የጠቅላይ ቤተክህነት ምክትል ስራ አስኪያጅ ርዕሰ ደብር መሀሪ ኃይሉ

የኦሮሚያ ቤተክህነት አደራጅ ኮሚቴ የጠራውን መግለጫ መንግሥት እንዲያስቆም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ሲኖዶስ ጠየቀ።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ቤተ ክህነት በኦሮሚያ ቤተክህነት አደራጅ ኮሚቴ የተጠራውን መግለጫ እንደማያውቀውና እውቅናም እንዳልሰጠው የጠቅላይ ቤተክህነት ምክትል ስራ አስኪያጅ ርዕሰ ደብር መሀሪ ኃይሉ በዛሬው የቅዱስ መግለጫ ላይ ተናግረዋል።

በተጨማሪም የኦሮሚያ ቤተክህነት አደራጅ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሆኑት ቀሲስ በላይ መኮንን ምንም እንኳ በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስትያን ትልቅ ሃላፊነት የነበራቸው ቢሆንም በአሁኑ ወቅት ግን የኦሮሚያ ክልል እንባ ጠባቂ ቢሮ ሃላፊ መሆናቸውን የቤተክህነት የስብከተ ወንጌል እና ሃዋሪያዊ ተልእኮ መምሪያ ሃላፊ የሆኑት አቶ ሶሎሞን ቶልቻ ገልፀዋል።

ቅዱስ ሲኖዶስ የኦሮሚያ ቤተክህነትን የማቋቋም ጥያቄ መምጣት ያለበት ምእመናኑ ተወያይቶበት እንጂ በተወሰኑ ሰዎች ፍላጎት መሆን የለበትም ብሏል።

ከቀናት በፊት ቢቢሲ ያናገራቸው የአደራጅ ኮሚቴው ሰብሳቢ ቀሲስ በላይ የኦሮሚያ ቤተክህነትን የማቋቋም ጥያቄ ከማንነት እና ከቋንቋ ጋር የሚገናኝ እንደሆነ ገልፀው ነበር። ኮሚቴው ጥያቄውን ለቅዱስ ሲኖዶስ አቅርቦ ምላሽ እየጠበቀ እንደነበርም ገልፀው ነበር።