June 17, 2019

Source: https://www.zehabesha.com/amharic/archives/95695

ሰሞኑን ብርሀኑ ነጋን አስመልክቶ የሰጠሁትን አስተያየት በምላሽ አስተያየት ጎርፎ አየሁት፡፡ ይገርማል፡፡ ብዙዎቹ ምን እንደጻፍኩ እንኳን ያዩት አይመስለኝም፡፡ ችግሩ ያለው የብርሀኑ አምላኪነትና የብርሀኑ ጭፍን ጥላቻነት ላይ ነው፡፡ የእኔ ጉዳይ ደግሞ የሕዝብና የአገር እንጂ ብርሀኑ እንደግለሰብ አደለም፡፡ ብርኑ ብቻም ማለቴ ሳይሆን ማንንም ቢሆን በግል ጉዳይ አደለም የእኔ ትችትም ሆነ ድጋፍ፡፡ የአገሬ ልጆች በመሠረታዊ ነገር ላይ እንነጋገር፡፡ አስተውሉ! ይሄን የተረዱ በዙ ጀነሌ እያስከተሉ ትልልቅ የአገርና ሕዝብ ጥፋትን እያስከተሉ ነው፡፡ እባካችሁ የገበያ እቃ አትሁኑ፡፡ እኔ እንትና ፕሮፌሰር እንትና ዶ/ር ወይም ሌላ ሰዎች የሰጡት ማዕረግ ብዙም ክብደት አልሰጠውም፡፡ ከእነዚህ ሁሉ ረጋ ብሎ ትውልድን፣ አገርን፣ ሕዝብን ለመታደግ የበኩሉን ተግሳጽና ምክር የሚሰጥ ሽማግሌና አስተዋይ ሰው በብዙ ይበልጥብኛል፡፡ አገርን የመሩና ትልልቅ ሥራን የሰሩ የቀደሙ አባቶች ጥበብን በትምህርት ቤት ቀለም በመቁጠር አይገኝም፡፡ በፍልስፍና እና በትህትና እንጂ፡፡ የሆነ ሆኖ ብርሀኑንም ሆነ ሌላን ማምለክ አቁሙ፡፡ በጭፍኑም መጥላትን አቁሙ፡፡ ለሁሉም ምክነያት ይኑራችሁ፡፡ እነእንትና ስለደገፉት መደገፍ እነ እንትና ስለጠሉ መጥላት አደለም፡፡ አሁን እኮ ምድረ አክቲቪስት ነኝ ባይ እንደፈለገው እየቀደደ ሕዝቡን የንግድ እቃ እያደረገው ነው፡፡ ለአክቲቪስት ሼርና ላይክ ገበያ ነው እኮ እየሆነ ያለው ትውልዱ፡፡ በቀደም አንዱ በወስጥ ሔኖክ የሺጥላ እንዳለው ብሎ ለእኔ አስተያየት ሊሰጠኝ የሞከረም ነበር፡፡ ያሳዝናል እንግዲህ እንዲህ ያሉ ግለሰቦች ናቸው ትልቅ የእውቀት ቤት ሆነው አገር ምድሩ የአምልኮት ያህል የሚከተላቸው፡፡ እነጀዋር በግድ ከሳንፎርድ በፖለቲካ ሳይንስ ተመርቀናል ብለው በዓለም ላይ ዋና የፖለቲካ አማካሪ ነን ሲሉ አላፈሩም፡፡ ለእኔ ከሚጠቀስልኝ አንዱ የእንደዚህ ዓይነት ግለሰብ አባባል ነው፡፡ አዝናለሁ፡፡ አንዳንዶቻችሁ እዚህ የምጽፈው በከንቱ መስሏችሁ ከሆነ ተሳስታችኋል፡፡ የምጽፈው መጻፍም ሰውም ጠቅሼ አደለም፡፡ እኔ የፖለቲካ ሰው አደለሁም፡፡ ግን ነገሮችን የማስተዋሉ አቅሙ አለኝ፡፡ የምናገረው ደግሞ የአገርና ሕዝብ ጉዳይ እንጂ ሌላ ጉዳይ አደለም፡፡

