BBC Amharic : ፀደቀ ይሁኔ ወልዱ (ኢንጂነር ) የፍሊንት ስቶን ኢንጂነሪንግ መስራችና ባለ አክሲዮን ናቸው። በዚህ ዓመትም በ29 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ያስገነቡትና በአባታቸው ስም የሰየሙት አዳሪ ትምህርት ቤት በደሴ ሥራውን ጀምሯል። በቅርቡም “ሾተል” የሚል መጽሐፍ ለንባብ አብቅተዋል። በመጽሐፉና በሙያቸው ዙሪያ ከቢቢሲ ጋር ቆይታ አድርገዋል።
መጽሐፍዎት ምን ላይ የሚያተኩር ነው?
ፀደቀ ይሁኔ፦ የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ ላይ ነው የፃፍኩት። የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ ባለ ሁለት ስለት ቢላ ነው። በአግባቡ ካልተያዘ በአንድ በኩል ሰውን ይጎዳል በአንድ በኩል ሊያለማ ይችላል የሚል ነገር ነው ያለው። በመጽሐፉ ውስጥ አምስቱ ቁልፍ ችግሮቻች ያልኳቸው የከተማ ልማት፣ ኮንስትራክሽን፣ ንግድ፣ ትራንስፖርት እና ፋይናንስን በሚገባ ለማየት ሞክሬያለሁ።
አሁን ያለነው ሁለተኛው የእድገት እና የትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ ነው። ይህ የሁለተኛው እድገትና ትራንስፎርሜሽን ምርመራ ያስፈልገዋል በማለት ለመፃፍ የተነሱት መቼ ነው?
ፀደቀ ይሁኔ፦ መጀመሪያ ላይ ያሰብኩት በበራሪ ወረቀት መልኩ ሀሳቤን ለማካፈል ነበር። ከተማ ልማት፣ ኮንስትራክሽን፣ ንግድ፣ ትራንስፖርትና ፋይናንስ እነዚህን አምስቱ ጉዳዮችን በማንሳት ውይይት እናድርግ በሚል ለሀገሪቱ ከፍተኛ አመራሮች በኢሜል እየላኩ ብቆይም ብዙም ሀሳቤን አልቀለቡትም።
ከዚያ ግራ ተጋባሁ፤ በኋላ ላይ ደግሞ አንድ ሰው ሌሎቹንም ጨምራቸው ሲለኝ ኢንዱስትሪንና ግብርናን ጨምሬ እንደገና ላኩላቸው። በዚህ ሂደት ላይ እያለሁ ነው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የመጡት።
እርሳቸው እንደተመረጡ የእድገትና የትራንስፎርሜሽኑ ግምገማ ህዝባዊ መድረኮች መካሄድ ጀመሩ። ሕዝባዊ መድረኮቹ ላይ ህዝቡ የሚያነሳቸውና አመራሩ የሚረዳበት መንገድ አልገጠመልኝም።
ሕብረተሰቡ እሮሮውን በግልፅ ነው የሚያስረዳው። አመራሩ ግን በእሮሮ ውስጥ ችግሮቹንና መፍትሄዎቹን የመቅለብ አቅሙ ዝቅተኛ ሆነብኝ። እና አሁንም ሌላ ጠበብ ያለ መድረክ እናዘጋጅ ብዬ ፋና ብሮድካስቲንግና ብሔራዊ የፕላን ኮሚሽን አንድ ላይ ሆነው እኔ ትንሽ እገዛ አድርጌ የዛሬ ዓመት ገደማ አንድ መድረክ አዘጋጀን።
እዚያ መድረክ ላይም የተነሱት ነገሮችን ስመለከታቸው ብዙ ሰው የታየው ነገር የለም። ስለዚህ ይህንን ነገር በደንብ ባየው ይሻላል በማለት ትንሽ ጽፌበት በመጽሀፍ መልክ ቀላል መረዳት (ኮመን ሴንስ) የሚጠይቁትን ነገሮች ባሰፍር፤ በዚህ በለውጥ ወቅት ብዙ ሰው ትራንስፎርሜሽንን ተገንዝቦ አዲሱን የለውጥ አመራር ያግዛል ብዬ በዚያ መልክ ጀመርኩት።
በኋላ ግን ሳየው፤ መረጃዎችን ስሰበስብ ውስጡ ብዙ ችግሮች አሉት። እና ይኼ በ100 ገፅ በራሪ ወረቀት ሊሆን አይችልም አልኩ። ምክንያቱም ፋይናንስ ብቻ 200 ገፅ ሆነብኝ። ለዚያውም ቆራርጨው ነው አንጂ የሰራሁት አጠቃላይ ወደ 800 ገፅ ነበር። ከዚያ ለሕትመት እንዲሆን በማለት ወደ 500 ገጽ አሳጠርኩት።
የኢህአዴግ አብዮታዊ ዲሞክራሲ መስመር ህፀጾች አሉበት። በነፃነትና በእኩልነት የሚያምን ድርጅት ነፃነትና እኩልነትን አላራመደም። በገበያውና በፖለቲካ ውስጥ ነፃ ገበያንና ነፃ ፖለቲካን ዋና ምሰሶዎቼ ናቸው ብሎ የተነሳ ድርጅት ነፃ ገበያም አላካሄደም ነፃ ፖለቲካም አላካሄደም።
ገና በ97 ዓ.ም ነፃነት ፖለቲካው ላይ ትንሽ ብቅ ሲል ደነገጠና ዝግት አደረገው። ልክ የፖለቲካውን ነፃነት ሲዘጋው ነፃ ገበያውም በነፃ ፖለቲካው ማፈኛ ሥርዓት ነፃ ገበያውን የሚቆጣጠሩ ኃይሎች መጡና የነበረውን እንዳልነበር አደረጉት።
ያንን ነው በማስረጃ አስደግፌ ከንድፈ ሃሳባዊ መነሻ ጋር ለማየት የሞከርኩት።

ለምሳሌ የኢትዮጵያ መንግሥት ስለታይዋን በጣም ነው አድንቆ የሚያወራው። ታይዋን ማለት ግን የነዋሪውን ብዛት የቆዳውንም ስፋት ስታየው ከአዲስ አበባ የማይተልቅ ኢኮኖሚ ያላት ሀገር ነች። በዚህ ብዝኀነት በበዛበት ሀገር የታይዋንን ሞዴል እጭናለሁ ማለት ከዲሞክራሲ ጋር የሚሄድ አይደለም። ማነሷ ብቻ አይደለም መሪዎቿ የደሴቲቱን ነዋሪዎች እንደ ሁለተኛ ዜጋ ጨቁነው ያሳደጓት ሀገር ናት።
እንደዛ ተጨቁኖ ሊያድግ የሚፈልግ የኢትዮጵያ ሕዝብ የለም። ጭቆናውን የሚፈቅድ ሕዝብ ባለበት የታይዋን ሞዴል ሊሰራ ይችላል። ጭቆናውን የማይፈቅድ ማህበረሰብ ባለበት ግን መጀመሪያ ላይ የዛሬ 19 ዓመት መለስ ዜናዊ ዲሞክራሲ፣ ነፃ ገበያ አማራጭ ሳይሆን የሕልውና ጉዳይ ነው ብሎ ጽፎታል። መንገድም ግብም ነው ብሎ ነው የሚጀምረው።
ፈጣን እድገት ሁሉንም አሳታፊ የሆነ፣ ከተመፅዋችነትና ከፖሊሲ ተጽዕኖ የራቀ ብሎ ያስቀመጠ ድርጅት በኋላ ግን የሁሉም መጫወቻ ነው የሆነው። አሁን ያንን መመለስ ይቻላል። የተጻፈ ነገር ስለሆነ ያንን ተከትሎ መሄድ ይቻላል። የሰው ሀሳብ ነው ገጣጥሜ የጻፍኩት የራሴ ሀሳብ የለበትም።
በእርስዎ ሀሳብ የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ መሬት ላይ ወርዷል? ስኬታማ ነበር?
