September 8, 2019

ከፖሊስ እውቅና ውጪ የሚካሄድ ሰልፍ ካለ የክልሉ ፖሊስ የህግ የበላይነትን ለማስከበር ተገቢውን እርምጃ እንደሚወስድ ኮሚሽነሩ አሳስበዋል።

(ኢፕድ)

በኦሮሚያ የተጠየቀም ሆነ የተፈቀደ ሰልፍ አለመኖሩን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ።
የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ከፍያለው ተፈራ ዛሬ በኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት በአፋን ኦሮሞ ለሚታተመው በሪሳ ጋዜጣ በክልሉ በየትኛውም አካባቢ የቀረበ የሰልፍ ጥያቄም ሆነ የተፈቀደ ሰልፍ አለመኖሩን ተናግረዋል።

በማንኛውም ጉዳዮች ዙሪያ መንግስት ከሚመለከታቸው አካሎች ጋር እየተወያየ መፈትሄ እንዲያገኙ ያደርጋል እንጂ ሰልፍ የሚያስወጣ ምንም ዓይነት ጉዳይ አይኖርም ብለዋል ኮሚሽነሩ። በመሆኑም ህብረተሰቡ በማህበራዊ ሚዲያዎች የሚናፈሱ አሉባልታዎችን ተከትሎ እንዳይሳሳት ኮሚሽነሩ አበክረው አሳስበዋል።

ለሁሉም የክልሉ ዞኖችና ከተሞች አቅጣጫ የተሰጠ መሆኑን የገለጹት ኮሚሽነሩ ከፖሊስ እውቅና ውጪ የሚካሄድ ሰልፍ ካለ የክልሉ ፖሊስ የህግ የበላይነትን ለማስከበር ተገቢውን እርምጃ እንደሚወስድ ኮሚሽነሩ አሳስበዋል።