April 8, 2019

ከደማሪው ታየ!

” ስንኖር ኢትዮጵያዊ ስንሞት ኢትዮጵያ እንሆናለን ” የሚል ስላቃዊ መፈክር ይዞ አደባባይ ብቅ ያለው የድል አጥቢያው አርበኛ አብዮት አህመድ በአገር ፍቅር ስሜት ነድጃለሁ ብሎ የሰበከንን አቋሙን ወላጆቹ እንዳወጡለት ስም በአንድ ጀምበር እርግፍ አድርጎ ወዲያ ጥሎ በሌላ ስም እና ማንነት መከሰት ቀላል መሆኑን በተግባር እያስመሰከረ ነው:: የኢትዮጵያ ሕዝቦች ለብዙ ሺህ ዘመናት አብረን በክፉም በደጉም ተዋልደንና ተፋቅረን የመኖራችንን ያህል ያን ያህል የኦሮሞ አክራሪ ኦነጋውያን እንደሚሉን የተለየ ጭቆና ያደረሰባቸው ብሄር ቢኖር እንኳ በሰላም እና በፍቅር ተለያይቶ ሁሉም እንደፈቀደው የየራሱን አገር መመስረቱ የሚከብድ ባይሆንም የደሃ ደም እንደ ጅረት እለት በእለት እንዲፈስ የዲያቢሎስን እኩይ መንገድ የመረጡበት ምክንያት ለብዙዎቻችን ዛሬም ድረስ እንቆቅልሽ ነው:: በደርግም በሕወሃትም አመራር ወቅት ከ 40 ዓመታት በላይ በኤርትራ በረሃ እና በኢትዮጵያ ድንበሮች አካባቢ ጥቂት ታጣቂዎችን ይዞ ሲንከላወስ የኖረው ኦነግ አብዮት አህመድ ሥልጣን በያዘ ማግሥት ኤርትራ ድረስ ተለምኖ የክብር ቀይ ምንጣፍ ተነጥፎለት ኢትዮጵያውያን ደም ተፍተው ከሚከፍሉት የቀረጥ ገንዘብ እየተሰፈረለት ለመሪዎቹም ለአባላቱም አዲስ አበባ ላይ ቅንጡ ሆቴል እና ቢሮ ሰጥቶ እንዲሁም ከፋፋይ መርዘኛ የጥላቻ ፕሮፓጋንዳ የሚነዙበትን ሚድያ ጭምር በማደራጀት ለሽብር ተግባር ካሰለፈ ወራት መቆጠር ጀምረዋል:: የዳውድ ኢብሳ ኦነግ ሸኔ አዲስ አበባ ዙሪያ ቡራዩ አካባቢ በርካቶችን በገጀራ ጨፍጭፎ እና በጥይት ቆልቶ ሺዎችን ቤት አልባ አድርጎ ያፈናቀለበትን እኩይ የወንጀል ተግባር ለማድበስበስ የአብዬን እከክ ወደ እምዬ ላከክ አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ እንዲሉ የዓብይ መንግሥት ዛሬም ድረስ ሰላማዊዎቹን የአዲስ አበቤ ወጣቶች በወታደራዊ ማሰልጠኛ አስሮ እያሰቃየ ይገኛል:: ሕዝቡ በምሬት እና በማህበራዊ ሚድያዎች ይህ ዓይነቱን ፍርደ ገምድል እርምጃ ሲኮንን አብዮት እሳት ለብሶ እና እሳት ጎርሶ በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ይልና በኢትዮጵያ ስም እየማለ ” አገር ለማፍረስ የሚሯሯጡ እኩያን ሴራ መቼም አይሳካም ” በሚል ሽንገላ ሕዝባዊ ተቃውሞውን በኢትዮጵያ ስም ለምብረድ ይሞክራል:: አክራሪ የኦሮሞ ብሄረተኞች የኦዲፒ አባላት  እና ኦነጋውያን ሺዎችን አቅመ ደካሞች ዘር ተኮር በሆነ ሥልት ዛሬም ድረስ በግፍ እያፈናቀሉ ነው:: ከመሃል ከተማ ርቀው በሚገኙ ክልልሎች ይቅርና ዋና መዲና አዲስ አበባ ቦሌ ሚካኤል እና እንጦጦ ጫካ ሳይቀር ዛሬ ቄሮ ነን የሚሉ መሳሪያ ገጀራ እና ዱላ የሚይዙ የተደራጁ ወንበዴዎች ዜጎችን በጠራራ ጸሃይ የሚዘርፉባቸው እና በግፍ የሰው ሕይወት የሚቀጥፉባቸው የምድር ሲዖሎች ሆነዋል:: አዲስ አበባ ላይ የኦነግ ታጣቂዎችን በመላው አገሪት አሰማርቶ ሕዝብን የሚያሸብር አመራሩን የእነ ዳውድ ኢብሳ ቡድን አብይ አህመድ እየተንከባከበ እና እየቀለበ ዓይናችን እያየ ከ 18 በላይ ባንኮችን አዘርፏል:: የመሳሪያ ግምጃ ቤቶችን እያሰበረ አደገኛ የጦር መሳሪያ ታጣቂዎቹ እጅ እንዲገባ አድርጓል:: ሕወሃት ሊያጠፋው የተቃረበውን ኦነግ ነፍስ ዘርቶበት ሥውር የኢትዮጵያ መንግሥት ፈላጭ ቆራጭ አድርጎ በላያችን ላይ ሾሞታል:: በሶማሌ እና የኦሮሞ ታጣቂዎች መካከል በተከሰተው ግጭት ኦነጋውያን እና የነ ለማ ቡድን በሚስጥር በሚልዮን የሚቆጠሩ ዜጎችን አፈናቅለው የአዲስ አበባን እና አካባቢው የሕዝብ አሰፋፈር ስብጥር ለመቀየር / Demography Change / የግጭቱ ሰለባ ሆነዋል ያሏቸውን በሚልዮን የሚቆጥሩ አካባቢዎች በማስፈር በሕገወጥ ግንባታ ስም የለላ ብሄር ተወላጆችን ማፈናቀሉን ገፍተውበታል:: አብይ አህመድ ነፍስ የዘራበት ሊከስም ተቃርቦ የነበረው ኦነግ ያለ እፍረት ህዝብ በአደባባይ ዘቅዝቆ ገሎ እየሰቀለ በመኪና የሚጓዙ ሰላማዊ ዜጎችን በጥይት ፈጅቶ እያቃጠለ አረመኔ ድርጊት እንዲፈጽም ከማደፋፈሩም በላይ የራሴን ገዥ መሬት ይዣለሁ የሚል መግለጫ ሁሉ በመገናኛ ብዙሃን እንዲያስነግር በማድረግ  ” ዓብዩ የኔ አንተን ባየ ዓይኔ ባንዳ ለምኔ ” ሲል በአደባባይ እየዘመረ ድጋፍ በሰጠው የኢትዮጵያ ሕዝብ እና በአገሪቱ ላይ ታላቅ ሴራ እና ክህደት ፈጽሟል:: አሸባሪውን የኦነግ ቡድን በአንቀልባ አዝሎ አስገብቶ አዲስ አበባ ላይ የሚያሽሞነሙነው አብይ አህመድ የሶማሌ የአማራ የቤኒሻንጉል የአርጎባ የጉጂ የኮሬ እና በርካታ የደቡብ ብሄሮችን በተለይም ንጹሃን ዜጎችን እንዲፈናቀሉ እንዲገደሉ አካላቸው እንዲጎድል በህይወት እንዳይኖሩ ሥልታዊ የዘር ማጥፋት በማድረስ እና ቤተ እምነቶች እንዲቃጠሉ በማድረግ ዓለማቀፍ የወንጀል ድርጊት አስፈጽሟል::

