April 7, 2019t

- በመጪው እሑድ፣ በመንበረ ጸባዖት ቅ/ሥላሴ ካቴድራል አዳራሽ፣ የምክክርና የድጋፍ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ይካሔዳል፤
- አዳጊዎች፣ በዘመናዊው የካቺሲ መድኀኔዓለም ት/ቤት እና በሚገነባው የአብነት ት/ቤት በተመጋጋቢነት የሚማሩበት ዕቅድ ነው፤
- ከወረዳው 41 አብያተ ክርስቲያን 15ቱ፣ ካህን የሚያገኙት በመንፈቅ ወይም በዓመት አንዴ ብቻ ነው፤ እርሱም በልመና ነው
- በተሰበከው የጥላቻ ፖሊቲካ፣ በክልሉ የቤተ ክርስቲያን ዕጣ ፈንታ አሳሳቢ ኾኗል፤ ባለመሥራትም የተፈጠረ ክፍተት ነው፤”
- “ከኦርቶዶክስ የጸዳች ኦሮሚያ” በሚል ስልታዊ ግንባር የፈጠሩ አክራሪዎች፣ በመብቶችና ይዞታዎች ላይ ጫና አጠናክረዋል፤
- ድጋፎችን ሲያደርግ የቆየውና የግንደ በረት አብያተ ክርስቲያን አገልግሎት ማኅበር፣ ለምእመናንና በጎ አድራጊዎች ጥሪ አቀረበ፤
*** ቤተ ክርስቲያን፣ በኦሮሚያ ክልል ያለችበትን አጠቃላይ ኹኔታ በተመለከተ ለማዕከል የሚቀርቡ ሪፖርቶች፣ ምርቅና ፍትፍት ናቸው፡፡ በክልሉ ከሚገኙ 15 አህጉረ ስብከት የሚበዙቱ፣ በመንፈሳዊና የአስተዳደር ዘርፎች፣ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መጠናከሩንና መስፋፋቱን የሚያሳዩ በርካታ ተግባራት እንዳከናወኑ የገለጹባቸው አስደሳችና ተስፋ ሰጪ ዘገባዎች፣ ፈጣን የጋራ ምላሽን የሚጠይቁ አሳሳቢ ስጋቶችና ተግዳሮቶች መኖራቸውንም የሚጠቁሙ ናቸው፡፡ በስኬት ረገድ፣ በጥቅምቱ የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ 37ኛ ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ የተሰሙት የአህጉረ ስብከቱ ሪፖርቶችና ተጓዳኝ መረጃዎች ካሰፈሯቸው ክንውኖች መካከል፡-
- ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የሰላም ዕጦት በታየባቸው ወረዳዎችና ሰበካዎች ሳይቀር ሐዋርያዊ ጉዞ በማድረግ እያስተማሩና እየቀደሱ አባታዊ ትምህርትና ቡራኬ መስጠታቸውን፤ የንዋያተ ቅድሳትና የአልባሳት ድጋፍ ማድረጋቸውን፤ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን መሾማቸውን፤
- ለስብከተ ወንጌል በበጀትና በሰው ኀይል ልዩ ትኩረት በመስጠት፣ በአፋን ኦሮሞ የሚያስተምሩ ተተኪ ሰባክያነ ወንጌል የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና መሠልጠናቸውን፤ ከመደበኛው የሠርክ ጉባኤ ባሻገር ታላላቅ ጉባኤያት መካሔዳቸውን፤ የፀረ ፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኮሚቴዎች ተቋቁመው የዕቅበተ እምነት ጉባኤያት በመጠናከራቸው፣ የተሳሳቱትና የራቁት ምክር ተሰጥቷቸው ሲመለሱ፣ ያልተመለሱት ከቤተ ክርስቲያን መለየታቸውን፤
