30 ኤፕረል 2019

የተወለዱት በምዕራብ ኦሮሚያ ደምቢ ዶሎ ከተማ ነው ። የመጀመሪያ ድግሪያቸውን በያኔው ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ዩኒቨርሲቲ ከሠሩ ጥቂት ዓመታት በኋላ ወደ ጀርመን አቀኑ። ከተማሪዎች እንቅስቃሴ ጀምሮ በኢትዮጵያ ፖለቲካ የህይወት ዘመን ተሳትፎ አድርገዋል ሊባል ይችላል።
ለበርካታ ዓመታት ከኖሩባት ጀርመን ሲመለሱ የአሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ኦህዴድን ተቀላቀሉ። የቀድሞ ፕሬዝደንት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ህልፈት ባለፈው ቅዳሜ ነበር ለዓመታት ከኖሩበት ከወደ ጀርመን የተሰማው።
ዶ/ር ነጋሶን አንዳንዶች በእጅጉ በመርህ እንደሚያምን ፖለቲካኛ ሌሎች ደግሞ ለፖለቲከኛ የሚሆን ስብእና የሌላቸው አድርገው ይስሏቸዋል።
ዶ/ር ነጋሶ -የጋጤኛው ማስታወሻ “የታሰረ አንበሳ”
ብዙዎች በአፃፃፍ ችሎታው በተደነቁበት የጋዜኛው ማስታወሻ መፅሃፉ ተስፋዬ አብረአብ ዶ/ር ነጋሶን ቤተ መንግስት ውስጥ እንደታሰረ አንበሳ ገልጿቸዋል። ኋላ ግን ኢህአዴግን ተለይተው የተቃውሞ ፖለቲካውን በመቀላቀላቸው እሳቸውን የሚያይበት መንገድ መቀየሩን ተስፋዬ ይናገራል።
የታሰረ አንበሳ ያላቸው ምንም እነኳ አቅም ቢኖራቸው ህወሃትን ያገለግሉ ስለነበር እንደሆነ “የጋዜጠኛው ማስታወሻ የታሰረው አንበሳና በኋላ በህዝብ ጉዳይ ላይ በሰፊው የተሳተፉት ዶ/ር ነጋሶ የተለያዩ ናቸው” በማለት ያስረዳል።
ኋላ ላይም ዶ/ር ነጋሶና ተስፋዬ ይገናኙ እንደነበር ተስፋዬ ይናገራል። የሚገናኙት በኢሜልና በስልክ የነበረ ሲሆን ምክንያቱ ደግሞ በአንድ ፎረም ላይ ዶ/ር ነጋሶ ሊያቀርቡት በነበረ ፅሁፍ ምክንያት እንደነበር ያስታውሳል።
ዶ/ር ነጋሶ የማስታወቂያ ሚኒስትር ሳሉ በወቅቱ የኢትዮጵያ ፕረስ ድርጅት መምሪያ ሃላፊ ለነበረው የተስፋዬ አለቃው ነበሩ። እሱና ሌሎች ባልደረቦች ያናግሯቸው የነበረው እንደ ጓደኛ እንደነበር፣ ራሳቸውን ከፍ የማያደርጉ ፣ አክብሩኝም የማይሉ ሰው እንደነበሩ ይናገራል።
“ሚኒስትር እያሉ ከመኪና ወርደው ሱቅ ላይ ሲጋራ ገዝተው የሚሄዱ ሰው ናቸው” ሲልም ያክላል።
በጋዜጠኛው ማስታወሻ ‘የታሰረ አንበሳ’ ያላቸው እንደ እሳቸው ያለ ጥሩ የታሪክ ምሁር፣ ቅን እና ጥሩ ስብእና ያለው ሰው እንዴት ከዚያ “ሰው በላ” ስርዓት ጋር አብሮ ይሰራል በማለት እንደሆነም ይገልፃል።