አክቲቪስት ነኝ የሚለን አክራሪ ብሄረተኛው እና የሴራ ፖለቲካው መሃንዲስ እንዲሁም  ዋና የብጥብጡ ጠንሳሽ ጃዋር መሃመድ ሰሞኑን በሚመራው የቴሌቪዥን ጣቢያ በገደምዳሜ እንደነገረን የኦነግ ሰራዊት ሙሉ ለሙሉ ትጥቅ እንዳይፈታ የሚፈልጉት ኦነጎቹ ብቻ ሳይሆኑ በባንክ ዘረፋው ተባባሪ የሆኑት የአብይ ፓርቲ ኦዴፓ አባላትም ጭምር ናቸው :: ይህ የአገርን ሃብት የመዝረፍ ወንጀል ተቃውሞው እያየለ ሲመጣ እነ ዳውድን እና ሸሪኮቹን የኦዴፓ አባላት ከተጠያቂነት ለማስመለጥ ኦነግ እና ታጣቂዎቹ ተለያዩ የሚል ዜና አቀነባሮ ማሰማትም ቢሆን የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በወንጀል ለፍርድ ከመቅረብ እንደማያድን እነ አብዮት አብይ ጠንቅቀው ሊረዱት ይገባል:: እናም የአሸባሪዎች አጋፋሪ ዓብይ ሆይ ቢያንስ ልጆች ወልደሃል :: ለዛሬው ጊዜያዊ ወንበረህ ሳይሆን መጻኢ እድላቸውን በውል አስብ :: የደሃ እምባ እና በየእለቱ በጠገቡ የኦሮሞ አክራሪ ብሄረተኞች እኩይ ሴራ የሚፈሰው ደም ነገ ባንተም በልጆችህም ላይ የማይከፈል እዳ ማምጣቱ እንደማይቀር የሩቁን ታሪክ ማስታወስ ቢሳንህ በአንቀልባ አዝለው እዚ ካደረሱህ የትህነግ አመራሮች ተማር እና የገለማ የፖለቲካ ቁማርህን እንድታቆም ነው በግፉአን ወገኖቻችን ስም የምንጠይቅህ:: መሰረተ ልማት የሌለው በድህነት የሚማቅቀው ቁርስ በልቶ እራቱን መድገም የሚሳነው የአማራው ብሄርም ሆነ ሌላው ማህበረሰብ ከኦሮሞው የተለየ ጥቅምም ሆነ ድሎት አግኝቶ አለመኖሩን ጠንቅቀህ ታውቀዋላህና ኢትዮጵያውያን ጎትተህ ባመጣሃቸው ኦነጋውያን አሸባሪዎች አረመኔዎች እና እኩያን እየተፈጁ እና እየተፈናቀሉ አዲስ አበባን ወርቅ አስመስላታለሁ የጎረቤት አገራትን አስማማለሁ የሚለው የህሊና ቢሶች ጨዋታህ የራሷ እያረረባት የሰው ታማስላለች ከሚባለው ብሂል ያለፈ አይደለምና አጓጉል ሽንገላህን ትተህ በሰላም ድብቅ አጀንዳህን ይፋ እንድታደርግ እንጠይቅሃለን:: በዚህ ዓይነቱ አስከፊ እና በገዛ አገር ከባርነት በከፋ ስቃይ እና ባይተዋር ሆኖ ከመኖር በእንዲህ ዓይነቱ የዘረኞች አድሏዊ ሥርዓት አንደኛ እና ሁለተኛ ዜጋ ሆኖ መከራ ከማየት በሰላም ተለያይቶ በራስ ጎጥ በሰላም ቆሎ ቆርጥሞ መኖር ጸጋ ነውና ስውር አጀንዳህን አደባባይ አውጥተህ የሕዝብ ፍጅት ሳይደርስ የንጹሃንን ደም ገብረህ የግፈኞች አገርን የመመስረት ፍላጎትህን ገታ አድርገህ ለዘመናት የቋመጥክለትን ምኞትህን በሰላም እና በሰላማዊ መንገድ ብቻ ትፈጽም ዘንድ ከአደራ ጭምር እንማጸንሃለን::

በገዛ ዜጋ እና አገር በስቃይ እና በባርነት ከመኖር ነጻነት !!!!!

ደማሪው ታየ