July 14, 2019

የማለዳ ወግ …ክቡር ሜ/ጄኔራል መሐመድ ግን ለምን ?* ጋዜጠኛ ተመስገን የህዝብ ልጅ ነው  !* ለምን ማስፈራራት አስፈለገ  ? ጋዜጠኛ ተመስገን ክብሩ የላቀ ነው  !

 የመከላከያው ጉምቱ  ሜ/ጄኔራል መሐመድ ተሰማ  እርስዎ የጀግናው መከላከያ ሰራዊት አባል በመሆን ታላላቅ ገድል የፈጸሙ ጀግና ሊሆኑ ይችላሉ ። ለሀገርዎ በከፈሉት መስዋዕትነት ያለኝ አክብሮት ታላቅ  ነው። ከሰሞኑ የሰጡት መግለጫ ላይ የትንታጉን ጋዜጠኛ የተመስገን ደሳለኝን ስም እየጠሩ ያስተላለፉት ከሀገሪቱ ህገ መንግስት የሚጣረስ ማስፈራሪያ ግን አሳፍሮ አሸማቅቆኛል። ብዙ አልልም ፣ ግን ለምን ?  ለምንስ አይበገሬውን ጉምቱ ሀገር ወዳድ ባለ ብዕር ማስፈራራት አስፈለገ ?  ብየ እጠይቅዎታለሁ  

ተመስገንን አያውቁትም  !

================ 

 የተከበሩ የጦር ባለሟል ሜ/ጄኔራል መሐመድ የሚያውቁት አይመስለኝም ።  ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እርስዎን ከመሰለ የጦር መኮንን የላቀ ገድል የፈጸመና የሚወደድ ብዕረኛ ነው ።    ተመስገን በብዕሩ በከፈለው ብርቱ መስዋዕትነት ዛሬን እንድናይ ያደረገ ፣ ለዛሬው ለውጥ ትወልድ ይተጋ ዘንድ ያልታከተ የለውጥ ጀግናችን ነው ።  ተሜ በእነ ጌታቸው አሰፋና በእነ በረከት ስምኦን የስለላ መዋቅር እየተጋፋ ዛሬን ያቀረበ ትንታግ ጎልማሳ ነው ። ተመስገን አልሸሽም ብሎ   የህዝቡንና የሀገሩን በደል ከዳር እስከ ዳር ያሰተጋባ ትናንትም ዛሬም የተገፊዎች ድምጻችን ነው ። ተሜ ለማንም ሳያደገድግ ከጨቋኞች አፍንጫ ስር ሆኖ እውነትን ይዞ የሞገተ ስለ ኢትዮጵያ የኖረ ፣ የሚኖርና ስለ ኢትዮጵያ ግንባሩን ሳያጥፍ የሚሞት የጀግና ኢትዮጵያዊ የደም አጥንት ክፋይ መሆኑን አይዘንጉ  !  ክቡር ጄኔራል ለመሆኑ ተሜ ልገልጸው በማይቻልኝ ሁሉ ፈተና እያለፈ ስለ ኢትዮጵያ ከነ ቤተሰቡ መስዋዕት የከፈለ ኩሩ ኢትዮጵያዊ መሆኑን አያውቁምን ?መንግስትን እንዳናምን አታድርጉን  !

======================= 

ክቡር ሜ/ጄኔራል መሐመድ መንግስትን ህዝብን እንዳያምን የሚያደርግና ለሚለያይ ዛቻና ማስፈራሪያ ሊያፍሩ ይገባል ።ተሜ ትናንት በክፉው ቀን ግንባሩን ለጥይት ሰጥቶ ስለ ፕሬስ ነጻነት የከበደ መስዋዕትነት የከፈለ ወንድ ነው ። ታሰሮ ተደብድቦ ፣ በህመም ተቀስፎ ለጨቋኞች ያልተበገረ ሀገር ወዳድ እንጅ ተራ ዘላን ልኩን የማያውቅ ወንበዴ አይደለም ። በዚህ ሀገርና ህዝብ በጭንቀት ባሉበት የከፋ ሰዓት ሌላ አጄንዳ መስጠተዎን ሳስበው በምክክር የማይሰራው የለውጥ አራማጁ መንግስት አካሄድ ያስፈራኛል ።በህግ አምላክ ፣ ህግ ያክብሩ !

==================== 

 አዎ ፣ ጋዜጠኛው አይደለም ማንም ካጠፋና ጥፋት ካለ ጥፋተኛን በህግ ማዕቀፍ  መጠየቅ ሲገባ ማስፈራራትና ዛቻ አግባብ አይደለም ። መከላከያ በጠራራ ጸሐይ የሚዘርፉትን ፣ የሚገሉ የሚያፈናቅሉት ከይሲዎች ያድንልን ። በመላ ሀገሪቱ ፊደራላዊ አስተዳደር በህግ ተጠይቀው መቅረብ ያልቻሉትን ወደ ህግ ፊት ያቅርብልን  !  ክቡር ጄኔራል ጋዜጠኛ ተመስገን ህግና ስርአትን ተከትሎ ፣ የፕሬስ ፈቃድ አውጥቶ ፣ በህግና ስርአትን ስለ ሀገሩና ወገኑ ሰላም ፣  ዲሞክራሲና ፍትህ ሳይሰለች የሚዋደቅ   ኩሩ ዜጋ እንጅ እርስዎ እንዳሉት አይደለም  !

ክቡር ጄኔራል  !

ህግ ካዎቁ ህግ ያክብሩ ፣ ህግ ካላዎቁ ከህግ አዋቂዎች ህጉን ይጠይቁ … ህግ ያክብሩ  !!

በህግ ፊት ማናችንም እኩል ነን  !

ከምስጋና ጋርነቢዩ ሲራክ

ሐምሌ 7 ቀን 2011 ዓም