ፀደቀ ይሁኔ፦ የመጀመሪያው አምስት ዓመት መለስ በሕይወት ስለነበር በደንብ ነው የሄደው። በተለይ ደግሞ እስከ 97 ዓ.ም ድረስ የነበረውን ነፃ አካሄድ ከዐዕቅዱም በፊት በድህነት ቅነሳ ስትራቴጂ ውስጥ ነበረው እንቅስቃሴ ውስጥ የነበረው ነፃ አስተሳሰብ መልሶ ማምጣት ይቻል ነበር። ያንን ማድረግ አልቻለም።
እንደሚመስለኝ ከ2002 በኋላ በጂቲፒ 2 የበለጠ ነፃ ፖለቲካና ኢኮኖሚ ለማካሄድ ታስቦ፣ እንኳን ከውጪ ነፃነት ሊኖር በዛው በኢህአዴግ ውስጥም ነፃ ወስጠ ድርጅት ዲሞክራሲ ጠፋ። በዚያ ዲሞክራሲ በጠፋበት ጊዜ ደግሞ ኃያል የሆኑ ሰዎች በፈቀዱት መንገድ መሩት።
ለሕዝብ ያልወገነ ሁሉም ለየራሱ የቆመበት አካሄድ ስለሆነ የሄደው መጨረሻው እንደምናየው ታሪክ ነው የሆነው። አንድ ቀን ያ እንዴት እንደሆነ ከእኔ የበለጠ የሚያውቁ ሰዎች መፃፋቸው አይቀርም።
አሁን ግን የታቀደው ምን ነበር? ወዴት ነው የምንሄደው? ካልክ ዘጠና በመቶ በሥራ ላይ የዋለው ህብረተሰብ 41 በመቶው ለራሱ ሥራ የፈጠረ ነው። 39 በመቶ በግብርና 11 በመቶው በግሉና በመንግሥት ተቀጥሮ ነው ያለው።
ብዙ ጊዜ የምንሟገተው በግሉና በመንግሥት ተቀጥሮ ስላለው 11 በመቶው ነው። 89 በመቶውን ሕብረተሰብ የሚያስተናግድ ሥራ ሳንሰራ፣ ስለእርሱ ሳናወራ ትራንስፎርሜሽን ማምጣት አንችልም። መጽሐፉ ውስጥ ዝርዝር ነገሮች ተቀምተዋል። ብዙ ስህተቶች ሊኖሩት ይችላሉ። የዓላማ ስህተት ግን እንደሌለው አረጋግጥልሀለው። ጂቲፒው ተመልሶ መስመር ውስጥ መግባት አለበት።
መንግሥት የተለያዩ የሕዝብ ንብረቶችን ወደ ግሉ ዘርፍ ለማዘዋወር እየተንቀሳቀሰ ነው፤ እርስዎ በዚህ እርምጃ ላይ ያለዎት አቋም ምንድን ነው?
