ዶቼ ቬለ – በዛላምበሳ፣ ራማ እና ሑመራ በኩል ወደ ኤርትራ በሚወስዱ መንገዶች የጉምሩክ ጣብያዎች ለመክፈት የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች በኢትዮጵያ በኩል መጠናቀቃቸውን የጉምሩክ ኮምሽን ገለፀ። የጉምሩክ ጣብያዎቹ ጽሕፈት ቤት አቋቁመው፣ ሠራተኛ ተመድቦላቸው ሥራ ለመጀመር ዝግጁ መሆናቸውም ተመልክቷል።
ከኢትዮ ኤርትራ የሰላም ስምምነት በኋላ ተከፍተው የነበሩት የድንበር መንገዶች እስከ ተዘጉበት ጊዜ ድረስ የንግድና ሌሎች ማኅበራዊ እንቅስቃሴዎችን እያስተናገዱ መቆየታቸው ይታወሳል። ሕጋዊ አሠራር ተበጅቶላቸው ዳግም ይከፈታሉ የተባሉት መስመሮቹ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ በኩል የቅድመ ዝግጅት ተግባራት እየተከወኑ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።
በተለይም በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል ዛላምበሳ፣ ራማ እና ሑመራ የንግድ እንቅስቃሴውን ሕጋዊ የሚያደርጉ የጉምሩክ ጣብያዎች መቋቋማቸውን በጉምሩክ ኮሚሽን የመቐለ ቅርንጫፍ አስተባባሪ አቶ ምሕረትአብ ገብረመድህን ለዶቼ ቬለ DW ገልፀዋል። የጉምሩክ ጣብያዎቹ በተቋቋሙበት አካባቢ ከሁለት ወር በፊት ጀምሮ ዝግጅት ሲደረግ መቆየቱ የገለፁልን ጣብያዎቹ በተቋቋሙበት አካባቢ የሚኖሩ የአካባቢው ሰዎች በአሁኑ ወቅት የፌደራል ፖሊስ አባላትም በስፍራው እንደሚገኙ ተነናግረዋል። የድንበር መንገዶቹ መቼ ይከፈታሉ ለሚለው የሕዝብ ጥያቄ ይፋዊ ምላሽ ባይሰጥም አሁን እየተደረገ ካለው ዝግጅት አኳያ በቅርቡ ይከፈታል የሚል ተስፋ በድንበር አካባቢ ነዋሪዎች ዘንድ አለ።
► መረጃ ፎረም – JOIN US