7 ጁላይ 2019

የተለያዩ ደራሲያን መፃህፍት

ዘመናዊ የአማርኛ ሥነ ጽሑፍን ዛሬ የደረሰበት ደረጃ ላይ ካደረሱት ጎምቱ ጸሃፍት መካከል ቀላል የማይባሉት አፋቸውን የፈቱት በሌላ ቋንቋ ነው። ከስብኅት ገብረእግዚያብሔርና ከበዓሉ ግርማ ውጪ የአማርኛን ልብወለድ ማሰብ ከባድ ነው። ጸጋዬ ገብረመድኅንን ደግሞ ከተውኔቱና ከሥነ ግጥም አንፃር አለማውሳት አፍ ማበላሸት ነው። ግጥምንስ እንደ ሰለሞን ደሬሳ ማን አዘመነው ሊባል ነው?

አንዳንድ ምሁራን ደግሞ የአማርኛን ትርጉምን ከሳህለሥላሴ ብርሀነማርያም ውጪ ማሰብም አይቻልም በማለት ዘመናዊ የአማርኛ ሥነ ጽሑፍን ከተለያዩ ቋንቋ ተናጋሪዎች የመጡ ሰዎች እንዳፋፉትና አሁን ያለውን ቅርፅ እንደሰጡት በመናገር “የአማርኛ ሥነ ጽሑፍ የኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ነው” ይላሉ።

ኮሎኔል መንግሥቱን ትግል ለመግጠም ቤተ መንግሥት የሄደው ደራሲ

“ከወጡት ስራዎቼ ይልቅ ገና የሚወጡት ናቸው ትልቅ ቦታ ያላቸው” አለማየሁ ገላጋይ

በኢትዮጵያ ዘመናዊ ሥነ ጽሁፍ ውስጥ ደረጃ ቢወጣ እነዚህ አንቱ የተባሉ ደራሲያን ከአምባው አናት ላይ የሚቀመጡ መሆናቸውን የዘርፉ ምሁራን ይስማማሉ።

እነዚህ ደራሲያን በሌሎች የዓለም ቋንቋዎች የመፃፍ እድል እያላቸው በአማርኛ የፃፉ፣ የራሳቸውን የሥነ ጽሁፍ ዘይቤ የገነቡ መሆናቸውን በመቀሌ ዩኒቨርስቲ የውጪ ቋንቋዎችና ሥነ ሥሑፍ ክፍል ረዳት ፕሮፌሰር የሆነችው ፀደይ ወንድሙ ትናገራለች።

እርግጥ ዘመናዊ የአማርኛ ሥነ ጽሁፍ ዘር ልቁጠር ካለች እርቃኗን እንደምትቀር የኮተቤው የሻው ተሰማ ያነሳል። ለዚህም በዓሉ ግርማ፣ ፀጋዬ ገብረመድኅ፣ ሠለሞን ደሬሳ፣ ገበየሁ አየለ፣ አማረ ማሞ፣ ሙሉጌታ ሉሌ፣ ታቦር ዋሚ እያለ መጥቀስ አማርኛ ሥነ ጽሁፍ በእነማን ጫንቃ ላይ ወድቆ እንደነበር ለመረዳት ይቻለናል ሲል ያብራራል።

ታዲያ እነዚህን ስመ ገናና ደራሲያን ለዘመናዊ አማርኛ ሥነጽሑፍ ያላቸው አበርክቶ ምንድን ነው?

ለዘመናዊ አማርኛ ሥነጽሑፍ ካስማ የሆኑ ደራሲያን

ደራሲ ዓለማየሁ ገላጋይ አማርኛ ከግራም ከቀኝም የተወጠረበት ካስማ አለው በማለት ከኮተቤ የሻው ሀሳብ ጋር ይስማማል።

የመጀመሪያዎቹን የአማርኛ ደራሲያንን በተመለከተ “እውነት ነው አፋቸውን በአማርኛ የፈቱ ሰዎችን እናገኛለን” ብሎ እነ መኮንን እንዳልካቸው፣ ዮፍታሄ ንጉሴ ፣ ግርማቸው ተክለ ሐዋርያትን የሚጠቅሰው ዓለማየሁ፤ በተጨማሪ ግን የአማርኛ ልብ ወለድ ሥጋና ደም ነስቶ እስትንፋስ የዘራው አፋቸውን በአማርኛ በፈቱ ደራሲያን እንዳልሆ ይጠቅሳል።

ለአማርኛ ሥነ ጽሁፍ ሁለተኛው ረድፍ ላይ ተሰልፈው የሚገኙት ከጣሊያን ወረራ በኋላ የተወለዱት፣ በተለይ ከ1928 ዓ.ም ወዲህ፣ ከመሰረተ ልማት መስፋፋት በኋላ የመጡት ደራሲያን መሆናቸውን ዓለማየሁ ያነሳል።

“ፍቅር እስከ መቃብር”ን በአይፎን 7?

ጣሊያን በገነባው የጥርጊያ መንገድ ላይ በእግርም በበቅሎም ተጉዘው ወደ ያኔዋ አዲስ አበባ መምጣት የቻሉ እነዚህ ደራሲያን የአማርኛ ሥነ ጽሁፍን በዛሬው መልክና ልክ አሳደጉት ሲል ዓለማየሁ ያስረዳል።

ከትግራይ ስብኅት፣ ከአምቦ ፀጋዬ፣ ሰለሞን ከወለጋ፣ አሰፋ ጫቦ ከጨንቻ በድርስቱም ሆነ በተለያዩ የመገናኛ ብዙኀን ውስጥ በመሳተፍ አማርኛ ለሥነ ጽሑፍ ምቹ ቋንቋ እንዲሆን ያበረከቱት አስተዋጽኦ ቀላል አለመሆኑን ያሰምርበታል።

ረዳት ፕሮፌሰር ፀደይም ዘመናዊ የአማርኛ ሥነ ጽሁፍን ዛሬ በምንነጋገርበት ደረጃ አጽንተው ያቆሙት ደራሲያን ወደ አዲስ አበባ የመጡት በልጅነታቸው መሆኑን በመጥቀስ አፋቸውን ከፈቱበት ቋንቋና ባህል በይበልጥ ከተሜነት ገኖ እንደሚታይባቸው ታስረዳለች።

ነባሩን ባህል በመግሰስ የከተሜ ባህልን ማንገስ

ሁሉንም በ1960ዎቹ አካባቢ የአማርኛን ዘመናዊ ድርሰት የጀመሩትን ደራሲያን በጅምላ ብንመለከት የሚለው ደራሲ ዓለማየሁ ነባሩን ባህል በማሻሻልና በዘመናዊ ባህል ውስጥ በማካተት የራሳቸውን አብዮት የመሩ ናቸው ይላል።

ለዚህም አስረጂ ሲጠቅስ አማርኛ አፍ መፍቻቸው ያልሆኑ ደራሲያንን ብቻ ሳይሆን ሌሎቹንም እንደ ዳኛቸው ወርቁ ያሉ ደራሲያንን መመልከት አስፈላጊ መሆኑን የሚያነሳው ዓለማየሁ “ዘላለም ውስጥ ለውስጥ የሚስለከለክ ባህልን በማደፍረስ ላይ የተመሰረተ ልብ ወለድ” በእንግሊዘኛም በአማርኛም በመፃፍ የዘመኑን መልክ ያሳየናል።

ይህ አቤ ጉበኛንም ይጨምራል ሲል ይጠቅሳል።

“ወሎዬው” መንዙማ

እነዚህ አፋቸውን በሌላ ቋንቋ የፈቱና ለዘመናዊ የአማርኛ ሥነ ጽሁፍ የአንበሳውን ድርሻ ያበረከቱ ደራሲያን የከተሜን አዲስ ባህልና ዘመናዊነትን በማምጣት በሥራዎቻቸው ውስጥ መታተራቸውን ያነጋገርናቸው በሙሉ ይጠቅሳሉ።

የገጠሩን ባህል ወደ አዲስ አበባ ይዞ የመጣውን ማህበረሰብ ፈትሮ በመያዝ አዲስ ባህል፣ አዲስ አስተሳሰብ እንዲያዳብር የዘመናዊ ደራሲያኑ ፋና ወጊዎች በሥራዎቻቸው ማሳየታቸውን ይጠቅሳሉ።

እነዚህ ደራሲያን ከተለያየ ባህልና ቋንቋ መምጣታቸውን ካየን የመጡበትን አካባቢ ባህል ወደ ሥራዎቻቸው አሻግረው ይሆን? መነሳቱ የማይቀር ጥያቄ ነው።

