May 2, 2019
Source: https://mereja.com/amharic/v2/113743

ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ቃል-አቀባይ አቶ ገለታ ሀይሉ ጋር ዛሬ ያደረግኩት አጭር የስልክ ቃለ- መጠይቅ:
Elias Meseret Taye
ጥያቄ: ከቀናት በፊት በክልላችሁ በሚገኙ የአማራ ክልል ተወላጆች ላይ ጥቃት መፈፀሙን ተከትሎ አሁን ተወሰደ ስለተባለው የአፀፋ እርምጃ መረጃ አለዎት?
መልስ: መረጃው ትክክል ነው። ድርጊቱ እንደተፈፀመ እና ዘግናኝም እንደነበረ መረጃ አለ።
ጥያቄ: ምን ያህል ሰው ተጎድቷል?
መልስ: ዝርዝር መረጃዎችን ለማቅረብ አሁን ይቸግረኛል። በቁጥር ደረጃ ዝርዝር ወደፊት እንገልፃለን።
ጥያቄ: እነዚህ የአፀፋ ጥቃት ተወሰደባቸው የተባሉት አካባቢዎች የት ናቸው?
መልስ: እንግዲህ ችግሩ መጀመርያ ላይ የተነሳው ዳንጉር ወረዳ ላይ ሚያዝያ 17 ነበር። አሁን ደሞ ትናንት እና ከትናንት ወዲያ ጃዊ በምትባል በአማራ ክልል ውስጥ በምትገኝ ወረዳ ላይ ቅድም ያልኩት የአፀፋ እርምጃ ተከስቶ ብዙ ህዝብ እንደሞተ፣ ቆስሎ ሆስፒታል እንደገባ እና እንደተፈናቀለ መረጃ አለን። እንግዲህ ጃዊ ላይ ሁለት እና ከዚያ በላይ ቀበሌዎች ላይ የጉሙዝ ብሄረሰብ ይኖራል። እነሱ ላይ ነው ጥቃቱ የተፈፀመው።
ጥያቄ: የመከላከያ እና ሌሎች የፀጥታ ሀይሎች በቦታው አልደረሱም?
መልስ: መከላከያ እየገባ ነው። ድርጊቱ እንደደረሰ የታወቀውም መከላከያ ከገባ በሁዋላ ነው። ስለዚህ ይህ መረጃ መከላከያ ዘንድም ይገኛል።
Note: የአማራ ክልል ቃል- አቀባይ አቶ አሰማኸኝን በስልክ ለማግኘት ያረግኩት ሙከራ እስካሁን አልተሳካም። ቆይቼ ሞክሬ ካገኘሁዋቸው መልሳቸውን ይዤ እቀርባለሁ።Filed in:Amharic