- ለነባር አብያተ ክርስቲያን የእድሳት ፈቃድ፣ ለአዲስ አብያተ ክርስቲያን የትክል ፈቃድ መሰጠቱንና መታነፃቸውን፣ የይዞታ ማረጋገጫ ማግኘታቸውን፤ በፍ/ቤት ክርክርና በስምምነት የተወሰዱ የዕጣን አዙር ይዞታዎች ማስመለስ መቻሉን፤ ሰበካ ጉባኤያት መደራጀታቸውንና በራስ አገዝ ልማት ቋሚ የገቢ ማስገኛ ተቋማትን መገንባታቸውን፤
- በአቅም ግንባታና ተተኪ አገልጋዮችን ከማፍራት አንጻር የካህናት ማሠልጠኛዎች ተቋቁመው ቀሳውስትና ዲያቆናት መሠልጠናቸውን፣ ለቢሮ ሓላፊዎችና ሠራተኞችም በመልካም አስተዳደር ወሳኝ ሥልጠና መሰጠቱን፤
- የሰንበት ት/ቤቶች ተጠናክረው በማገልገል ላይ መኾናቸውን፤ የአብነት ት/ቤቶች ባልተቋቋሙባቸው አጥቢያዎች እየተቋቋሙ መኾኑንና በተቋቋሙባቸውም የባንክ አካውንት ተከፍቶ የአብነት መምህራንና ደቀ መዛሙርት ወርኀዊ የበጀት ድጎማ እየተደረገላቸው በተለይም በንባብ(ፊደልና መዝሙራት)፣ በቅዳሴ፣ በቅኔ የመማር ማስተማሩ ሥራ በመከናወን ላይ እንደሚገኝ፣ ይህም ፍልሰታቸውን በመቀነስ ለውጥ ማሳየቱን፤ በዘመናዊውም፣ ሙዓለ ሕፃናትና የአንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች ተቋቁመው እያስተማሩ መኾኑን፤
- ለንብረት አያያዝና ለቅርስ ጥበቃ ትኩረት በመስጠት ምዝገባና ቆጠራ እየተደረገ መኾኑን፤ ዓመታዊው የሰበካ ጉባኤ የአባልነት አስተዋፅኦ መጨመሩን፣ የሒሳቡ አመዘጋገብ ከነጠላ ወደ ኹለትዮሽ ሥርዓት መሻሻሉን፣ በአጥቢያ ደረጃ የሚሰበሰበው ጠቅላላ ገቢና ለሀገረ ስብከት ፈሰስ የሚደረገው የ20 በመቶ ድርሻ ዕድገት ማሳየቱንና ብልጫ መመዝገቡን አትተዋል፡፡
በውስጣዊ ችግሮችና ድክመቶች እንዲሁም በውጫዊ ተጽዕኖዎችና ተግዳሮቶች ረገድ፣ ሪፖርቶቹና መረጃዎቹ ከጠቆሟቸው መካከል የሚከተሉት ዐበይት ነጥቦች ይገኙባቸዋል፡-
- ግጭቶችና አለመረጋጋቶች ባስከተሏቸው መጠነ ሰፊ መፈናቀሎች፣ ኦርቶዶክሳውያን ገፈት ቀማሽ መኾናቸው፤ አብያተ ክርስቲያን መዘጋታቸው፣ የፈረሱና የተቃጠሉም መኖራቸው፣ ከሰብአዊ ቀውስ በመለስ በአህጉረ ስብከቱ ኹለንተናዊ አቅም ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ መፍጠሩ፤
- በኹሉም አህጉረ ስብከት ባይኾንም ጥቂት በማይባሉት፥ የአክራሪ እስልምና፣ የፕሮቴስታንት እና የዋቄፈና እምነት ተከታዮች፣ በኦርቶዶክሳውያን ምእመናንና በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚያሳድሩት ተጽዕኖ እየጎላ መምጣቱ፤
- በዚህም ሳቢያ፣ ለቤተ ክርስቲያን ማሠሪያም ኾነ ለመካነ መቃብር ማስፈጸሚያ ቦታ በሚጠየቅበት ወቅት አፋጣኝ ምላሽ ከመንግሥት አካላት አለማግኘት፤ ይህም ችግር በተለይ እንደ ደቡብ ምዕራብ ሸዋ – ወሊሶ ባለው ሀገረ ስብከት፣ በኹሉም ወረዳዎች ላይ እንዳጋጠመ ከአብያተ ክህነት ጽ/ቤቶች ሪፖርት መቅረቡ፤
