April 24, 2019

ጠ/ሚር ዐቢይ አሕመድና የልዑካን ቡድናቸው ከቻይና ፕሬዚዳንት ሺ ዥንፒንግ ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አካሂደዋል::

በውይይቱ ወቅት ፕሬዚዳንት ዥንፒንግ የጠ/ሚር ዐቢይ አሕመድን አመራርና ያለፈውን አንድ ዓመት የኢትዮጵያ የለውጥ ሂደት እንደሚያደንቁ ገልፀዋል።

ሀገራቸው ለኢትዮጵያን ዕድገት ትልቅ ቦታ እንደምትሰጥም ገልፀዋል::

የቻይና መንግሥት የሸገርን ማስዋብ ፕሮጀክትን ጠቀሜታ ይረዳል ያሉት ፕሬዝዳንት ዥንፒንግ ለፕሮጀክቱ የገንዘብ ድጋፍ ለማድረግ መንግሥታቸው እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል::

ጠ/ሚር ዐቢይ አሕመድ በበኩላቸው ኢትዮጵያ ከቻይና ጋር ያላትን ሁለንተናዊ የስትራቴጂ አጋርነት በማጠናከር እንደ አዲስ ጅቡቲ የባቡር መንገድ ፕሮጀክት ያሉ እዳዎችን ለመከለስ የሚረዱ ወሳኝ እንቅስቃሴዎችን ለመተግበር ያላትን ቁርጠኝነት ለፕሬዝዳንት ዥንፒንግ አስረድተዋል::

የባቡር ፕሮጀክቱ ኢትዮጵያ ተሳታፊ የሆነችበት የቤልት ኤንድ ሮድ ማዕቀፍ ቀዳሚ ውጤት ነው::

ከአለም አቀፍ ቀጠናዊና ሁለትዮሽ መግባባቶች በተጨማሪ የወጣት ኢንጂነር ናዝራዊት አበራ እስርም እንዳሳሰባቸው ጠ/ሚር ዐቢይ አሕመድ ገልፀዋል::

ሁለቱም ወገኖች በሀገራቱ መካከል ያለውን ትብብር በተለያዩ ዘርፎች አጠናክረው ለመቀጠል ተስማምተዋል::

ምንጭ :-ጠቅላይ ሚንስትር ፅ/ቤት