
ከሰሞኑ በሰዎች የመነገድ፣ በሕገ-ወጥ መንገድ ድንበር ማሻገር እና ህገ-ወጥ የውጭ አገር የሥራ ስምሪት ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ረቂቅ አዋጅ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበ ሲሆን፤ የሞት ቅጣትም እንደተካተተበት የጠቅላይ አቃቤ ህግ አስታውቋል።
ረቂቅ ህጉ ብዙ የቅጣት ድንጋጌዎች የተካተቱበት ሲሆን ከእስራት ጀምሮ እስከ ሞት ቅጣትም የሚያደርስ ነው።
•በተሻሻለው የወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ህግ ረቂቅ ጥፋተኛና አቃቤ ህግ ይደራደራሉ
•“መንግሥት የዋጋ ንረቱን ለመቆጣጠር መሰረታዊ የምግብ ሸቀጦችን ያስገባል”ፕሬዚዳንት ሣህለወርቅ
ኢትዮጵያ በተቀበለቻቸው የዓለም አቀፍ ድንጋጌዎችም ቢሆን የሰዎች ህገወጥ ዝውውር እንዲሁም በሰዎች መነገድ ከባድ ወንጀል መሆኑን የጠቀሱት የጠቅላይ አቃቤ ጽህፈት ቤት ቃል አቀባይ አቶ ዝናቡ ቱኑ ይህንንም ታሳቢ በማድረግ ህጉ እንደተረቀቀ ይናገራሉ።
የተሻለ ህይወትን ፍለጋ በአሰቃቂ ሁኔታ ብዙዎች ባህር ውስጥ ሰምጠዋል፣ የሰውነት አካላቸው ተሽጧል፣ ምኞታቸውን ሳያሳኩ ለሞት ተዳርገዋል፣ ሌሎችም ለማይሽር አካላዊና ህሊናዊ ጠባሳ ተዳርገዋል። በተለያዩ ሀገራትም ከደረሱ በኋላ የከፋ ህይወት የሚያጋጥማቸው ብዙ ናቸው።
በተለይም ወደ አረብ አገር የሚሄዱት በአሰሪዎች መደብደብ፣ መደፈር፣ የጉልበት ብዝበዛ፣ ክፍያ መከልከልና ሌሎችም አስከፊ ስቃዮች የበርካታ ኢትዮጵያዊያን እጣ ነው።
በዚህም ሁኔታ ማህበረሰቡ ለእንግልት፣ ስቃይ ሲከፋም ሞትን እየተጋፈጠ ሲሆን ይህንንም ለመቅረፍ ጠንከር ያለ መፍትሄ እንደሚያስፈልግ አቶ ዝናቡ ቱኑ ለቢቢሲ ገልፀዋል።
ይህንን ለመቆጣጠር ጊዜ የሚሰጠው ጉዳይ ባለመሆኑና በዚህ ወንጀል ተግባር የሚሳተፉ አካላት ላይ ተገቢና ጠንከር ያለ ቅጣትን አስፈላጊ መሆኑን ታሳቢ በማድረግ ረቂቁ እንደወጣ አቶ ዝናቡ ጠቅሰው በተለያዩ ባለድርሻ አካላት ውይይት እየተደረገበት እንደሆነም ይናገራሉ።
•በኢትዮጵያ አየር መንገድ አደጋ የሞቱ ሰዎች አጽም ለቤተሰቦቻቸው እየተሰጠ ነው
•“ሰልፍ የዜጎች መሰረታዊ መብት ነው” መስፍን ነጋሽ
ጉዳዩ አስከፊነትና አሳሳቢ ከመሆኑ አንፃር መንግሥትም የዜጎቹን ደህንነት የመጠበቅ ኃላፊትም ስላለበት ህጉ እንደተረቀቀ አፅንኦት በመስጠት ይናገራሉ።
ከዚህ ቀደምም ችግሩን ለመቅረፍ የተለያዩ ሥራዎች እንደተስሩ ጠቅሰው በዋነኝነት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ ከተጓዙባቸው ሃገራት በችግር እንዲሁም በእስር ላይ ያሉ ዜጎችን ለመመለስ የተደረገው ጥረትን እንደምሳሌ ይጠቅሳሉ።
ከሰሞኑ ፕሬዝዳንት ሣህለ ወርቅ ዘውዴ፣ የሕዝብ ተወካዮችና የፌደሬሽን ምክር ቤት የጋራ ስብሰባ የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት ላይ ባደረጉት ንግግር፤ በ2011 ዓ.ም ብቻ በተለያዩ ሀገራት በእስር እና በእንግልት ላይ የነበሩ ከ90 ሺህ በላይ ዜጎቻችን ወደ ሀገራቸው ተመልሰዋል ብለዋል።
ዜጎችን የመመለስ ሥራ የበለጠ ማጠናከር እንዳለ ሆኖ ህገወጥ ደላሎችም ከሥራቸው እንዲታቀቡ የማያዳግም እርምጃ መወሰድ እንዳለበት ይናገራሉ።
ከዚህ ቀደምም ያለ ህገወጥ ዝውውርን ለመከላከል የቀደመ ህግ ቢኖርም የተወሰኑ ክፍተቶች በመኖራቸው ይህ ማሻሻያ እንዳስፈለገው የሚናገሩት አቶ ዝናቡ አዳዲስ ፅንሰ ሃሳቦችም ተካቶባቸዋል