- “አባቶቻችን የተቀበሩበት ቤተ ክርስቲያን ለእኛ ይገባል” በማለት በቤተ ክርስቲያን ይዞታ ላይ ውዝግብ መፍጠርና የተነጠቁም ይዞታዎች መኖራቸው፤
- የጎሠኝነት ፖሊቲካን ከሃይማኖት ጋራ በማምታታትና ኦርቶዶክሳዊነትን የተወሰነ ወገን መለያ አድርጎ በመስበክ መዋቅራዊ አድልዎ መፈጸሙ፤ በዚህም የተነሣ ሓላፊዎች ከሥልጣናቸው እንደ ተነሡ፣ የዩኒቨርሲቲ ምሩቃን በዕውቀታቸውና በሞያቸው የመወዳደር ዕድል እንደ ተነፈጋቸው፣ ሠራተኞችም ከሥራ ገበታቸው እንደተባረሩ መገለጹ፤ በማኅበራዊ ኑሮ(በጾም ወቅት ጋብቻና ቅርጫ እየፈጸሙ ያልተሳተፉትን በማራቅ ጭምር) እንዲሁም በኢኮኖሚያዊ መስተጋብር ስልታዊ ማግለልና ቅሠጣ የታየባቸው ተንኮሎች መኖራቸው፤
- በቤተ ክርስቲያን በኩል፣ በቋንቋው ሥርዓተ አምልኮን ለመፈጸምና ለማስተማር ልዩ ልዩ ጥረቶች እየተደረጉ ቢኾንም፣ ችግሩን የሚመጥን አገልጋይ በብዛትና በጥራት ለማፍራት አለመቻሉ፤ በችግሩ አረዳድ ላይ ውስንነቶች መኖራቸውና በመፍትሔውም የአገልጋዮች አቀራረብ ወጥነት የሌለው መኾኑ፤
- ይህንም ክፍተት በመጠቀም፥ በምሥራቅ ኦሮሚያ የአክራሪ እስልምና፣ በምዕራብ ኦሮሚያ የፕሮቴስታንትና የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ፣ በመሀል ኦሮሚያ የዋቄፈና ጽንፈኞች፣ ጥንታዊቷንና የአገር ባለውለታዋን ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን፣ በወራሪነት በመፈረጅና የሰሜኖች ብቻ በማድረግ በመሠረተ ህልውናዋ ላይ እየዘመቱ መኾናቸው፤
- በአጠቃላይ ቤተ ክርስቲያን፣ በአንድ በኩል፣ “እስላማዊት ኦሮሚያ” በሚለውና በሌላም በኩል፣ “እምነቱ ዋቄፈና የኾነ፣ መገለጫውን እሬቻ ያደረገና እሴቱን የሚጠብቅ መንግሥት” በሚለው ወገን እንደ ጋራ ተቀናቃኝ ተቆጥራ በተለያዩ አካሔዶች አስከፊ ጫና እየተደረገባት እንዳለ ተዘግቧል፤ እኒህ ብዙኀኑን የማይወክሉ ጠርዘኞች፣ “ከኦርቶዶክስ የጸዳች ኦሮሚያ” በሚል ተወራራሽ መርሕ፣ በቤተ ክርስቲያን ላይ ስልታዊ ግንባር እንደፈጠሩና በሕዝብ ቆጠራውም ፍጹም የበላይነትን ለመቀዳጀት አልመው እየተንቀሳቀሱ እንደኾነ በመረጃዎቹ ተጠቁሟል፡፡
‡‡‡‡‡‡‡‡‡‡‡ በማዕከል ደረጃ፣ የአህጉረ ስብከቱን ስኬቶች ለማጠናከርና ዘላቂ ለማድረግ፣ ችግሮቹን ለመቅረፍና ተግዳሮቶቹን ለመቋቋም እንደሚያስችሉ የታመነባቸው ተግባራት ተከናውነዋል፡፡ በሰባክያንና በካህናት ሥልጠና እና ስምሪት፣ ቅዳሴያትን ጨምሮ የሥርዓት መጻሕፍት ትርጉሞች እንዲሁም የመዝሙራት ዝግጅቶች ተጠቃሾቹ ናቸው፡፡ማኅበረ ቅዱሳን፣ ሥርዓተ ትምህርት በመቅረፅና መምህራንን በማሠልጠን በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያትና በመደበኛ ጉባኤያት የሚያበረክተው