ፀደቀ ይሁኔ፦ ልማት ምርጫ አይደለም። ልማታዊ መንግሥት ያልሆነ የለም። መንግሥት ነው ካልን ልማት አለ። ያልለማ ሀገር ላይ አለመልማት ጭራሽ የሚታሰብም ነገር አይደለም። ልማት ምን ጊዜም ቢሆን የፖለቲካ አጀንዳ ከመሆን አይቆምም፤ በበለፀጉት ሀገሮችም እንኳ ቢሆን።
ጥያቄው ልማትን ማን ያልማ የሚል ነው። መንግሥት ያልማ ወይስ የግሉ ዘርፍ። በእርሱም ደግሞ ሙግት የለም። መንግሥት ሊያለማ አይችልም። መንግሥት መሠረተ ልማት ነው የሚያለማው ሌላውን ነገር የግሉ ዘርፍ ያለማል።
ገንዘብን የሚያውቀው፣ ለገንዘብ የሚቆመው የግሉ ዘርፍ ነው። የሕዝብ ሀብት (ስቴት ካፒታል) በማን ስር ይሁን? ካፒታሉን ማን ይቆጣጠረው ቢባል፣ የስቴት ካፒታሉ ይብዛ ቢባል፣ እንደ አሜሪካ ግዙፍ ስቴት ካፒታል ያለበት ሀገር የለም።
በአሜሪካ በቢሊየን የሚቆጠሩ ሀብቶች የሚያንቀሳቅሰው ጦር ሠራዊቱ ያለው ኢንደስትሪ ነው፤ የወደብ አስተዳደሩ ትልቁ ነገራቸው ነው። ትራንስፖርት ዘርፉ እንዳለ የእነርሱ ነው። ስለዚህ ብዙ ካፒታል የስቴት ካፒተታል ነው አሁንም ቢሆን።
መንግሥት ካፒታል አይኑረው ከሆነ በሎሌነት ለሌሎች ሀገሮች ወይ ለሌሎች ካፒታሊስቶች እንደር ካልሆነ በስተቀር፤ በሀገር ጉዳይ ላይ ስቴት ካፒታል አይኑረን የሚል መንግሥት አይመጣም። ሊመጣም አይችልም። ቢመጣም አሁን ባለው የንቃተ ህሊና ደረጃ በአጭር ጊዜ ከሥልጣን ይወርዳል።
ዲሞክራሲ ስር ባልሰደደበት ሀገር ሁለት መንገድ ብቻ ነው ያለው። አንዱ ምንድን ነው የኢኮኖሚ ተሳታፊዎቹ ድንበር ዘለል ወደ ሆነ ወደ ድብቅ ኮንትሮባንድ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ውስጥ ይገቡና መንግሥትን ያንቁታል። ብር ሲያጣ ይወድቃል። ሌላው ኢኮኖሚውን ይተውና ኢኮኖሚ ውስጥ ያልተሳተፉ ሰዎች አማፂ ይሆናሉ። በዚህም ያፈርሱታል።
ዲሞክራሲ ስር ቢሰድ ኖሮ ግን በምርጫ ብቻ ነበር ከስልጣን የሚወርደው። አሁን ግን ዲሞክራሲው ስር ስላልሰደደ መጀመሪያ ዲሞክራሲውን ስር የማስያዝ ሥራ መስራት አለብን።
የመጀመሪያው የመንግሥት ሥራ ምን ልሽጥና ምን አልሽጥ ሳይሆን እንዴት አድርጌ ዲሞክራሲውን መሰረት ላስይዝ ነው መሆን ያለበት።
ለምሳሌ የአካባቢ ምርጫ 2010 ላይ መካሄድ ሲኖርበት አልተካሄደም። ስለዚህ ይህ ምርጫ 2012 ድረስ ዘግይቶ ከሀገራዊ ምርጫ ጋር የሚካሄድበት ምክንያት የለም። ድሮም ሕገ መንግሥቱ በአንድ ጊዜ የሕዝብ ሥርዓቱ አንዳይፈርስ ለማድረግ የአካባቢና ሀገራዊ ምርጫ የሚካሄዱበትን ነገሮች እንዲንገጫገጩ አድርጓቸዋል።
ስለዚህ መጀመሪያ በአካባቢ ምርጫ መሰረት ላይ የቆሙ ክልሎችና አካባቢዎች መኖር አለባቸው። ያ ሕዝባዊ ተቋም በአግባቡ ሳይቆም ሀገራዊ ምርጫ ማካሄድም አይቻልም።
ድርጅቶቹን የሚገዙትስ ቢሆኑ በድርድር ሰዓት ቀጣይነት በሌለው መንግሥት ምንድን ነው የሚደራደሩት? የአንድ ነገር እሴት እኮ የረዥም ግዜ ትርፉ ነው። ስለዚህ የሚቀጥለው ምርጫ ውጤቱ ምን እንደሆነ ሳያውቁ ምንድን ነው የሚገዙት?