ሰሞኑን የኢሳት ጉዳይ በብዙዎች ዘንድ ዋና አጀንዳ ነው፡፡ አሁን ለእኔ የኢሳት ጉዳይ ተራ የዛው ኢሳት የተባለው ቡድን አባላት ችግር እንጂ የአገርም የሕዝብም ችግር አደለም፡፡ ኢሳት ችግር እንዳለበት ቀደም ብዬ ስጠቁም እንዲሁ አሁን ብርሀኑን ስለነካሁ እንደተንጫጫው የጀሌ ብዛት ይንጫጫ ነበር፡፡ የሚገርመው ማን ምን ችግር እንዳለበት ለመጠቆም ሞክሬ ነበር፡፡ ሰው የሚከተለው በጅምላ የሚነዳውን ነው፡፡ በዛ ወቅት በግል ጓደኛ ለሆኑኝ ኢሳትን አስመልክቶ ኧረ ባካችሁ እያስተዋላችሁ ስል አንተ ሊሰሙኝ አለመቻል ብቻም ሳይሆን የወያኔ ደጋፊ ለማለት ሞክሯቸዋል፡፡ እኔ ወያኔንም ቢሆን የምጠላው በምክነያት እንጂ በትግሬነት አደለም፡፡ ዛሬ ላይ የገረመኝ እነዛ ሰዎች ዋና የኢሳትን አንጃ አንዱን ደጋፊ ሌላውን እርኩስ አድርገው አያለሁ፡፡ እኔን ግን ይሄ ያሁኑ የኢሳት ጉዳይ አይመለከተኝም፡፡ የእኔ ችግር ኢሳት ውስጥ የነበሩ ሰዎች በአገርና ሕዝብ ላይ የሚሰሩት ቁማር ስለነበር ነው፡፡ ኢሳት አደለም መከፈል ከእነችርሱ ቢጠፋ ኢትዮጵያ ተገላገለች እንጂ አትጎዳም፡፡ ከዚህ በፊት ስሰጣቸው የነበሩ አንዳንድ ጠንካራ ትችቶቼን ሳተናው ሳያወጣቸው እንደቀረ በዚሁ አጋጣሚ ሊጠቁም እፈልጋለሁ፡፡ ሆኖም ብዙ ሌሎች ጉዳዮች ላይ አስታክኬ የተቸሁባቸውን ጽሁፎቼን ሳተናው ስላወጣቸው ወደኋላ ካገኛችሁን አንብቡ፡፡ አሁን የኢሳት ጉዳይ የእኛ ጉዳይ አደለም፡፡ የሕዝብ ነው የምትሉ ከፈለጋችሁ የሕዝብ ስታደርጉት እንያችሁ፡፡ ኢሳትም ሆነ ኦኤም ኤን ወይም ሌላ ግን በኢትዮጵያና ሕዝቧ መከራ የሚነግዱ አደገኛ ተቋማት እንሆኑ ነው የማውቀው፡፡ ኢትዮጵያ ሙሉ በሙሉ ሠላም ብትሆን እነዚህ ሚዲያዎች እንደሚጠፉ አትጠራጠሩ፡፡

