(ኢዜአ) በተለያዩ ወገኖች የሚነሱ የሃሳብ ልዩነቶች አገራዊ ጠቀሜታ አንዲኖራቸው በማድርግ የሁሉም የጋራ የሆነውን ሰላም፣ አንድነት፣ ልማትና እድገት ማጠናከር እንደሚገባ ተገለጸ

“የብሔራዊ ኩራት ቀን” በተለይ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ዛሬ ከ250 ሺህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች በታደሙበት በተለያዩ ትእይንቶች ተከብሯል።
ኢዜአ ያነጋገራቸው የበአሉ ታዳሚዎች እንደገለጹት፤ በየትኛውም ስፍራ የሚኖሩ ዜጎች እንደ መልካቸው ሁሉ የሚያነሱት ሀሳብና አመለካከት ሊለያይ ይችላል።
በዚህም ከተለያዩ ወገኖች የሚነሱ የሃሳብና የአመለካከት ልዩነቶች በተለያዩ አጋጣሚዎች አለመግባባትና ግጭቶችን ሊፈጥሩ ይችላሉ።
ይሁንና የሃሳብ ልዩነቶች ይበልጥ አንድነትን የሚያጠናክሩ እንጂ የሚያለያዩና በህዝቦች መካከል ቁርሾ የሚፈጥሩ መሆን እንደሌለባቸው አስተያየት ሰጭዎቹ ይናገራሉ።
በመሆኑም ልዩነቶችን በማቻቻል ብሎም አገርን የሚለውጡ ሃሳቦችን በማቀናጀትና ወደ ሚበጅ አላማ በማምጣት የአገሪቱን ሰላምና አንድነት ማስጠበቅ ያስፈልጋል ብለዋል።
ኢትዮጵያ በፊት የምትታወቅበት የመከባበርና የመፈቃቀር ብሎም አንድ የመሆን ባህልና እሰቶቿ ተጠብቀው እንዲቆዩም ህዝቡ በጋራ መቆም አለበት ብለዋል።
“ኢትዮጵያ” የሚለውን ስም በማስቀደም ሁሉም ህብረተሰብ ለአገሩ ቅድሚያ መስጠት እንዳለበትም አሳስበዋል።
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አዘጋጅነት በመስቀል አደባባይ በተከናወነው ብሔራዊ የኩራት ቀን ምክትል ከንቲባ ኢንጂኒየር ታከለ ኡማ በክብር እንግድነት በመገኘት ንግግር አድርገዋል።
የመከላከያና የፖሊስ አባላት፣ ተማሪዎች፣ ወጣቶች፣ አባት አርበኞች፣ አንጋፋ አትሌሎችና ሌሎችም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችም ተገኝተው እለቱን አድምቀውታል።
ብሄራዊ የኩራት ቀን “አዲስ አበባ ቤቴ፤ ኢትዮጵያዊነት ኩራቴ” በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ ተከብሯል።