ያለንን የሕዝብ ሀብት ወደ ግል ለማዘዋወር ብቻ ካልሆነ በስተቀር የምንሸጠው ውጤታማ የሆነ ዘርፍ ለማምጣት ከሆነ መጀመሪያ መደረግ ያለበት የመቀመጫዬን ነው።
መጀመሪያ ዲሞክራሲው መስፈን አለበት። በእርግጥ ዲሞክራሲ እስኪሰፍን ድረስ ተብሎ ስለ ኢኮኖሚው ሳይወራ አይቀርም። ግን ቢያንስ ቢያንስ የአካባቢ ምርጫ ተካሂዶ ህብረተሰቡ በራሱ ጉዳይ፣ በእለታዊ አጀንዳዎቹ የሚጠመድበትን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ምህዳር ማደላደል አለብን።
ያንን ሳናደርግ ቴሌንና መብራት ኃይልን መሸጥ የሚባለው ነገር አያስኬድም። እነዚህ አገልግሎቶች የሚተሳሳሩት ከወረዳና ከቀበሌዎች ከከተሞች ጋር ነው። የገበያ ሁኔታን ሳታረጋጋ ቴሌን የምትሸጥበት መንገድ ምንድን ነው? የገንዘብ፣ የኢኮኖሚም ሆነ የፖለቲካ ትርጉም አይሰጥም።
ከነበሩት አለመረጋጋቶች ጋር በተያያዘ የኮንስትራክሽን ዘርፉ መቀዛቀዝ ይታይበታል ይባላል፤ እርስዎ በዘርፉ ላይ እንደተሰማራ አንድ ግለሰብ ሁኔታውን እንዴት ነው የሚገመግሙት?
ፀደቀ ይሁኔ፦ እኔ ኮንስራክሽኑን የማየው እንደ ሁለት ነገሮች ነው። አንዱ ኪራይ (ሬንት) ነው። መሸሸጊያ ነው። የመንግሥት በጀት ላይ ጥገኛ ስለሆንን ከአንዱ ነጥቄ ወደ አንደኛው እንዴት ላምጣው በሚለው ሙግት ውስጥ ነው ያለነው።
ሁለተኛው ግን ማንኛውም ባለሀብት የሚበዘብዘው በምንድን ነው? ባለሀብት ማለት በዝባዥ ማለት ነው፣ ሳትበዘብዝ ካፒታል አታጠራቅምም (ሳቅ)። የሚበዘበዘው ጉልበት ነው። የሚበዘበዝ ጉልበት በጣም በብዛት ያለው ደግሞ ገጠር ውስጥ ነው።
የገጠሩ አርሶ አደር የገፋውን አምራች ኃይል ሥራ ፍለጋ መንገድ ላይ ይቆማል። ከዚያ ደግሞ አልፎ ወደ ከተማ ይመጣል። ስለዚህ ኮንስትራክሽን ላይ ይህ የሰው ኃይል ነው ያለው።
ለሰራተኛው ደህንነት ግድ ሳይሰጠን ከፎቅ ላይ ሰው እየፈጠፈጥን፣ ሚስማር አየወጋው፣ ከተገቢው በታች እየከፈልነው ነው የምናተርፈው። ስለዚህ ይኼ ከአርሶ አደሩ በተበዘበዘ ገንዘብ በመንግሥት በጀት ጥገኛ የሆነ ዘርፍን እንዴት እናስተካከለው የሚለው ነው የመጀመሪያ ጥያቄ።
የትኛውም መንግሥት ቢመጣ ይኼንን ሳያስተካክል የመንግሥት ግዢ ስላለበት፤ መንግሥት የመሰረተ ልማት ግዢ ውስጥ ያለውን ግፍና ሌብነት ሳያስተካክል የመደብ ለውጥ አይመጣም።
የመደብ ለውጥ ሳያመጣ እንዲሁ አርሶ አደር እንደሆነ መቀጠል የለበትም፤ መቼም። ያንን ለማምጣት ከፈለገ የሕብረተሰቡን ገንዘብ የሚበላውን ነገር ማስተካከል አለበት።