ክፍተት የመሙላት አገልግሎት በቀላሉ የሚታይ አይደለም፤ የተግባር ምላሽ እየሰጡ የሚገኙ ሌሎችም ተቆርቋሪዎች ያሉ ሲኾን፣ በአካባቢ ደረጃ፣ በምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት የግንደ በረት እና አቡና ግንደ በረት አብያተ ክርስቲያን የአገልግሎት ማኅበር አንዱ ነው፡፡ የሀገረ ስብከቱ መንበረ ጵጵስና በኾነው አምቦ፣ አዳማ፣ አዲስ አበባ፣ ሰበታና ሌሎችም ከተሞች በሚኖሩ የግንደ በረት እና የአቡና ግንደ በረት ተወላጅ ምእመናንና በጎ አድራጊዎች፣ ከዐሥር ዓመት በፊት የተቋቋመው ማኅበሩ፣ በመጪው ሳምንት እሑድ፣ ሚያዝያ 6 ቀን 2011 ዓ.ም.፣ ከ7፡00 ጀምሮ “የግንደ በረት አብያተ ክርስቲያናትን እንታደግ” በሚል መሪ ቃል፣ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል አዳራሽ የገቢ ማሰባሰቢያና የምምክር መርሐ ግብር ማዘጋጀቱን አስታውቋል፡፡ ባለፉት 27 ዓመታት የተሰበከው የጎሠኝነት ፖሊቲካ የፈጠረው ጥላቻ፣ በቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ተልእኮ አፈጻጸም ላይ ያሳደረው አሉታዊ ተጽዕኖ በቁጭት ያነሣሣው ማኅበሩ፣ አገልግሎቷ የተሟላና ዘላቂ ይኾን ዘንድ የበኩሉን አስተዋፅኦ እያበረከተ ቆይቷል፡፡ “የሰሜኖች/የምኒልክ እንጂ የአንተ አይደለችም” የሚለውን ከፋፋይ ተረክ ስሑትነት በማስጨበጥ፣ አንዲት፣ ቅድስት፣ ሐዋርያዊትና ኵላዊት ቤተ ክርስቲያን እንደኾነች የሚገልጽ ኹለንተናዊ እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል፡፡

ከወረዳው 41 አብያተ ክርስቲያን ውስጥ ከ15 በላይ የኾኑት፣ ምንም አገልጋይ እንደሌላቸውና በመንፈቅ አልያም በዓመት አንዴ፣ ከሌሎች አድባራት ተለምነው፣ አውሬውንና ተናዳፊውን ታግሠው በሚመጡ ካህናት እንደሚከፈቱ የማኅበሩ አመራሮች ተናግረዋል፡፡ ከመቶ ያላነሱ የፕሮቴስታንት አብያተ እምነት በአጭር ጊዜ በተስፋፉበት የግንደ በረት ወረዳ ከተማ/ካቺሲ/ ኦርቶዶክሳውያን ያላቸው፣ አንድ የመድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ብቻ መኾኑ፣ “የፖሊቲካውን ተጽዕኖ ያሳያል” ይላሉ፡፡ ማኅበሩ፣ መንፈሳዊ ጉባኤያትን በማዘጋጀት፣ በየዓመቱ ጥቅምት 27 ቀን በሚከበረው የካቺሲ ደብረ ሰላም መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በዓለ ንግሥ ጉዞ በማድረግ፣ ያረጁ ሕንፃ አብያተ ክርስቲያንን በማደስ ችግሩን ለመቀነስ ከስምንት ዓመት በፊት የጀመረውን ጥረት አሁንም ቢቀጥልም፣ ዋነኛው መንሥኤ፣ ቤተ ክርስቲያን በልጆቿ ላይ አለመሥራቷ መኾኑን የአመራር አባላቱ አስገንዝበዋል፡፡ መንፈሳዊውን ትምህርት ከዘመናዊው ያጣጣሙ ኹለገብ ተተኪ አገልጋዮችን ለማፍራት በማሰብ፣ ከስምንት ዓመት በፊት የአንደኛ ደረጃ ዘመናዊ ት/ቤት በወረዳ ከተማው መክፈታቸውንና በቅርቡም ተመጋጋቢ የኾነ የአብነት ትምህርት ቤት ለማቋቋም ማቀዳቸውን ተናግረዋል፡፡ የካቺሲ መድኀኔዓለም መንፈሳዊ ት/ቤት የተሰኘውና በደብሩ ቅጽር ለመገንባት የታቀደው የአብነት ት/ቤቱ፦ የመማሪያ ክፍሎች፣ የተማሪዎች ማደሪያ፣ ቤተ መጻሕፍት፣ የኮምፒዩተር ማእከልና የእንግዶች ማረፊያ እንደሚኖሩት አመራሮቹ ገልጸዋል፡፡ ግንባታው ሲጠናቀቅ፣ ከወረዳው 41 አብያተ ክርስቲያን የተውጣጡ 50 ተማሪዎችን በመያዝ ሥራውን እንደሚጀምር አስታውቀዋል፡፡ በቀኑ መርሐ ግብር፣ ቀደም ሲል በተቋቋመው የካቺሲ መድኀኔዓለም ት/ቤት፣ ዘመናዊ ትምህርታቸውን እንደሚከታተሉና በአዳሪ መርሐ ግብር ደግሞ በአብነት ት/ቤቱ መንፈሳዊውን እንደሚገበዩ ገልጸዋል፡፡ “ተማሪዎቹ በወረዳው እስካሉና በሚሔዱባቸው ቦታዎች ኹሉ ብቁ አገልጋዮች ኾነው እንዲወጡ የሚያደርግ ሥርዓት እንከተላለን፤” ያሉት አመራሮቹ፣ በወረዳውም ኾነ በክልሉ የካህናትንና የዲያቆናትን እጥረት ለማቃለል አስተዋፅኦ እንደሚኖረው ተስፋቸውን ገልጸዋል፡፡ ማኅበሩ፣ የተመረጡትን ተማሪዎች አልባሳትና የምግብ ወጪ እንደሚችልና ትምህርት ቤቱን በመገንባትና በማደራጀት ረገድ፣ ምእመናንና በጎ አድራጊ አካላት፣ የገንዘብ፣ የሞያና የቁሳቁስ እገዛ እንዲያደርጉላቸው ጠይቀዋል፡፡ ከቤተ ክርስቲያኑ ኹለት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኝ የደብሩ የከተማ ይዞታ ላይ የተገነባው ዘመናዊው የመድኀኔዓለም አንደኛ ደረጃ ት/ቤት፣ ከዐጸደ ሕፃናት እስከ ስድስተኛ ክፍል ተማሪዎችን ተቀብሎ እያስተማረ ይገኛል፡፡ ከአቻ ት/ቤቶች ጋራ በተደረገ የተማሪዎች ውድድር ቀዳሚና የሌላ እምነት ተከታይ የኾኑ ነዋሪዎችም ለልጆቻቸው መማሪያ የሚመርጡት እንደኾነ ተገልጿል፡፡ በአንድ ብሎክ የጀመረውን የመማር ማስተማር ሥራ እያስፋፋ አራት ማድረሱንና ግንባታውን ሲያስፋፋ ደረጃውን እስከ 8ኛ ክፍል ማሳደግ እንደሚችል በወረዳው ትምህርት ጽ/ቤት ፈቃድ ተሰጥቶታል፡፡ ኾኖም ተጨማሪ ቦታ ጠይቆ በመከልከሉ፣ ያለውን 4ሺሕ ካሬ ያህል ይዞታ በማመጣጠን ዘመናዊ ቤተ መጻሕፍትንና ቤተ ሙከራን ያካተቱ አራት ተጨማሪ ብሎኮችን ለመገንባት ዐቅዷል፡፡ ተማሪውንና ኅብረተሰቡን በማገልገል ቋሚ ገቢ የሚያስገኙ ዳቦ ቤት፣ ወፍጮ ቤትና የእንስሳት ማድለቢያ ግንባታም እንደሚከናወን የማኅበሩ ዕቅድ ይጠቁማል፡፡ በመኾኑም፣ የአዳሪ አብነት ት/ቤቱን በመገንባትና ዘመናዊውን ት/ቤት በማጠናከርና በማስፋፋት ረገድ፣ ምእመናንና በጎ አድራጊዎች፣ በመጪው እሑድ ሚያዝያ 6 ቀን፣ ከቀኑ 7፡00 ጀምሮ፣ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በሚካሔደው የገቢ ማሰባሰቢያና የምክክር መርሐ ግብር ላይ ተገኝተው ኹለንተናዊ
