May 31, 2019
Source: https://ethiothinkthank.com/2019/05/31/development-bank-of-ethiopia-is-keeping-the-legacy-of-tplf/
አብይያችን ችግኝ ይተክላል! ባንካችን ደን ያስጨፈጭፋል!




ላለፉት አመታት የህወሓት ካድሬዎች ከልማት ባንክ ኃላፊዎች እና የጋምቤላ ክልል መስተዳደር ጋር በመመሳጠር የክልሉን 65% የሚጠጋ መሬት መዝረፋቸው፣ 9.3 ቢሊዮን ብር ብድር በመውሰድ መቀሌ ላይ ፎቆ መስራታቸው፣ በጋምቤላ ክልል በሚገኘው የተፈጥሮ ደን ላይ ከፍተኛ ጭፍጨፋ መፈፀማቸው ይታወሳል። በተለይ ከደን ጭፍጨፋ ጋር በተያያዘ የህንድ ሀገር ኩባንያዎች ተሳታፊ እንደነበሩ ይታወቃል። የዶ/ር አብይ አመራር ወደ ስልጣን ከመጣ በኋላም ችግሩ ተደፋፍኖ የቀረ ይመስላል። አሁንም በተግባር እየተደረገ ያለው ግን ሌላ ነው።በጋምቤላ ክልል በሻይ ልማት የኢንቨስትመንት ፍቃድ አውጥተው ከተሰማሩ ድርጅቶች ውስጥ ቨርዳንታ ሀርቨስት ፒ.ኤል.ሲ የተባለው የህንድ ኩባንያ አንዱ ነው። የኢትዮጵያ ሆርቲካልቸርና ግብርና ኢንቨስትመንት ባለስልጣን መስከረም 10/2011 ዓ.ም በፃፈው ደብዳቤ የቨርዳንታ ሀርቨስት ፒ.ኤል.ሲ የሻይ ልማት እስካሁን ያለውን የሥራ አፈፃፀም፣ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና አከባቢያዊ ፋይዳ ዙሪያ የሰራውን የዳሰሳ ጥናት ሪፖርት ለኢፌዲሪ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ማቅረቡን ገልጿል። በዚህ ሪፖርት መሰረት፤
- 1ኛ) ለቨርዳንታ ሀርቨስት የሻይ ልማት የመሬት ዝግጅትና ማስተላለፍ ሂደቱ በተለያየ ደረጃ የሚገኙ የመንግስት አካላትን እና የአከባቢውን ማህብረሰብ ስምምነት እና ተሳትፎ ሳይኖረው በወቅቱ በነበሩ የተወሰኑ የፌደራሉ መንግስት ባለስልጣናት ጫና እና ትዕዛዝ የተሰጠ መሆኑን፣
- 2ኛ) ቨርዳንታ ሀርቨስት ሚያዚያ 17/2003 ዓ.ም ባወጣው በ50 አመት ሊዝ ከወሰደው 3012 ሄክታር መሬት በ7 አመት ውስጥ የቦታውን 75% ለማልማት የተስማማ ቢሆንም እስከ 2011 ዓ.ም መጀመሪያ ድረስ ለድርጅቱ ከተላለፈው መሬት ውስጥ 81.4% (2452 ሄክታር) የሚሆነው መሬት ያለማ በመሆኑ፣
- 3ኛ) ፕሮጀክቱ ለአከባቢው ማህብረሰብ የሥራ እድል ከመፍጠር ይልቅ ሰራተኞችን ከህንድ ሀገር እንደሚያመጣ፣ እንዲሁም እነዚህ የውጪ ሀገር ሰራተኞች ከደሞዛቸው ግብር እንደማይከፍሉ፣
- 4ኛ) ኩባንያው በአከባቢው የሚገኘውን የተፈጥሮ ደን በመጨፍጨፍ በምትኩ ባህር ዛፍ እንደሚተክል፣ በዚህም የተፈጥሮ ደኑን ከመጨፍጨፉ በተጨማሪ የባህር ዛፍ ተክሉ ከጭፍጨፋ የተረፈውን ደን እንደሚያጠፋ፣… እና ሌሎች ተያያዥ ምክንያቶችን በመጥቀስ የቨርዳንታ ሀርቨስት በአከባቢው የተፈጥሮ ሀብትና ማህብረሰብ ላይ እያደረሰ ያለው ጉዳት ሊገታ እንሚገባ ገልጿል።