ሌላው ሰሞኑን ብዙ አስተያየት ስላየሁ አንዳንዱም ጥሩ ስላልሆና መደናገርን ስለሚፈጥር እስኪ ልመልስላችሁ፡፡ የረጅም ጊዜ የእኔን ጽሁፍ ረጋሚው ገመዳ እኔን በጻፍኩ ቁጥር መሳደቡ ያስቀኝ ነበር፡፡ ለአስቴር ጥሪ ምላሽ በጻፍኩት ላይ ግን ስለሰጠው አስተያየት ዝም ብዬ ማለፍ አልፈለኩም፡፡ ገመዳ ራሱን በጥላቻ እንደተመረዘ ግልጽ የሚያሳይ አስተያየት ስለሆነ፡፡ አስቴር ከሌሎች ጋር በፍቅር ስለኖረች ለገመዳ አስቴር ከምንም በላይ የተረገመች ሰው ነች፡፡እንግዲህ አስቴር ኦሮሞ ሆና ከሌሎች ጋር በፍቅር መኖሯ ነው ገመዳን ይሄን ያህል እብድ ያረገው፡፡ እንጂ አስቴር አንዳች ያጠፋቸው ጥፋት ኖሯት አደለም፡፡ ጥሪዋም ኦሮሞን በጭፍን አትጥሉ ብዙ ኦሮሞ ያልሆኑ ሆን ብለው ኦሮሞን እንዲጠላ እያደረጉ ናቸውና እባካችሁ በማለት ለኦሮሞ ቆመች እንጂ አንዳች ነቀፋ ያለበት ነገር አልተናገረችም፡፡ እንግዲህ ገመዳ የኦሮሞ የጥላቻና ዘረኝነት ፖለቲካ አብቅሎ ያሳደጋቸው አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ለገመዳ ግን ወደራስህ ተመለስ ነው የምለው፡፡ በብዙ ኦሮሞ ወጣትና የተማረው ከሌላ ጋር ትብብር ያለው ኦሮሞ እንደጠላት ነው የሚታየው፡፡ ይሄ እንግዲህ አደገኛ በሽታ ነው፡፡ ኦሮሞ ሲንድሮም መባል ተጀምሯል አሁንማ፡፡ ጥሩ አደለም አስቴርም እንዳለቸው ሕዝቡን ሁሉ በኦሮሞነት እንዲጠላ እያደረጉ ያሉ እንደነዚህ ያሉ በጥላቻና ዘረኝነት የተመረዙ ናቸው፡፡ ገመዳ የዚህ ልክፍት ተጠቂ ነው የሆነው እንግዲህ፡፡

ሌላው እዚሁ አስቴር አስመልከቶ የጻፍኩት ላይ የአስቴርን አባት ለመጻፍ ጉራማይሌ መጠቀም ግድ የሆነብኝ የግዕዝ ሶፍት ዌር dha()ስሌለው ነው ያልኩትን አንዳንዶች አለ ብለው እንደሚያውቁት አድርገው የጻፉት ስህተት ሆኖ ስለተሰማኝ ፊደሉ ከእነሙሉ ርቢው የሚከተለውን ይመስላል፡፡ እንግዲህ እነ ጳ ወይም አንደ ጰ አናቱ ላይ ያለው ደ ሆኖ በግዕዝ ሶፍት ዌር ቀርቦ ከሆነ አላውቅም፡፡ ከሆነ ስህተት ይመስለኛል፡፡ ለማንኛውም ፊደሉን ለማታውቁ የሚከተለው ነው፡፡ አያሳስትም ራሱን የቻለ ነው፡፡  ስህተት ማረም ስላለብኝ ነው ዛሬ፡፡ ነገ ደግሞ ሌላው የተሳሳተ መረጃ ይዞ አዋቂ እንዳይሆን ጭምር፡፡

ሌላው ያው አንዳንዶች ብዙ እንደምታውቁ ለማሳየት ይሁን ወይስ ሌላ ባይገባኝም የምትጽፉ ነገር ያስቃል፡፡ አንዱ ዲሞክራሲን የቃል ትንታኔ ሊሰጠኝ ሞከረ፡፡ እኔ ሲጀምር ስለዲሞክራሲ ያብራራሁት ነገር የለም፡፡ በዚሁ ስለብርሀኑ በጻፍኩት ላይ ነው፡፡ ራይት የተባለ አስተያየት ሰጪ ነው፡፡ ሲጀምር ራይት በትምሀርት እንኳን ትንሽ ፈቀቅ ያለ አይመስለኝም፡፡ ምክነያቱም በግሪክ ዲሞክራሲ ማለትን ዛሬ የስድስተኛ ክፍልም ተማሪ ሊያውቀው ይችላልና፡፡ ዲሞ ማለት ደግሞ በግሪክ ሕዝብ ማለት እንጂ ራየት ዲ ማለት አፍራሽ ነው እንዳለው አደለም፡፡ በግሪክ ዲ መባሉንም አላውቅም፡፡ ምን አልባት በላቲን እንደዛ ነው፡፡ ለማንኛውም የግሪኩ ዲሞክራሲ የሕዝብ አገዛዝ ማለት ነው፡፡ ክራሲ ማለት አገዛዝ ማለት ነውና፡፡ ዲሞግራፊ ማለት የሕዝብ ቁጥር እንደማለት ነው (ግራፊ የሚለው ቃል ግን ብዙ ጊዜ ከማሳየት ጋር የተያያዘ ነው)፡፡ እኔም የቋንቋ ሰው አደለሁም፡፡ ለማንኛውም ራይትና መሠሎች አጣሩ አሁን እንግዲህ ይሄን ተቀብሎ ነገ አንዱ አክቲቪስት የዲሞክራሲ ተንታኝ እንዳይሆን ነው፡፡

