Source: https://mereja.com/amharic/v2/123209
በጋዜጠኛና የሰብአዊ መብት ተሟጋች እስክንድር ነጋ ላይ የሚደርሰው ወከባ እንዲቆም አምነስቲ ጠየቀ

አምነስቲ ኢንተርናሽናል የተሰኘው ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋም በጋዜጠኛና የሰብአዊ መብት ተሟጋች እስክንድር ነጋ ላይ የሚደረገው ወከና እንዲቆም በዛሬው ዕለት ባወጣው መግለጫ ጠይቋል።
“ሰናይ መልቲ ሚዲያ” የተሰኘ የቴሌቪዥን ጣቢያን ለማስተዋወቅና ስለ ሸር ሽያጭ መረጃ ለማድረስ ጋዜጣዊ መግለጫ ለመስጠት በሂልተን ሆቴል ጥሪ ተደርጎ የነበር ቢሆን በመንግስት አካላት ክልከላ እንደተደረገ አስተባባሪዎቹ ገልፀዋል። መግለጫ ለመስጠት ኪራይ ወደተከፈለበት አዳራሽ መግባት በመከልከሉ ጋዜጠኛና የሰብአዊ መብት ተሟጋች እስክንድር ነጋ ከሆቴሉ ውጭ ስለ ክልከላው ለጋዜጠኞች ማብራሪያ መስጠቱ ታውቋል።
ጣቢያውን ለማስተዋወቅ ሊሰጥ የነበረው የዛሬው መግለጫ ሲከለከል በሳምንት ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን ግንቦት 26/2011 ዓ/ም በተመሳሳይ በኢትዮጵያ ሆቴል መግለጫ ለመስጠት የተያዘው ፕሮግራም በመንግስት አካላት ትዕዛዝ መታገዱ ይታወሳል። ፖሊስ ጋዜጣዊ መግለጫውን የከለከለው ሆቴሉ ከደሕንነት አንፃር እንዳይካሄድ በመጠየቁ ነው ቢልም የሆቴሉ ኃላፊዎች “ከአቅማችን በላይ ነው” ብለው ጋዜጣዊ መግለጫው እንዳይካሄድ መጠየቃቸውን አዘጋጆቹ መግለፃቸው አይዘነጋም።
ጋዜጠኛና የሰብአዊ መብት ተሟጋች እስክንድር ነጋ ላይ እየደረሰ ያለው ወከባ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብቱን ለማፈንና ለማሸማቀቅ ያለመ መሆኑን የገለፀው አምነስቲ ሀሳቡን በመግለፁ ምክንያት የሚደርስበት ወከባ እንዲቆም ጠይቋል።