April 27, 2019

ትላንት ኢትዮጵያ ውስጥ ሰዎች ሃሳባቸውን በመግለጻቸው የተነሳ ይቆጣና ጥቃት ይሰነዝር የነበረው በወያኔ የሚመራው የጎሳ ብሔረተኛው ቡድን እና አጃቢዎቹ ነበሩ። ሰዎች ሃሳባቸውን በመግለጻቸው ብቻ ሽብርተኛ እየተባሉ በየማጎሪያው ይታሰሩ እና ይሰቃዩ እንደነበር የቅርብ ትውስታችን ነው።

ብሔረተኛ ገዢዎቹ ዛሬም በስልጣን ላይ ያሉ ቢሆንም የአፈናው ነገር ለጊዜው ጋብ ብሏል። እንደገቡት ቃልም ከተፈጸመ ከነወዲያኛው ሰዎች በሃሳባቸው የማይታሰሩባት፣ የማይዋከቡባት እና የማይሰደዱባት ኢትዮጵያ እውን ትሆን ይሆናል። በእዚህ ተስፋ ውስጥ እያለን አፋኝ የሆኑ እና የአፋኝነት ዝንባሌን ከወዲሁ እያሳዩ ያሉ ብሔረተኛ ቡድኖች፣ ግለሰቦች እና የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደ አሸን መፍላታቸው አፈናን የማስወገዱ ትግል ገና ብዙ መንገድ እንደሚቀረው ነው የሚያሳየው። ለዚህም አንዳንድ የቅርብ ትውሳቶቻችንን እንደማሳይስ ላስቀምጥ፤

እነዚህን የመሳሰሉ በርካታ ምሳሌዎች መጥቀስ ይቻላ።

ከላይ ለምሳሌነት የጠቀስኳቸው ክስተቶች ሁለት ነገር ያመላክታሉ፤

የመጀመሪያው ዜጎች ሃሳባቸውን በነጻነት እንዳይገልጹ ለማሸማቀቀ የሚደረገው ጫና እና አፈና ከመንግስት እጅ ወጥቶ በብሔረተኛ ቡድኖች መቀጠሉን ሲሆን፤ እነዚህ ቡድኖች ማሰር ባይችሉም ያሸማቅቃሉ፣ ያዋክባሉ፣ ያጠለሻሉ፣ አንዳንዴም እንደ አቶ አዲሱ አረጋ አይነት በራሱ የማይተማመን ፈሪም ሲያገኙ በአደባባይ የተናገረውን ነገር መልሶ እንዲውጠው እና አምኖ የተናገረውን እውነት ተሸማቆ ይቅርታ እንዲጠይቅበት ያደርጉታል።

ሁለተኛው አስገራሚ ነገር እራሳቸውን የሕዝብ ተወካይ አድርገው በማቅረብ ሕዝብ ተሰደበ በሚል ሙግት እና ክስ ማቅረባቸው ነው። እርግጥ የብሔረተኞች አንዱ መገለጫ የሄው ነው። የአንድን ብሔረሰብ ወይም ኃይማኖት ወይም ቡድን ስሙን ይዘው ስለተደራጁ ብቻ እራሳቸውን የሕዝቡ ብቸኛ ተወካይ አድርጎ ማቅረብ። ኢትዮጵያ ውስጥ የሕዝብ ውክልና ያለው ገዢውን ፓርቲ ጨምሮ የፖለቲካም ሆነ ሌላ አይነት ድርጅት ወይም ቡድን ገና አልተፈጠረም። የኢትዮጵያ ሕዝብ በአገር ደረጃም ሆነ በብሄር ደረጃ እራሱን ወክሎ አያውቅም። እድሉን መች አግኝቶት፣ ማንስ ሰምቶት።

ለማንኛውም ግለሰቦች ሃሳባቸውን በነጻነት እንዳይገልጹ በሕዝብ፣ በሃይማኖት፣ በብሔር ተቆርቋሪነት ስም የሚደረጉ ጫናዎች እና ማስፈራሪያዎች የዲሞክራሲ ባህል እንዳይኖር ከማድረግም ባሻገር አፈናን ያጸናል። ይህ አይነቱ በሽታ የህዝብ አይንና ጆሮ ነን በሚሉ የኢሳት አይነት ሚዲያዎችም ሲፈጸም እያየን ነው። በቅርቡ በጋዜጠኛ ርዕዮት እና በቴውድሮስ ጸጋዮ ቃለ ምልልስ ላይ የተደረገውም አፈና የዚህ አንዱ መገለጫ ነው።

ሃሳቦች በሃሳብ ይሞገቱ። ሕዝብ ሃሳቦችን የማወዳደር እድል ይሰጠው። የሃሳብ ገበያን እያነጠፉ ዲሞክራሲ ሊገነባ አይችልም። የዲሞክራሲ ሥርዓት የሚገነባው በሃሳቦች ገበያ ነው። በአደባባይ የሚደረጉ የሃሳብ ሙግቶች ሦስት ነገሮችን ይጠይቃሉ። በሚናገሩበት ጉዳይ ጥልቅ እውቀት፣ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ እና የሚመጣውን ተጠያቂነት ለመቀበል የሚያስችል ድፍረት እና ሥልጡን የሆነ የሃሳብ አገላለጽ ክህሎት። እነዚህን እሴቶች ካላዳበርን ነገራችን ሁሉ ከርሞ ጥጃ ነው የሚሆነው።

የቡርቃ ዝምታ ውሸት ነው ያለን ሰው በሰልፍ እና ዛቻ ጸጥ ማሰኘት፣ አማራ የለም ያለውን ሰው በክስ አፉን ለመለጎም መዳዳት፣ የታሪክ ምርምር ውጤቱን የሚናገር እንደ ፕ/ር ሃይሌ ላሬቦን አይነት ምሁርን በዛቻ እና በስድብ እንካ ሰላምታ መግጠም የሃሳብ ነጻነት ላይ የተነጣጠረ የፈሪዎች ዘመቻ ነው። ይህ አይነቱ እንቅስቃሴ በጊዜ ካልተገራ እያደር የፖለቲካ ባህል ይሆናል። ያኔ በተበላሸው እና መደማመጥ ቀድሞውንም በጠፋበት የፖለቲካ ባህላችን ላይ ይህ ሲታከልበት ያው እንኳንም ዘንቦብሽ ነው የሚሆነው።

መልካም የፋሲካ ባዕል ለሁሉም የክርስትና እምነት ተከታይ ይሁንቶ

አቶ ያሬድ ሃይለማሪያም፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች