July 14, 2019

Source: https://www.zehabesha.com/amharic/archives/96060

ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 6/2011 ዓ.ም (አብመድ) ወቅቱ የተረጋጋች ሀገር የሚገነባበትና የምርጫ ዝግጅት የሚደረግበት በመሆኑ ፖለቲካዊ መተማመን ላይ መድረስ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ ሊቀመንበር ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ ተናገሩ፡፡

መግለጫ የሚያወጡ አካላት በድርጅታዊ ህይዎት ውስጥ ብዙ ያሳለፉና ሃገር የሚመሩ ናቸውና ክልላዊና ሃገራዊ አንድምታውን አይተው ለሰላምና መረጋጋት እሴት በሚጨምር መልኩ መግለጫ ቢያወጡ ይሻላል ብለዋል ከአብመድ ጋር ቆይታ ያደረጉት ፖለቲከኛ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ፡፡ ሀገር መምራት ማለት በእልኸኝነት ብሶትን ብቻ በማንፀባረቅ የሚሆን አይደለም፤ ብዙ ነገሮችን ችሎ ለሀገር እና ሕዝብ የሚበጀውን ማስቀደም ነው ብለዋል ፕሮፌሰር በየነ፡፡ ከሰሞኑ ከዚህም ከዚያም የተወረወሩት መግለጫዎች ቀድሞ ከተገባበት እልህ ውስጥ ሳንወጣ ወደ ሌላ እልህ የሚያስገባ አይነት ነው ብለዋል ፖለቲከኛው፡፡

ፖለቲከኞች በለመዱት አግባብ የሀገርንና የሕዝብን ጥቅም በማስቀደም ፊት ለፊት በመገናኘት በችግሮቻቸው ላይ ተወያይተው ይቅርታ መባባል ይኖርባቸዋል እንጂ በሩቅ ሆኖ መወራወሩ ዳኛው ማን እንደሆነ ባይታወቅም የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ይታዘባል ነው ያሉት ፕሮፌሰር በየነ፡፡ ይቅርታ ይጠይቁም ሆነ የግድያ ሁኔታው ይጣራ የሚሉት ጥያቄዎች ወደ አንድ በኩል ባደላ መልኩ ሳይሆን መቅረብ ያለበት ከተጣራ በሁለቱም ወገን በኩል ያለው ችግር መጣራት ይኖርበታል ያሉት ፕሮፌሰሩ የሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ (ሕወሃት) መግለጫ ሀገራዊ አስተሳሰብና ሃቅ ላይ መመስረት እንደነበረበት ጠቁመዋል፡፡

‹‹ከአንድ አካል ለተፈጠረ የቃላት ትንኮሳ ምላሽ አልሰጣችሁም የሚል ትችት ሊኖር እንደሚችል አውቃለሁ፤ ነገር ግን የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) መግለጫም ቢሆን ስሜታዊነት ይስተዋልበታል›› ነው ያሉት ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ፡፡
‹‹የተሰጡት መግለጫዎች የሁለቱ ክልል ሕዝቦች ጉዳይ ብቻ አይደሉም፤ ጉዳዩ የኢትዮጵያ ጉዳይም ጭምር እንጂ›› ያሉት ፕሮፌሰር በየነ ድርጅቶቹ ሀገራዊና ሕዝባዊ ጉዳዮችን አስቀድመው የእርቅ፣ የሰላም እና የሀገራዊ መረጋጋት ፋና ወጊ ሆነው መገኘት እንደሚኖርባቸው መክረዋል፡፡

የሕወሃት መግለጫ እራሳቸውን ከኢህአዴግ ውጭ አድርገው እንደሚናገሩ ነው የሚመስለው ሲሉም ትዝብታቸውን አጋርተውናል፡፡ በውስጣቸው የተፈጠረውን ቅራኔ ተቀራርበው በውይይት እስከሚፈቱ ድረስ ችግራቸውን አደባባይ ማውጣት እንዳልነበረባውም ነው የተናገሩት፡፡

ሕወሃት በመግለጫው ከእናት ድርጅቱ ኢህአዴግ ውጭ ካሉ ድርጅቶች ጋር አብሮ ለመስራት ያቀረበው ጥያቄ ትዝብት ላይ የሚጥለው እና እምነት እንዳይጣልበት የሚያደርገው ነው ያሉት ፕሮፌሰር በየነ ሀገር የሁሉም ነገሮች መሞከሪያ አይደለችም እና በከፍተኛ ጥንቃቄ ኃላፊነትን መወጣት እንደሚገባ ነው የመከሩት፡፡

እንደ ፕሮፌሰር በየነ ማብራሪያ የአንድ ሃገር መሰረታዊ የፖለቲካ ህይዎት በትክክለኛ ፈር ላይ እስካልተቀመጠ ድረስ ቀሪው ሁሉ ዘበት ነው፤ እናም በመጀመሪያ በፖለቲካው ላይ መተማመን ይገባል፡፡ ህገ መንግስቱን ለማሻሻልም በህጋዊ መንገድ የተመረጠና የሕዝብ ውክልና ያለው መንግስት መመስረት ያስፈልጋል ያሉት ፖለቲከኛው፡፡ ወቅቱ የተረጋጋች ሀገር የሚገነባበትና የምርጫ ዝግጅት የሚደረግበት መሆኑንም አስገንዝበዋል፡፡

አዘጋጅ፡- ታዘብ አራጋው