አንድ ሀገር ከፍ ያለ አደጋ ሰያጋጥመዉ ለምሳሌ ቴረሪዝም ወይም መፈንቅለ መንግስት እንዲሁ ዝም ብሎ በደቂቃዎች ዉስጥ ተነስቶ ይህ መፈንቅለ መንግስት ነዉ፡፡ ይህ ቴረሪዝም ነዉ አይልም፡፡ መጀመሪያ ይጣራል፡፡ ችግሩን አደረሰ የተባለዉ ሰዉ ፕሮፋይሉ እና ያቀናበረዉ ነገር ብሎም ያደረሰዉ ጉዳት ይመረመር እና ለሀገሪቱ ሹማምንቶች ቀርቦ አዎ ይህ ነገር እንዲህ አይነት አደጋ ነዉ ይባላል፡፡

ባህርዳር ችግር ተከሰተ በተባለ ጊዜ ወዲያዉኑ ተነስቶ መፈንቅለ መንግስት ተደረገ ተብሎ በቴሌቪዥን የታወጀዉ እንዴት ነዉ፡፡ የግል ጠብ ቢሆንስ ወይም ቂም በቀል ቢሆንስ? ሌላ አካል ቢሆንስ? በአዴፓ ወይም በኢህአዴግ ፓርቲ ዉስጥ የሰዎች አለመስማማት ቢሆንስ? ይህ ሁሉ እንዴት በ 1 ሰአት ወይም በ 30 ደቂቃ ዉስጥ ተመርምሮ የጠቅላይ ሚኒስቴር ቢሮ ዉሳኔ ላይ ደረሰ? የአዴፓ ፕሬዝደንት አቶ ደመቀ መኮነን፤ የበፊቱ የአዴፓ ምክትል ፕሬዝደንት አቶ ገዱ አንዳርጋቸዉ፤ የአሁኑ የአዴፓ ምክትል ፕሬዝደነት ዶ/ር አመባቸዉ በተገደሉበት፤ የአዴፓ ጽ/ቤት አቶ ሃላፊ ዮሃንስ በሌለበት፤ የአማራ ክልል መንግስት ኮሙኒኬሽን ሃላፊ አቶ አሰማኃኝ ስልኩ በማይሰራበት ሁኔታ የትኛዉ አካል ነዉ ጉዳዩን አጣርቶ ተወያይቶ ይህ ድምዳሜ ላይ የደረሰዉ፡፡ ነዉ ወይስ ጠቅላይ ሚኒስቴር ቢሮ መፈንቅለ መንግስት እንደሚካሄድ ያዉቅ ነበር እናም ጉዳዩ እስኪፈጸም ድረስ እየጠበቀ ነበር? ሌላዉ መፈንቅለ መንግስት ወይም ቴረሪዝም ወይም ሌላ ነገር ሀገሪቱ ላይ ሲከሰት የሀገሪቱ የሴኪዩሪቲ ካዉንስል ተሰብስቦ ዉሳኔ ይወስናል፡፡ የዚህ ካዉንስል አባላት የሀገሪቱ ም/ጠቅላይ ሚኒስቴር አቶ ደመቀ አልነበሩም ተብሏል፤ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩ አቶ ገዱ አልነበሩም፤ የሀገሪቱ ጦር ሃይሎች አዛዥ ተገለዋል:: እና እንዴት ነዉ እዚህ ድምዳሜ ላይ በ 30 ደቂቃ ዉስጥ የተደረሰዉ፡፡
ይህ ነገር አማራን መሪ አልባ ከማስቀረት ባለፈ ሌላም አላማ ነበረዉ፡፡ ህወሃት በ 1993 ስትከፋፈል መለስን ለመግደል እነ ስየ አብርሃ አሲረዉ ከመቀሌ በፍጥነት ቦሌ ከማረፍ ይልቅ በአቶ አዲሱ ለገሰ ምክንያት ደ/ዘይት እንዲያርፍ ሆኖ ተርፏል፡፡ የእነ ስየ ቡድን ቤተመንግስት ለመግባት ሲሞክር እዛዉ በጠባቂዎቹ ተይዘዋል፡፡ ይህ መፈንቅለ መንግስት አልተባለም፡፡ በኤርትራ ጉዳይ ስላልተስማሙ ነዉ በሚል ታለፈ፡፡ ጠ/ሚ መለስ በሽሬ በኩል ወደ ጎንደር በመኪና ሲያቀና ተተኩሶበት እርሱ ይኖርበታል የታባሉ ሁለት መኪኖች ተመተዉ እስከ 4 የሚሆኑ የጦር መኮነኖች መተዉ እና ቆስለዋል፡፡ ይሄን ያደረገዉ የዘመቻ ሃይል አስተባባሪዉ ነዉ በማለት በነገዉ ከስልጣን አባሮታል በኋላም እንዲገደል ሁኗል፡፡ ይሄም መፈንቅለ መንግስት አልተባለም፡፡ ሽፍቶች ናቸዉ ተብሎ ታለፈ፡፡ ምክንያቱም ይሄ ነገር የተካሄደዉ እዛዉ እነ መለስ ወክለዉት ከመጡበት ማህበረሰብ የወጡ ሰዎች ስላደረጉት መፈንቅለ መንግስት ቢባል ከጉዳዩ ፈጻሚዎች አልፎ የማህበረሰቡን ስም ስለሚያጠፋ ነዉ፡፡ በቅርቡ ከአመት በፊት በጠ/ሚ አብይ ላይ የግድያ ሙከራ ሲደረግ መፈንቅለ መንግስት አልተባለም፡፡ ለዉጡ ያልጣማቸዉ ግለሰቦች ናቸዉ ተብሎ ታለፈ፡፡ ከዛም አልፎ ከ 60 በላይ ወታደሮች እና ኦፊሰሮች ጠቅላይ ሚኒስትሩን እና ምክትል ጠቅላይ ሚንስትሩን ለማፈን ቤተ መንግስት የገቡ ጊዜ ደምዝ ጭማሪ ፈልገዉ ተባለ እንጅ መፈንቅለ መንግስት አልተባለም፡፡
እንዲያዉም ቤተመንግስት የሄዱት ወታደሮች አቶ ደመቀን አፍነዉ እነ ተፈሪ ባንቲ ወደ ተገደሉበት ቦታ ለመግደል ወስደዉ 4 እና 5 አብረዉ የነበሩ የአማራ ወታደሮች ነገሩን አይተዉ እዚሁ እንተላለቃታለን እንጅ አትገድሉትም በማለታቸዉ በወታደሮቹ መካከል ክፍፍል በመፈጠሩ በህይወት እንደተረፈ ይታወቃል፡፡ ቤተመንግስት ተሂዶ እንዲህ የተደረገ ድርጊት እንዴት መፈንቅለ መንግስት አልተባለም? እኒህ ሁለት ኩነቶች የተደረጉት እና የተቀነባበሩት እነ አብይ ከወጡበት ማህበረሰብ የወጡ የራሳቸዉ ሰወች ስለሆኑ መፈንቅለ መንግስት ብለዉ ቢያዉጁ ከአድራጊዎቹ አልፎ የማህበረሰቡን ስም የሚያጠፋ እና ጠባሳ ጥሎ የሚያልፍ በመሆኑ ነዉ፡፡
በአንጻሩ በ 2 ሺህ ዓ.ም ገደማ ገና አንዲት ጥይት ሳይተኩሱ በደህንነቱ በኩል ተደርሶባቸዋል ተብሎ በመቶዎች የሚቆጠሩ የአማራ የጦር ኦፊሰሮች ተለቃቅመዉ ሲያዙ አይተናል፡፡ ነገር ግን ለአም በሰበር ዜና የተነገረዉ የትምህክተኛዉ እና የነፍጠኛዉ የአማራ ማህበረሰብ አባላት የሆኑ መፈንቅለ መንግስት ሊያደረጉ ሲሉ ተያዙ ተብሎ ተነገረ፡፡ ከዛም አልፎ አሸንፈን የቀበርነዉን የአምባገነኑን የደርግ ስርአት ለመመለስ ነዉ ተብሎ ለአለም ህዝብ ተሰራጨ፡፡