ዛሬ ስለሌላ ጉዳይ ብዙ የምለው የለኝም አብይ ደሴ ሄዶ አንድም ኦሮሞ በፊት ከነበረው ቁጥር በላይ ስልጣን ላይ ጨምሮ ከሆነ ሥልጣኔን እለቃለሁ ያላት ንግግሩ ግን አልተመቸችኝም፡፡ ለመንቀፍ ብዬ አደለም፡፡ ጉዳዩ የቁጥር ጉዳይም አደለም፡፡ አጠቃላይ የሚኒስቴር መሥራቤቶች ሁኔታ በራሱ ልክ ያልሆነ ነገር አለበት፡፡ አንዳንድ ቦታ ግን ግልጽ የሆነ የአንድ ብሄረሰብ መስሪያቤት እስከሚመስል የተደረገበት አለ፡፡ እያልን ያለንው የኮታ ጉዳይ አደልም፡፡ ሰዎች በምንም መለኪያ በማንነታቸው ስልጣን መያዝ የለባቸውም፡፡ በቂ አማራ ሊያውም ጥራት ባለው ቦታ መዲቤያለሁ የሚለው ንግግር ጥሩ አደለም፡፡ በአማራነት፣ ኦሮሞነት በሌላም በኮታ አይሁን እኮ ነው እያልን ያለንው፡፡ መስራቤቶች ሙሉ መዋቅራቸው ኢትዮጵያዊ ይሁን ነው እያልን ያለንው፡፡ የገቢዎችን መዋቅር ከላይ ከሚኒስቴሯ እስከ ታች ያለው ሰንሰለት ኃላፋችን በኦሮሞ የሳይንስና ቴክኖሎጂን በአማራ አይነት አደልም የፈለግንው፡፡ የንግድ ባንክን ሙሉ ሥራ አስፈጻሚ በኦሮሞ የብሔራዊ ባንክን በአማራ አደለም እያልን ያለነው፡፡ ሲሆንስ ከአለን የከፋ ችግር አንጻር በአጋጣሚ በችሎታም ከአንድ ብሄር የሆነ መስሪያ ቤት በዝቶ ከታየ ሆን ብሎ መበወዝን ይጠይቃል አሁን ግን ያለው እውነት ሆን ብሎ ማንነትን መሠረት በማድረግ መመደብ ነው፡፡ አዲስ አበባ ላይ ያለው በቀጥታ በኦሮሞነት የተመደቡ ብዙ አሉ፡፡ ነውሩ እኮ ይሄ ነው፡፡ ሰሞኑን አዲስ አበባ ስላለ የዝርፊያ ችግር የኦሮሚያ፣ የአዲስ አበባና ፌደራል ፖሊስ የሚል ወሬ እሰማለሁ፡፡ የኦሮሚያ ፖሊስ አዲስ አበባ ላይ ምን አገባው? ሲጀምር የአዲስ አበባ ፖሊስ በቂ ነው፡፡ ከዛ ካለፈ ፌደራሉ አለ፡፡ ይሄ አዲስ አበባ ላይ የሚደረግ የኦሮሚያ ጣልቃ ገብነት እስካላቆመ ድረስ ችግሮች እየተባባሱ እንደሚሄዱ አትጠራጠሩ፡፡ አብይ ማክበር ያልፈለገው አዲስ አበባ ራሱን የቻለ አስተዳደር ነው የሚለውን ነው፡፡ አዲስ አበባን በኦሮሞነት ሊያስተዳድሩት ይፈልጋሉ፡፡ አደገኛ ስህተት እየተሰራ ነው፡፡ ባለፈው የሆነ ጋዜጠኛ ከአዲስ አበባ የኦሮሚያ ፖሊስ እንዳሰረ ሲነገር ነበር፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ እንዲህ ማንም እንደፈለገ የሚፈነጭበት እየተደረገና ራሱ የመንግስት መዋቅር የሆነው ሥርዓት አለባ ሆኖ ሥርዓት ማስከበር አይቻልም፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የኦሮሚያ ፖሊስ በአዲስ አበባ ውስጥ ሊንቀሳቀስ አይገባውም፡፡ አዲስ አበባ ከኦሮሚያ እንደመዋሰኑ በወሰን አካባቢዎች ትብብር አይደረግ ማለት አደለም፡፡ ግን ውስጥ ባለ የአዲስ አበባ ጉዳይ በመጀመሪያ የሚመለከተው የአዲስ አበባ ፖሊስ ነው፡፡ የፌደራል ፖሊስ የትም ቦታ እንደሚያደርገው ሊያግዝ ይችላል፡፡ የኦሮሚያ ፖሊስ የምትለዋ ቁማር አሁንም ችግር አለባት፡፡

