May 8, 2019

Source: https://fanabc.com

አዲስ አበባ ፣ ሚያዚያ 30 ፣ 2011 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያና የአውሮፓ ህብረት የ33 ነጥብ 5 ሚሊየን ዩሮ የእርዳታ ስምምነት ተፈራረሙ።

ስምምነቱን የኢፌዴሪ የገንዘብ ሚኒስትር ዲኤታ አቶ አድማሱ ነበበ እና በኢትዮጵያ የአውሮፓ ትብብር ልዑክ መሪ ኤሪክ ሃበርስ ተፈራርመውታል።

የዛሬው ስምምነት የአውሮፓ ህብረት አደጋን ለመቀነስ ለሚተገብረው ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የሚውል መሆኑን ከገንዘብ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

ፕሮጀክቱ አደጋን ለመቋቋምና ለመቀነስ የሚደረገውን ጥረት በማገዝ ማህበረሰቡንና አባወራዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ሲሆን፥ መፈናቀልንና ህገ ወጥ ስደትን ለመቀነስ ያግዛልም ነው የተባለው።

ድጋፉ ከህብረቱ አደጋን ለመቀነስ ከሚተገበረው እና ከአውሮፓ ልማት ፈንድ ፕሮጀክት የተገኘ ነው።

ፕሮጀክቱ በአራት አመት ተኩል በአማራ፣ ኦሮሚያ፣ ሶማሌ እና በደቡብ ክልል መንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች፣ በፌደራልና በክልል መንግስታት የሚተገበር ይሆናል።

ቤተሰብና ማህበረሰቡን ማጠናከር፣ የክልሎችን አደጋ የመቋቋም አቅምን ማሳደግና ተጋላጭነትን መቀነስ፣ የማህበረሰቡን ሰብዓዊ እና ኢኮኖሚያዊ ተጎጅነት መቀነስ እንዲሁም የሃገር ውስጥ ተፈናቃዮችን በኢኮኖሚው መስክ ተጠቃሚ ማድረግ የፕሮጀክቱ አላማ ነው ተብሏል።

አደጋ የመቋቋም አቅምን ከማሳዳግ ባለፈም የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓትን ማጎልበት እና የአደጋ ጊዜ ማገገሚያ ፈንድ ማቋቋምንም ያካትታል።