
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በሺዎች የሚቆጠሩ “ህገወጥ ቤቶችን” ከሁለት ሳምንት በኋላ እንደሚያፈርስ መግለፁን ተከትሎ የአዲስ አበባ ባለአደራ ምክር ቤት ዛሬ ባደረገው ስብሰባ እንቅስቃሴውን ኮንኖታል።
ከ30 ሺ በላይ ቤተሰቦች የሚኖሩባቸው ቤቶች በምን ሁኔታ እንደተገነቡ፤ መቼ እንደተገነቡና በወቅቱ የከተማው አስተዳደር ለምን ኃላፊነታቸውን እንዳልተወጡ ለህዝብ መረጃ ሳይቀርብ ማፍረሱ ዜጎችን ከሰላማዊ ኑሯቸው ማፈናቀል፣ የዘፈቀደ አካሄድና በአስተዳደሩም ላይ ጥያቄ የሚያስከትል ነው ብሏል።
“በምርጫ እሸነፋለሁ” በሚል ስጋት ውስጥ ያለ ጊዜያዊ አስተዳደር መሆኑን ግምት ውስጥ በማስገባት ፣ ይህ እንቅስቃሴ ሕጋዊ ሽፋንን የተላበሰ መንግስታዊ የመሬት ወረራ ሆኖ አግኝተነዋል” በሚል መግለጫው አትቷል።
• “በሰላማዊ ትግል እስከመጨረሻው በፅናት እንታገላለን” እስክንድር ነጋ
• ”አዲስ አበባ የሁላችንም ከተማ ናት” ከንቲባ ታከለ ኡማ
ባለአደራ ምክር ቤቱ ከተማዋ ውስጥ ህገወጥነት መስፋፋት እንደሌለበት ቢያምንም ነዋሪዎች የመኖሪያ ቤት የማግኘት ፍላጎታቸው ሊሟላ ይገባል በሚለው መግለጫው ቤቶቹ የሚፈርስበት ወቅቱ ክረምት መሆኑም ተቀባይነት እንደሌለው ገልጿል።
“ጊዜያዊ አስተዳደሩ እንደሚለው ቤቶቹ ሕገ ወጥ ናቸው ቢባል እንኳን፣ ዓመቱን ሙሉ ጠብቆ የክረምት ወቅት መባቻ ላይ ስናስገባ”አፈርሳለሁ” ብሎ መነሳቱ ፍጽሞ ሰብአዊነት እና ኃላፊነት የጎደለው አፈጻጸም ሆኖ አግኝተነዋል፡፡” ብሏል።
አስተዳደሩ በጊዜያዊነትና እና በቋሚነት የመፍትሄ አቅጣጫዎች ባለማስቀመጡ ዜጎች ተፈናቅለው በየጎዳናው ላይ የሚጥላቸው ሁኔታም እንደሚፈጠርም አሳስቧል።
በተጨማሪም ምክር ቤቱ በመግለጫው አስተዳደሩ ሊያደርጋቸው ይገባል የሚላቸውን የመፍትሄ ሃሳቦች ጠቁሟል።
• ጠበቃ ሔኖክ አክሊሉና ሚካኤል መላክ እንዲለቀቁ አምነስቲ ጠየቀ
የኃገሪቱ ህገመንግሥትም ሆነ ኢትዮጵያ የፈረመቻቸው አለም አቀፍ ህግጋት እንዲከበሩ በሚደነግገው መሰረት ቤቶች ከመፍረሳቸው በፊት ዜጎች መጠለያ የማግኘት መብታቸው እንዲከበርና፤ አስተዳደሩ አዳዲስ ህገወጥ ቤቶች እንዳይሰሩ በመከላከልና ህግጋቱን እያከበሩ እስከቀጣዩ ምርጫ ባለበት እንዲቆዩ የሚል ምክረ ኃሳብ ይዟል።
እነዚህ ምክረ ኃሳቦች ተግባራዊ ካልሆኑ ግን ወደ ሰላማዊ እንቅስቃሴ እንደሚገባ አስታውቋል።