ህገመንግስቱ መከበር አለበት የሚል አቋም እንደነበራቸው ይህ ብቻም ሳይሆን ሊከበር ይችላል ብለው ያስቡም እንደነበር የሚናገረው ተስፋዬ “ይህ ቅንነታቸውን ያሳያል ።ይህ ቀንነታቸው ደግሞ ከፖለቲካ ሰው የማይጠበቅ ነበር ” ይላል።
‘ኢህአዴጉ’ ዶ/ር ነጋሶ እና ‘ኦነጉ’ ሌንጮ
አቶ ሌንጮ ለታና ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን የተከታተሉት አንድ ላይ ነው። አብሮ አደጎች ነበሩ ማለት ይቻላል።
የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ሳሉ ብዙ አፍሪካ ሃገራት ከቅን ግዢዎቻቸው ነጻነታቸውን የተቀዳጁበት ወቅት ስለነበር የራስን መብት በራስ ስለመወሰን ብዙ ጊዜ ያወሩ እንደነበር አቶ ሌንጮ ያስታውሳሉ።
አቶ ሌንጮ ለከፍተኛ ትምህርት ወደ አሜሪካ ሲያቀኑ ዶ/ር ነጋሶ ደግሞ ቀዳማዊ ሃይለስላሴ ዩኒቨርሲቲን ተቀላቀሉ። በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው ዶ/ር ነጋሶ የተማሪዎች ንቅናቄ ተሳታፊ እንደነበሩ አቶ ሌንጮ ያስታውሳሉ።
እኛ የኦሮሞ ነጻነት ግንባርን ስንመሰርት እሱ ለትምህርት ጀርመን ነበር። በወቅቱ የታሪክ ትምህርት ለማጥናት ነበር የሄደው።
“አንተ ውጪ ሃገር ሄደህ ታሪክ ተማር እኛ ታሪክ ሰርተን እንጠብቅሃለን ብዬው እንደነበር ከብዙ ጊዜ በኋላ አስታውሶኛል። እኔ ግን ረስቼው ነበር።”ይላሉ አቶ ሌንጮ
እንደ አቶ ሌንጮ አገላለፅ ዶ/ር ነጋሶ በጣም እልኀኛና በአንድ ጉዳይ ላይ አቋም ከያዙ ወደኋላ የማይሉም ናቸው። ምን ይደርስብኛል ብለውም አያስብም።”ለዚህም ይመስለኛል ከኢህአዴግ ጋር የተለያየው።”ይላሉ።
“ፕሬዝዳንት በነበረበት ወቅት ለስራ ወደ ውጪ ሃገራት ሲሄድ ብዙ ጊዜ ተገናኝተን እናወራ ነበር። ያው እኔ ኦነግ እሱ ደግሞ ኢህአዴግ።ነገር ግን በሃሳብ ብቻ ነበር እርስ በርሳችን የምንታገለው።”

“በኢህአዴግ ክፍፍል የወሰደው አቋም ታሪካዊ ነው”
በወቅቱ ትግል ላይ የነበረው ህዝባዊ ወያነ ሃርነት ትግራይ ህወሃት ነጋሶን ጀርምን ሃገር ሳሉ እንዴት እንደቀረበና እንዳነጋገራቸው የቀድሞ የህወሃት ማእከላዊ ኮሚቴ አባልና የአረና ፓርቲ መስራች አቶ ገብሩ አስራት ያስታውሳሉ።
• በእርጥብ ሳርና ቅጠል ጥቃትን ያስቆሙ አባቶች
ዶ/ር ነጋሶ ኦህዴድ ፤ አቶ ገብሩ ደግሞ ህወሃት ሆነው ብዙ ጊዜ በማእከላዊ ኮሚቴ ስብሰባዎች ይገናኙ ነበር። ሁለቱም ኢህአዴግን ለቅቀው በመውጣ እንደገና በተቃዋሚ መስመር ሰልፍ ላይም እንደገና ተገናኝተዋል። እናም አቶ ገብሩ ዶ/ር ነጋሶን በእነዚህ ሁኔታዎች ሁሉ አይተዋቸዋል።
ዶ/ር ነጋሶ ከኢህአዴግ ከተለዩ በኋላ ደምቢደሎ ላይ ተወዳድረዋል የአንድነት ፓርቲ ሊቀ መንበር ሆነውም አገልግለው ነበር።