ይሁን እንጂ የልማት ባንክ ፕረዜዳንት እና አንዳንድ የክልሉ ባለስልጣናት ከቨርዳንታ ሀርቨስት ኃላፊዎች ጋር ያልተገባ የጥቅም ትስስር በመፍጠር ድርጅቱ በአከባቢው የተፈጥሮ ሀብትና ማህብረሰብ ላይ እያደረሰ ያለውን ጉዳት እንዲቀጥል ፈቅደዋል። ይህ በሀገርና ህዝብ ላይ የሚፈፀምን በደልና ግፍ የተቃወሙ የልማት ባንክ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ከሥራቸው እንዲታገዱ ተደርጓል። ከዚህ ቀደም ከህወሓት ካድሬዎች ጋር በመመሳጠር በጋምቤላ ክልል መሬትና የተፈጥሮ ሃብት፣ እንዲሁም 9.3 ቢሊዮን ብር የሚደርስ የሀገር ሃብት ሙጥጥ አድርገው መዘረፉ ሳያንስ አሁን ያሉት ልማት ባንክ ፕረዜዳንት የቀድሞውን የዘረፋ ሌጋሲ ለማስቀጠል ጥረት እያደረጉ ነው። ለዚህ ደግሞ ለሀገርና ህዝብ፣ እንዲሁም ለህሊና እና ሙያቸው ታማኝ የሆኑ የልማት ባንክ ሰራተኞች ላይ ግፍና በደል እየፈጸሙ ነው።ከላይ በተጠቀሰው መሰረት የልማት ባንክ ፕረዜዳንት እና የቨርዳንታ ሀርቨስት ኩባንያ በፈጠሩት የጥቅም ትስስር አማካኝነት ድርጅቱ ተጨማሪ የደን ጭፍጨፋ እንዳይፈጽም፣ እንዲሁም በአከባቢው በሚገኘው የተፈጥሮ ደን ሃብት ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያደርሰው ባህር ዛፍ እንዳይተከል፣ ከዚያ ይልቅ ለሻይ ማጠውለግ የሚያስፈልገው ባህር ዛፍን ከአከባቢው ነዋሪዎች አንዲገዛ ከኢትዮጵያ ሆርቲካልቸርና ግብርና ኢንቨስትመንት ባለስልጣን፣ ከጋምቤላ ክልላዊ መስተዳደር፣ እንዲሁም ፕሮጀክቱ የሚገኝበት ዞን እና ወረዳ የሰጡትን መመሪያ በመተላለፍ ይህ የጥፋት ፕሮጀክት እንዲቀጥል ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉ።ይህን እኩይ ተግባር ከተቃወሙ የልማት ባንክ አመራሮች አንዱ አቶ ተክሌ ዘውዴ ናቸው። አቶ ተክሌ የ30 አመት ልምድ ያካበተ ሰራተኛ ሲሆን በየአመቱ የላቀ ብቃትና አፈፃፀም በማሳየት ረገድ በአረዓያነት የሚጠቀስ እንደሆነ የሥራ ባልደረቦቹ ምስክርነት ይሰጣሉ። ይህ ትጉህ ሰራተኛ የህወሓትን ሌጋሲ ለማስቀጠል የሚጥሩትን የባንኩን ፕረዜዳንት ፊት ለፊት ሙግት በመግጠሙ በድን ጭፍጨፋ ለተሰማራው የህንድ ኩባንያ ተጨማሪ ብድር ሊሰጠው አይገባም ብሎ በመከራከሩ ምክንያት ከታች ባለው የእብሪት ደብዳቤ ከሥራው ታግዷል፡፡ በጥቅሉ ዶ/ር አብይ ችግኝ ይተክላል የልማት ባንኩ ፕረዜዳንት የጋምቤላ ተፈጥሯዊ ደን እንዲጨፈጨፍ ያደርጋል፡፡Filed in:Uncategorized