May 13, 2019

(ኤፍ.ቢ.ሲ)
በትግራይ ክልል በአይነቱ ልዩ የሆነ ነዳጅ መኖሩ በጥናት መረጋገጡን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ደብረጺዮን ገብረሚካኤል ገለጹ።ዶክተር ደብረፂዮን ይህንን ያሉት በዛሬው ዕለት በመቐለ ኢንዱስትሪ ፓርክ በሚገኘው ኬይ ፒ አር የተሰኘውን የህንድ ኩባንያ የምርቃት ስነ ስርዓት ላይ ነው።ኩባንያው በ2 ነጥብ 5 ሚሊየን መነሻ ካፒታል በኢንዱስትሪ ፓርኩ በጨርቃ ጨርቅ እና አልባሳት ምርት የተሰማራ ነው።

እስካሁንም በሁለት ዙር ብቻ ከ200 ሺህ በላይ አልባሳትን ወደ ውጪ የላከ ሲሆን፥ ከ700 በላይ ለሚሆኑ ወጣቶችም የስራ እድል መፍጠሩ ተገልጿል።በምርቃት ስነ ስርዓቱ የተገኙት ዶክተር ደብረጺዮን ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፥ ኩባንያው ሀገሪቱ ለያዘችው የኢንዱስትሪ ሽግግር የጎላ አስተዋፅኦ ያለው መሆኑን ጠቁመዋል።ዶክተር ደብረጺዮን አያይዘውም፥ በትግራይ ክልል እምባ አላጀ፣ ነበለት እና ዓዲ-ግራት ባሉት ተራራማ አካባቢዎች በአይነቱ ልዩ የሆነ ነዳጅ መኖሩ በጥናት ተረጋግጧል ብለዋል።
ይህም በአካባቢው የሚገኙ ድንጋይና አለቶችን ሰባብሮ በማቅለጥ የሚገኝ መሆኑን ነው የተናገሩት።የተፈጥሮ ሃብቱን ጥቅም ላይ ለማዋልም ግዙፍ ኢንቨስትመንት የሚጠይቅ መሆኑን ነው የጠቁሙት።ስለሆነም በቀጣይ አቅም ያላቸው አለም አቀፋዊ ኩባንያዎችና ባለሃብቶችን በዘርፉ በማሰማራት የተፈጥሮ ሃብቱ ጥቅም ላይ እንዲውል ጥረት እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል።በምርቃት ስነ ስርዓቱ ዶክተር ደብረጺዮንን ጨምሮ የዓለም አቀፍ የንግድ ዳይሬክተር እና ሌሎች ተጋባዥ አምባሳደሮች ተገኝተዋል።