚቸግር እንደ ኾነ ከወዲሁ ታይቷል፤ ለቤተ ክርስቲያናችን በአጠቃላይም ስጋት እንደኾነ ተጠቁሟል፡፡

የመጀመሪያው፣ የውጭ ጉዳይ መምሪያው፣ በ‘አባ’ ቃለ ጽድቅ ሙሉጌታ ቦታ እንዲተካለት የጠየቀው፣ ኢኦተቤ – ቴቪን በበላይነት የሚመራው የብዙኃን መገናኛ አገልግሎት ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅን መ/ር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤልን መኾኑ ነው፡፡ በትምህርት ይኹን በቋንቋ ችሎታ ከፍተኛ ዝግጅት ያላቸው መ/ር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል፣ ለውጭ ግንኙነት ሥራው፣ የተሻለና አግባብነት ያለው ልምድ እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ ኾኖም፣ ወደ ውጭ ጉዳይ መምሪያው ሲዛወሩ፣ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ፣ በዋና ሓላፊነት ደረጃ የሚኖረው ብቸኛ ክፍት ቦታ፣ የብዙኀን መገናኛ አገልግሎት ድርጅቱ ሥራ አስኪያጅነት ይኾናል፤ የመምሪያ ዋና ሓላፊነት ደረጃው ተጠብቆ ይዛወር ለተባለው ‘አባ’ ቃለ ጽድቅ ሙሉጌታ የሚኾን ክፍት መምሪያ ይኹን ድርጅት የለም፤ ተብሏል፡፡ በብዙኀን መገናኛ አገልግሎት ድርጅቱ ሥራ አስኪያጅነት መመደብ ማለት ደግሞ፣ በስርቆቷ አፏን ሲመቷት አሁን ከብሆው ለመግባት ተመቸኝ እንዳለችው ውሻ መኾኑ ነው፤ ሥጋን በጅብ ትክሻ እንደ መጫን ነው፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተሻለ አደረጃጀትና በከፍተኛ ሞያዊ መነሣሣት ላይ ለሚገኙት የቴሌቪዥን ጣቢያው ባለሞያዎችም ታላቅ ስድብ ነው፤ ጠቅላላ ተቋማዊ አደጋው ግልጽ ነው፡፡

በመኾኑም፣ የውጭ ጉዳይ መምሪያው የበላይ ሓላፊ ጳጳስ በጠየቁት መሠረት፣ መ/ር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል ከኢኦተቤ-ቴቪ ዋና ሥራ አስኪያጅነት የሚዛወሩ ከኾነ፣ በኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ብስለቱና በተግባቦት ክህሎቱ የላቀ፣ ከግለሰቦች ይልቅ የቤተ ክርስቲያንን መብትና ጥቅም ቅድሚያ ሰጥቶ ከማስከበር አኳያ የሚዲያውን አንጻራዊ ነጻነት አስከብሮ በመምራት ብቃቱ የሚታመንበት፣ አሁን የሚታየውን የጣቢያውን ባለሞያዎች ተነሣሽነት የሚመጥንና ሠርቶ የሚያሠራ ዋና ሓላፊ በጥንቃቄ ተለይቶ ሊተካለት ይገባል፡፡

የውጭ ጉዳይ መምሪያውም ቢኾን፣ የውጭ ግንኙነት ሥራውን የሚመራበት ግልጽ ፖሊሲ ተቀርፆለት፣ ስትራተጅና ዕቅድ ወጥቶለት የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ በዓለም አቀፍ ደረጃ በሚያሳካ፣ ክብሯንና ጥቅሟን በሚስጠብቅ መልኩ ተግባሩን መፈጸም ይጠበቅበታል፤ አድማሳዊ ግንዛቤ ባላቸው ብቁ ባለሞያዎችና የሥራ መሣሪያዎች መደራጀት፣ በበጀትም መጠናከር ይኖርበታል፡፡

መምሪያው፣ በክፍላተ ዓለም ዴስኮች እንዲደራጅና በተለያዩ ቋንቋዎች መደበኛ ኅትመቶች እንዲኖሩት፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ከጥቅምት 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ልዩ ልዩ ውሳኔዎችን ቢያስተላልፍም፣ ለተግባራዊነቱ የተደረገ የጎላ እንቅስቃሴ አልታየም፡፡ ከሪፖርቶች እንደሚታየው፣ የውጭ ግንኙነት ተብለው የሚቀርቡት ዓመታዊ ዘገባዎች፣ በፓትርያርኩ ኦፌሴልያዊ ጉብኝቶችና ለአገልግሎት በሚመደቡ ልኡካን አላላክ ላይ የሚያተኩሩና በዚሁ ጉዳይ ዙሪያ የታጠሩ ናቸው፡፡ ተልእኮው ግን ከዚህም የገዘፈና የሰፋ በመኾኑ፣ ተጠሪነቱ በግልጽ ተወስኖለትና የሥራ ዝርዝሩም ተቀምጦለት፣ ከፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ጥገኝነት መላቀቅ ያስፈልገዋል፡፡

በዓለም አቀፍ ግንኙነት እጅግ ጥንታዊ ታሪክ ያላት ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያናችን፣ ለተጽዕኖ ፈጣሪነቷም ዋናው ምክንያት፣ የውጭ ግንኙነት ሥራዎችዋ ውጤት እንደኾኑ ሊዘነጋ አይገባም፡፡ ከመቼውም ጊዜ በላይ፣ በውጭ አገሮች፣ አብያተ ክርስቲያን እየጨመሩና እየተጠናከሩ የመጡበት ጊዜ ነው፡፡ የመምሪያው የበላይ ሓላፊም በማመልከቻቸው እንዳሰፈሩት፣ ከሲኖዶሳዊው አንድነት መመለስ ጋራ ተያይዞ፣ ዓለም አቀፋዊውን ተልእኮ በማቀናጀት በአንድ ማዕከል የመምራት ሓላፊነት ስላለበት፣ “ብዙ ሥራዎች ከመምሪያው ይጠበቃሉና”፣ የሰው ኀይል ምደባው በእጅጉ ይታሰብበት፡፡

አባ’ ቃለ ጽድቅ ሙሉጌታ ግን፡-

ኾኖም፣ በዳግም ምደባው ሌሎች መምሪያዎችንና ድርጅቶችን ለበለጠ አደጋ ከማጋለጥ ይልቅ፣ በዝርዝር በተገለጹት ሕጸጾቹና ጥፋቶቹ እርምት መውሰዱ ቅድሚያ ቢሰጠው፣ ርምጃውን የተሟላና አብነታዊ ያደርገዋል፡፡

ኾኖም፣ በዳግም ምደባው ሌሎች መምሪያዎችንና ድርጅቶችን ለበለጠ አደጋ ከማጋለጥ ይልቅ፣ በዝርዝር በተገለጹት ሕጸጾቹና ጥፋቶቹ እርምት መውሰዱ ቅድሚያ ቢሰጠው፣ ርምጃውን የተሟላና አብነታዊ ያደርገዋል፡፡