ሦስቱም እንግዶቻችንን የሚያስማማው እነዚህ ደራሲያን መጥተው የገቡበት የከተሜነት ባህል የራሱ ቀለም ያለው መሆኑ ላይ ነው።

እሳት ወይ አበባ እና ትኩሳት መጽሐፍት

ለረዳት ፕሮፌሰር ፀደይ ወንድሙ የእነዚህ ደራሲያን የሕይወትና የንባብ ተጋልጦ በራሱ ዘመናዊነትን የሚያሳይ እንደነበር በመጥቀስ “በዓሉ በእንግሊዘኛ የጻፋቸው ግጥሞች ነበሩት፤ ስብኅትም የዳኛቸው ወርቁን ሥራ አንብቦ በአማርኛ መጻፍ ከመጀመሩ በፊት በሌላ ቋንቋ መጻፉን በዘነበ ወላ ‘ማስታወሻ’ ውስጥ አንብበናል” ትላለች።

አክላም እነዚህ ደራሲያን ዘመናዊነትን የተዋወቁትና ወደ ሥራዎቻቸው ያመጡት ከሕይወት ልምዳቸው መሆኑን በመጥቀስ በዘመናዊነት ውስጥ የሚጠቀሙበት ቋንቋ የአማርኛ ሥነ ጽሁፍ ቅልጡፍ እንዲሆን መጣራቸው ይታያል ትላለች።

ደራሲ ዓለማየሁ ገላጋይ ስብኅት ከተሜነት፣ ሁሉን አቀፍ በሆነው የከተሜ ባህል፣ ዘመኑ የፈጠረውንና የሚያሳየውን በማስተጋባት አስተዋፅኦ እንደነበረው በማስታወስ፤ የተወለደበትንና ያደገበትን ባህል ወደ አማርኛ ሥነ ጽሁፍ የማሻገር ሀሳብ እንዳልነበረው ያሰምርበታል።

የበዓሉ ግርማ ሥራዎችም ውስጥ ከተሜነት መንበሩን ተቆናጦ እንደሚታይ ሁለቱ ምሁራን ሲናገሩ ደራሲ ዓለማየሁ ደግሞ ከተሜነት ብቻ ሳይሆን ነባሩ ባህል ከአዲሱ መጤ ባህል ጋር ሲጣላ፣ ሲጋጭ፣ ሲናጭ ይታያል ይላል።

በበዓሉ ድርሰት ውስጥ ነባሩን ባህል አዲሱ ሲያሸንፍ ይስተዋላል የሚለው ዓለማየሁ አዲስ አስተሳሰብን፣ አዲስ አበቤነትን በመመስረት፣ አዲስ አበቤነትን በማንፀባረቅ የተሻለ መሆኑን ይጠቅሳል።

ተፈጥሮን በብሩሽ የሚመዘግበው መዝገቡ

የኮተቤው የሻው የእነዚህ ደራሲያን ከተሜነት ብቻ ሳይሆን ዘመናዊ ደራሲያን መሆናቸው በራሱ የተወለዱበትን ባህል ለማሻገር እድል እንዳልሰጣቸው ያስረዳል።

ረዳት ፕሮፌሰር ፀደይ፤ የመረጡት ዘውግ ለዚህ ምቹ እንዳልነበር ከየሻው ጋር ትስማማለች። በርግጥ መቼታቸውን ከተማ ማድረጋቸው ባህልን ለማሻገር ከብዷቸዋል ብሎ ለመደምደም አስቸጋሪ ነው በማለት አብዛኞቹ ዘመናዊ ደራሲያን ወደ ከተማ የመጡት ገና በልጅነታቸው እንደሆነ ገልፃ ረጅም ጊዜ በንባብና በኑሮ ያሳለፉት በከተማ ውስጥ በመሆኑ ከተሜነት በሥራዎቻቸው ውስጥ እንደሚጎላ ታብራራለች።

አክላም “ያኔ ትልቋ ከተማ አዲስ አበባ ብቻ ነበረች፤ እንደዛሬው ሌሎች ከተሞች ባለመኖራቸው አዲስ አበባና አዲስ አበቤነት ብቻ” መጉላቱን ታስረዳለች።