ሌላው ይቺ የሞቅታና የስሜት ቀስቃሽ የአስመሳይነት እንቅስቃሴ ካልቆመ አገር እንደ አገር አትመራም፡፡ ቁርጠኝነት፣ ለሕዝብ ታማኝነት የአመራር ብቃት ይጠይቃል፡፡ ሕዝብን በቅንነትና በታማኝነት ማገልገልና የራስንም ክብር መጠበቅ ሲቻል የዘሬን ብተው ይመንዝረኝ እንደተባለው በሴራ ካልሆነ የሚሳካ ሆኖ የማይሰማቸው ስለበዙ ችግሮችን በራሳቸው ጭምር እያመጡ ነው፡፡ እነ አብይ መጀመሪያ በሕዝብ ዘንድ የነበራቸውን አቀባበል አክብረውትና ታምነውለነት ቢሆን ዛሬ የት በደረሱ፡፡ አብይ ፖል ካጋሜ ጋር ብዙ ጊዜ ተገናኝቷል፡፡ ፖል ልምዱን ሳይነግረው አልቀረም፡፡ አብይና ፖል የማይመሳሰሉት ግን ፖል የአገርና ሕዝብ ቁጭትና እልሕ ስለነበረው ቁርጠኛ ነበር፡፡ አብይን ከኢትዮጵያዊ የመሪ ቁርጠኝነት የሚጎትቱት ብዙ ነገሮች አሉበት፡፡ የግሉ ችግሮች ማለቴ ነው ሌሎች የሚያሳርፉበት ጫና ሊኖር ይችላል፡፡

ሰሞኑን የሰማሁት ሌላው የመኢኣድ በአዲስ አበባ ሊፈርሱ በተወሰነባቸው ቤቶች ላይ ያወጣው መግለጫ ነው፡፡ የት ነበር ግን እስከዛሬ? እስክንድር በግል ይሄን ሁሉ ሲታገል አንድም የፖለቲካ ቡድን ከሕዝብ ጎን አልታየም ነበር፡፡ እነ ብርሀኑ ግልጽ ሆነዋል ባለፈው እንደተናገርኩት ነው፡፡ ሌሎችስ ተፎካካሪ ነን የሚሉ የት ናቸው? ለማንኛውም ሕዝባና አገር ባጣ ቆየኝ አደለም!

የአገሬ ልጆች  የአስበሳዮች መጠቀሚያና መነገጃ አትሁኔ፡፡ ያለምክነያት ሌሎችን ተከትላችሁ አትጥሉ አታጅቡ፡፡ አገርና ሕዝብን ማሰብን ሁል ጊዜ ተቀዳሚ ማስተዋላችሁ ይሁን!

ልዑል እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይባርክ! አሜን!

ሰርፀ ደስታ