“አቋም ያለው ቅን ሰው ነው። ብቻውንም ቢሆን ላመነበት ነገር እንደሚቆም ያረጋገጠ ሰው ነው” በማለት ይገልጿቸዋል አቶ ገብሩ ዶ/ር ነጋሶን።
በተለይም በኢትዮጵያና በኤርትራ ጦርነት ከዚያም ኢህአዴግ ውስጥ መከፋፈል ተፈጥሮ በነበረበት ወቅት የያዙትን አቋም ከዚያም ኢህአዴግ አምባገነን ሆኗል ብለው ድርጅቱን የለቀቁበትን ሁኔታ አቶ ገብሩ ያስታውሳሉ።
በጥቅሉ “ላመነበት ነገር ቆሞ ያለፈ ሰው ነው” በማለት ነው የሚገልጿቸው።
ኢህአዴግ ከባድ መከፋፈል ውስጥ በነበረበት በዚያ ወቅት ድርጅቱ አምባገነን እየሆነ አደገኛ መንገድ ላይ መሆኑን ብዙዎች ሊሞግቷቸው ይቅርና ሊያናግሯቸው በሚፈሯቸው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ፊት በግልፅ መናገራቸው ዶ/ር ነጋሶን በፖለቲከኞች በህዝብ ዘንድም ከፍተኛ ነጥብ ያሰጠ እርምጃ ነበር።
“እኔ እንኳን ስብሳባው ላይ አልነበርኩም ግን ጓደኛዬ አምባሳደር አዋሎም ነግሮኛል። መለስ መንግስቱ የጦር መኮንኖችን አሸንፎ የተናገረውን የሚመስል ነገር ሲናገር ልክ መንግስቱን መሰልከኝ ብሎ በድፍረት ተናግሮታል” ይላሉ። በርግጥም ይህ የዶ/ር ነጋሶ ህይወትና የፖለቲካ እርምጃ ላይ በተፃፈውና “ዳንዲ” በተሰኘው መፅሃፋቸው ላይ የሚገኝ ሲሆን በተባለው ስብሰባ ላይ ተገኝተው የነበሩት አምባሳደር ገነት ዘውዴ ‘እንዴት መለስን ከመንግስቱ ጋር ታመሳስለዋለህ’ ብለው ስለማልቀሳቸውም ተፅፏል።
አቶ ገብሩ ያ ጊዜ አቶ መለስ ዜናዊ በዶ/ር ነጋሶ ላይ ቂም በመያዝ እስከ መጨረሻው ሊያጠቋቸው የወሰኑበት እንደሆነ ያምናሉ። ከዚያ በኋላ በዶ/ር ነጋሶ ላይ የሆነውም የዚህ ማረጋገጫ ነው ይላሉ።
በተቃራኒው ዶ/ር ነጋሶ ብዙ በደል ባደረሱባቸው የኢህአዴግ ሰዎች ቂም እንዳልነበራቸው አቶ ገብሩ ምስክርነታቸውን ይሰጣሉ።
አቶ ገብሩ ራሳቸውም ብዙ በደሎች ቢደርሱባቸውም ገለልተኛ ካልሆነ ስርዓት ፍትህ አገኛለው ብለው ባለማመን ወደ ህግ አልሄዱም። “እሱ ግን ፍርድ ቤት እየሄደ ይሟገት ነበር” በማለት እንደ ቀድሞ ፕሬዝዳንትነት የሚገባቸውን መብት በሚመለከት በሁለት ፍርድ ቤቶች አሸንፈው እንደነበር ይናገራሉ።
“ነገሩ ኋላ የፖለቲካ ውሳኔ ነው የሆነው። የተፃፈለትን ደብዳቤ አሳይቶኝ ነበር አሁንም እጄ ላይ አለ” ይላሉ።
ብዙዎች ‘ዳንዲ፡ የነጋሶ መንገድን” ካነበበሩ በኋላ የዶ/ር ነጋሶ ስብእና የፖለቲከኛ ዓይነት አይደለም የሚል አየስተያየት ሰንዝረው ነበር። አቶ ገብሩ በዚህ አስተያየት በተወሰነ መልኩ ይስማማሉ። ነገር ግን ለሳቸው ችግሩ የዶ/ር ነጋሶ ስብእና ሳይሆን የኢትዮጵያ ፖለቲካ አካሄድ ብልጣብልጥነትና አድርባይነት መሆኑ ነው።