ጋሽ ፀጋዬ ከሌሎቹ ደራሲያን ይለያል የሚሉት የኮተቤው የሻውና የመቀሌዋ ረዳት ፕሮፌሰር ፀደይ፣ በተለይ በግጥሞቹና መጣጥፎቹ ውስጥ የኦሮሞን ባህል ሲያስገባ እናያለን ይላሉ።

ግን ይሄ የኦሮሞን ባህልና ቋንቋ ብቻ ሳይሆን ከዚያ ከፍ ባለና ደማቅ በሆነ መልኩ በሥራዎቹ ነባር ጀግኖችን በመፍጠር በሀገርና በዓለም አቀፍ ደረጃ አግዝፎ ማሳየት የፀጋዬ ሥራዎች ውስጥ የሚታዩ መሆናቸውን የሻው ያነሳል።

“ጋሽ ፀጋዬ የሚያስብበት ጠገግ ሥነሰባዊ ስለሆነ፣ እኛን በጥንትነት ውስጥ የመፈለግ አዝማሚያ ስላለው ነው” በማለትም ሌሎቹ ግን አዲስ አበቤነት በሚያጠቃው የአስተሳሰብ ጠገግ ውስጥ ያሉ በመሆናቸው ለምን አፋቸውን የፈቱበትን ቋንቋና ባህል አላሻገሩም ብሎ እንደማይከሰሱም እንደማይወቀሱም ሁለቱም ይናገራል።

ጥበብን በወር-አበባና በአጽም

ደራሲ ዓለማየሁ፤ የፀጋዬ ጥረት ኢትዮጵያን ዓለም አቀፋዊ ማድረግ ነው በማለት “በግብፅ በኩል አድርጎ ግብፅ ላይ ደግሞ በጥቁር ሥልጣኔ ውስጥ ኢትዮጵያ ያላትን ድርሻ ከፍ አድርጎ ማሳየት ነበር ሕልሙ” ይላል።

ፀጋዬ ኢትዮጵያን ከፍ ከፍ በሚያደርግ ጥናት ላይ ተመስርቶ ነበር ሲሰራ የነበረው የሚለው ዓለማየሁ ወደ ኋላ 13 ሺህ ዓመታት ተጉዞ የአፍሪካዊያንን የፍልስፍና መሰረትና የሥልጣኔ ማማነት ለማሳየት መትጋቱን በማስታወስ የመጣበትን ባህል በአማርኛ ሥነ ጽሁፍ ላይ ለመጫን አለመሞከሩን ያስረዳል።

ሠለሞን ደሬሳ የተለመዱ ሥራዎች ላይ አመጽ ያስነሳ፣ ያፈነገጠ ደራሲ ነው የሚለው ዓለማየሁ የተሻለ መንገድ በመቅደድ ያበረከተው አስተዋጽኦ እንደሚጎላ ይናገራል።

ዓለማየሁ የሰለሞን ደሬሳን “ባህልና እኔ” የሚል አጭር መጣጥፍ በመጥቀስ የኖረውን ሥርዓት በማፍረስ አዲስ ጥርጊያ መንገድ በመቅደድ ረገድ ደፋርና የተሳካለት ደራሲ እንደነበር ያስታውሳል።

ከመጡበት ማበረሰብ ወደ አማርኛ ቋንቋ ያሻገሩት ቃል፣ እሳቤ፣ ባህል

አማርኛን ቋንቋ የዳበረው ከአረብኛና ከኦሮምኛ በወሰዳቸው በርካታ ቃላት ነው የሚለው ዓለማየሁ ገላጋይ አንዳንዴ እንደውም ቃላት ብቻ ሳይሆን እሳቤም ይወስዳል ሲል “ጉዲፈቻ”ን በምሳሌነት ያስረዳል።

ስለዚህ እነዚህ ደራሲያን በስልትም ሆነ በቋንቋ ወደ አማርኛው በማጋባት በኩል እምብዛም መሆናቸውን በመግለፅ፤ ደራሲያኑ ከተሜነት ውስጥ ሲገቡና እዚያው ውስጥ በአማርኛ ሲጽፉ ይታያል እንጂ ከመጡበት ቋንቋ ወደ አማርኛ ሲያመጡ አይስተዋልመ ይላል።

ረዳት ፕሮፌሰር ፀደይ እነዚህ ደራሲያን ከመምጣታቸውም በፊት ቋንቋዎቹ በራሳቸው መዋዋስ ጀምረዋል በማለት ባህልና ቋንቋ ማሻገሩን ከደራሲያኑ አንጻር ብቻ ማየት እንደማይገባ ትገልፃለች።

በእርግጥ ዘመናዊ ደራሲያኑ ሥነ ጽሑፉን ሲያዘምኑ ቋንቋውን ለዚህ እንዲመች አድርጎ ቅልጡፍ ማድረግ ላይ መጨነቃቸው እንደማይቀር የምትናገረው ፀደይ ሠለሞንና ፀጋዬ በሥራዎቻቸው ውስጥ ከኦሮምኛ የወሰዷቸውን ቃላትና አንዳንድ አገላለፆች መጠቀማቸውን ትጠቅሳለች።

”አዝማሪዎቻችን የሙዚቃ ሳይንቲስቶች ናቸው”

“እነዚህ ደራሲያን ከኦሮምኛ ቃላትን በመምጣት ከአማርኛ ጋር በመሸመን ሲጠቀሙ ቢስተዋልም ሌሎቹ ደራሲያን ግን የአማርኛ ቋንቋ ለሥነ ጽሁፍ ቅልጡፍ እንዲሆን በማድረግ ውስጥ ሚናቸው ይጎላል።”

የኮተቤው የሻው ተሰማ ዘመናዊ የአማርኛ ሥነ ጽሑፍ ደራሲያን የኖሩበትና የጻፉበት ዓለም በዙሪያው ከሚገኙ የተለያዩ ማኅበረሰቦች በተዋጣና በተዳቀለ ባህልና ወግ ውስጥ በመሆኑ የመጡበትን ማኅበረሰብ ባህል በተለየ ሁኔታ ለማሳየት እንዲጨነቁ አላደረጋቸውም ይላል።

በእርግጥ ሰለሞን ደሬሳ አንዳንድ የኦሮምኛ ቃላትን አምጥቶ ለማስገባትና ወደ አማርኛ ለመለወጥ ሲሞክር ይታያል የሚለው ደራሲ ዓለማየሁ፤ ፀጋዬ ገብረመድኅንም አማርኛ ከአያቱ ግዕዝ ይልቅ ሊዳብርም ሊስፋፋም የሚችለው በወንድሞቹ ኦሮምኛ፣ ወላይትኛ ሲዳምኛ ያሉ ቋንቋዎች ነው ይል እንደነበር ይገልፃል።

የአማርኛ ሥነ ጽሁፍ ከሌሎች ወንድም ቋንቋዎች እየተቀበለ በውስጡ ቢያካትት የውጪውን ቋንቋ ሊገዳደር በሚችል መልኩ ስፋቱም ይገዝፍ፣ ጥልቀቱም ይርቅ እንደነበር ያስረዳል።

ድምፅ ፈታዮቹ መረዋዎች

በአማርኛ ሥነ ጽሑፍ ውስጥ ከተለያየ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ትርጉሙን፤ ቃላቱን ብቻ ሳይሆን እሳቤውንም ጭምር በማምጣት አማርኛን ማግዘፍ ይቻል እንደነበርም ሲያስረዳ ወላይታ “ሀይሲ” የሚሰኝ የአገጣጠም ስልት አለው በማለት ነው።

ይህ የወላይታ አገጣጠም ስልት ከሰሜን በመጣው የቅኔ ባህልም ሆነ በዘመናዊ የአማርኛ የአገጣጠም ስልት አይሄድም በማለት አማርኛ ወደ ራሱ ለመውሰድ እንዳልቻለ በማንሳት በዚህ ረገድ በዘመናዊ ደራሲዎቹ ላይ የታየውን ክፍተት ያነሳል።

የተጠቀሱት ዘመናዊ ደራሲያን ለአማርኛ ሥነ ጽሑፍ ያበረከቱትን ውለታ መሠረት በማድረግ ከአማርኛ ቋንቋ ውጪ ያሉ የሌሎች ሀገርኛ ቋንቋ ተናጋሪ የሆኑ ደራሲያን በአማርኛ የመጻፍ አስተዋጽኦ ቢያደርጉ የአማርኛ ሥነ ጽሁፍን የተሻለ ማድረግ ይቻል ይሆን?