ለምን ባህርዳር ላይ የተከሰተዉን ነገር በፖለቲካ ስላልተስማሙ ነዉ አልተባለም? ለምን በድርጅቱ ዉስጥ በነበረዉ ዳይናሚክስ ምክንያት እርስ በርስ ነዉ አልተባለም? ለምን በለዉጡ አካሄድ ስላልተስማሙ ነዉ አልተባለም? ነገሩ ወዲህ ነዉ፡፡ ባንድ ድንጋይ ሁለት ወፍም እንደማለት ነዉ፡፡ህዝቡን ያለመሪ ከማስቀረትም ባሻገር የአማራን ህዝብ በጅምላ blackmail የማድረግ እና ከሀገር አልፎ በአለም አቀፍ ማህረበሰቡ ዘንድ ሀገር አፍራሽ አድርጎ ለማቅረብ እና ከዚህ በፊት እንደተደረገዉ የአማራን ህዝብ ከሀገሪቱ የፖለቲካል ኢኮኖሚ ሜዳ ዉጭ ለማድረግ ነዉ፡፡ ይሄን በመንተራስ ነዉ የአሜሪካ ስቴት ዲፓርትምንት carreer diplomat የሆኑት እነ ሄርማን ኮኸን ሳይቀር የተደረገዉ መፈንቅለ መንግስት የአማራን hegmoney ለመመለስ ነዉ፡፡
ይህ ደግሞ አይሳካም እያሉ ሲያወሩ የነበረዉ፡፡ ችግሩ እነሱ ላይ ሳይሆን ከመንግስት የተነገራቸዉ መረጃ ነዉ፡፡ አላወቁትም እንጅ ይህ ለአዴፓ ብሎም ወደፊት ለሚመጡት የአማራ ፖለቲከኞች ከፍተኛ ችግር የሚፈጥር እና ምናልባትም ኦህዴድ እራሱን አምባገንን በማድረግ ሀገሪቱን ለረዥም ጊዜ ለመቆጣጠር የሚያደርገዉን ዝግጅት ያሳያል፡፡ ህወሃት ከዚህ በፊት የኦሮሞን ፖለቲከኞች ሀገር አፍራሽ ናቸዉ በማለት ለዉጩ አለም በማናፈሳቸዉ እነ ዶ/ር አብይ እና ለማ ወደ ስልጣን ሲመጡ የአሜሪካኖችን ይሁንታ ለማግኘት በወር 5 ጊዜ እነ ወርቅነህ ገበየሁ ዋሽንግተን ይመላለሱ ነበር፡፡ የአማራን ፖለቲከኞች የደርግን ስርአት ሊመልሱ ነዉ የሚታገሉት በማለት አለም ላይ ለ 27 አመታት ይደረግ የነበሩትን ተቃዉሞወች ጀሮ ዳባ ልበስ ተብለዉ ነበር፡፡ የአማራ ህዝብ ለጊዜዉ መሪዎቹን ማጣቱ ብቻ አይደለም የሚጎዳዉ፡፡ ወደፊትም ሀገር እንዳይመራ፤ ልጆቹ በኢትዮጵያ ሰማይ ስር ተሸማቀዉ እና አንገት ደፍተዉ እንዲኖሩ እንጅ ሀገር የማስተዳደር ሃላፊነት እንዳይረከቡ፤ በአለም መድረክ ስሙ እንዲጠፋ በማድረግ ከፍተኛ ችግር ዉስት ይከታል፡፡
በመሆኑም ካጣናቸዉ ወንድሞቻችን በላይ አጠቃላይ የአማራን ህዝብ ለረዥም ጊዜ የሚጎዳ እና ስሙን የሚያስጠፋ (character assassination) በገለልተኛ አካል ያልተመረመረ፤ በአዴፓ አመራር ዉስጥ የነበረዉን የርስ በርስ ግንኙነት ያልመረመረ እንዲሁም የክልሉ መንግስት መርምሮ አደጋዉን ስም ሳይሰጥ የፌደራል መንግስቱ የወሰደዉን አቋም እንደገና እንዲያየዉ እና መፈንቅለ መንግስት የሚባለዉን ትርክት ኦፊሻሊ እንዲሰርዝ እጠይቃለዉ፡፡ ገለልተኛ አካል ተቋቁሞ ባህርዳር እና አዲስ አበባ የተደረገዉ ነገር ተመርምሮ ዉጤቱ ለህብረተሰቡ እንዲገለጽ አሳስባለዉ፡፡