“የመርህና የዓላማ ፖለቲካ የሚያራምድ ሰው በአገራችን ፖለቲካ ቦታ የለውም ይላሉ። እሱ ደግሞ ግልፅ፣ የዋህና ቀጥ ብሎ የሚሄድ ነው” ይላሉ።
“ዶ/ር ነጋሶ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ተንኮል መጠን መሳያ”
የ ‘ዳንዲ’ ፀሃፊ አቶ ዳንኤል ተረፈ ለመፅሃፉ ከዶ/ር ነጋሶ ጋር ለሶስት ወራት ቃለ ምልልስ አድርጓል።
ቁሳዊ ነገር ላይ ብዙ ጉጉት የላቸውም የሚላቸው ዶ/ር ነጋሶ የኢትዮጵያ የተንኮልና የሴራ ፖለቲካ ልክ ማሳያ ናቸው ሲልም ይደመድማል።
ኑሯቸው እንደ ቀድሞ ፕሬዘዳንት ሳይሆን እንደ ተራ ግለሰብ እንደነበር የአደባባይ ምስጢር ነው። ህልፈታቸውን ተከትሎ ብዙዎች እንዴት በተለያየ አጋጣሚ እንዳገኟቸው ማህበራዊ ድረ ገፅ ላይ ፅፈዋል።
አንድ ሰው ታክሲ ላይ እንዳገኛቸውና መኪናቸው ጋራጅ ገብቶ እንደሆነ ጠይቋቸው እሳቸውም መኪና የለኝም ብለው በቀጥታ እንደመለሱለትና እሱም ምን ያህል እንደሚያከብራቸው እንደገለፀላቸው በትዊተር ገፁ ላይ አስፍሯል።
አቶ ዳንኤል እንደሚለው ደግሞ ላመኑበት ነገር እንደ ተራ ሰው ከመኖር በላይ ሁሉ ዋጋ ለመክፈል ዝግጁ ነበሩ ይላል።
ይኖሩ ከነበረበት የሚያፈስ ቤት እንዲለቁ ደብዳቤ ተፅፎላቸው እንደነበር በማስታወስ ” የቀድሞ ፕሬዝዳንት ጎዳና ተዳዳሪ ሊሆኑ ነው የሚል ፅሁፍ ፍትህ ጋዜጣ ላይ ሲወጣ ነው መልሰው ነገሩን የተውት” ይላል።
እሱ እንደሚለው ውሳኔአቸው የሚያስከፍላቸውን ዋጋ ሁሉ ለመክፈል የስነ ልቦና ዝግጅት ነበራቸው ዶ/ር ነጋሶ።
እንደ አቶ ገብሩ ሁሉ ገዳይ ጀግና በሚባልበት ፣ ተንኮለኛና ሴረኛ አሸናፊ ሆኖ በሚወጣበት የኢትዮጵያ ፖለቲካ የዶ/ር ነጋሶ እንደ ገራገር መታየታቸው የሚገርም አይደለም ይላል ዳንኤል።
በኢህአዴግ ሂስህን አውርደህ መቀጠል ፣ ተራ አባል ሆኖ መቀጠል ፣ መሄድ የሚሉ ሶስት ምርጫዎች ሲቀርቡላቸው በመህር ላይ ቆመው ከድርጅቱ ለመልቀቅ የወሰኑ ፖለቲካኛ መሆናቸውን የሚናገረው ዳንኤል “ጥንቁቅ ፖለቲካኛና የሚያምኑበትን ለማድረግ ወደ ኋላ የማይሉ ናችው” ይላል።
የዶ/ር ነጋሶ ሁለተኛ መፅሃፍ በመጠናቀቅ ላይ እንደነበር ዳንኤል ይናገራል። ስነዳ ላይ እጅግ ጎበዝ ናቸው የሚላቸው ዶ/ር ነጋሶ ለቤተ መፃሀፍት የሚሆኑ መፅሃፍት፣ ጋዜጦችና በርካታ ፅሁፎች እንዳሏቸውም ይናገራል።
“ኢህአፓ የበተነው ወረቀት፣ መኢሶን የፃፈው ፅሁፍ ና አንድ ጊዜ ብቻ የታተማ የቀረች መፅሄት እና የአሁኑ መፅሄትና ጋዜጦች እያንዳንዱ እትም የሚገኘው ዶ/ር ነጋሶ ቤት ነው” ይላል።