ከተሞችና ኮንስትራክሽን አብረው አርሶ አደሮቹን መበዝበዣዎች ናቸው፤ እርሱን መጀመሪያ ማስተካከል አለብን። ይኼ መሰረታዊ የፖለቲካል ኢኮኖሚ ሀሳብ ነው። አሁን ግን ሌሎች ሌብነቶችም ወደ ኮንስትራክሽን ዘርፉ እየገቡ ነው።
ለምሳሌ ብረትን ብትወስድ ብዙ አስመጪዎች ሲያስመጡ ታክስ የለባቸውም ነገር ግን ዶላሩ በእጃቸው ስለማይገባ ብዙ ፐርሰንት ይወስድባቸዋል። (30 ፐርሰንት ይመስለኛል) ዶላሩንም ቢሆን እንደፈለጉ ስለማይገዙ የአርማታ ብረት ብዙ አስመጪዎች የውጪ ምንዛሬ የሚመነዝሩበት ሆኗል።
የውጪ ምንዛሬ እጥረት ተፈጠረ ከተባለ በኋላ የብረት ዋጋ በ300 ፐርሰንት ጨምሯል። በኪሎ ከ18 ብር የነበረው 54 ብር ነው የገባው። ብሄራዊ ባንክ የሚያወጣውን መረጃ ብናይ ብር ተገቢ ያልሆነውን ዋጋ እንደተሰጠው ያሳያል። ላኪው ይህንን የብርን ያልተገባ ዋጋ የሚያካክሰው ቡናውንም ሰሊጡንም በርካሽ ዋጋ ይሸጥና ከውጪ የሚመጣውን ብረት ውድ ያደርገዋል።
ስለዚህ ብረት አሁን ወርቅ ሆነ፤ የኮንስትራክሽን ዘርፉን የሚቆጣጠሩት ብሔራዊ ባንክንና የውጪውን ንግድ የሚቆጣጠሩት ኃይሎች ናቸው። ስለዚህ እኛ ዝም ብለን አስተላላፊ ነን። የውጪ ምንዛሬ እናገላብጣለን እንጂ ሥራ አንሰራም።
ይኼ ቢከፈት ግን ቀጥታ ማስመጣት ብንችል ላኪውም ያ መንገድ ስለሌለው ወደ አገልግሎት ሰጪ ዘርፎች ወይንም ወደ ካፒታል ኢንቨስትመንት ይሄዳል።
ወደ ኮንስትራክሽን ዘርፉ መግባት ለሚፈልጉ ወጣቶች ምን ትመክራቸዋለህ?
ኮንስትራክሽን በእኔ ግምት በየትኛውም ሀገር ውስጥ በቀላሉ የሌብነት ጫካ መሆን የሚችል ዘርፍ ነው። የመሰረተ ልማት ግዢ ግዙፍ ስለሆነ በርካታ ነገሮች በቀላሉ አይታወቁም። አንድ የሽንት ቤት መቀመጫ አምስት ሺህ ዶላርም አምስት ዶላርም ሊሆን እችላል። በእነዚህ ነገሮች ውስጥ አንዱን ዋጋ ሰጥተህ አንደኛውን ማቀበል ዋናው የትርፍ ምንጭ ነው።
ሌላው የትርፍ ምንጭ ደግሞ በወዛደሩ ጉዳት ማትረፍ ነው። እነዚህ ነገሮች መስተካከል አለባቸው። አዳዲስ ወደ ገበያው የሚገቡ ወጣቶች የዋህነታቸው ሳይጠፋ የሀገር ተልእኳቸውን እንዲጨምሩበት ማስቻል አለብን።
ይህ ለየትኛውም ዘርፍ ይሰራል። ኮንስትራክሽን ዘርፉ ላይ ደግሞ ለሰው ልጆች ብሎ የቆመ ከሁሉም የላቀ ውጤት ያገኛል ብዬ አምናለሁ። እኔ እንደዛ ነው እዚህ የደረስኩት። መጥፎ ሳልሆን ቀርቼ ሳይሆን መጥፎዋን መንገድ ቀድሜ ስለተውኩት ነው።