December 3, 2019 – Abebe Bersamo

በቅርቡ አቶ ለማ መገርሳ የብልጽኛ ፓርቲን እንደማይቀበሉ የገለጽበት ከአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ ጋር ያደረጉት ቃለ ምልልስ ብዙዎችን እያነጋገረ ነው፡፡ አቶ ለማ የተናገሩትን አቶ በቀለ ገርባ ወይንም ጃዋር መሀመድ ቢናገሩት ፣ ሁሎ ሲናገሩት የምንሰማው ስለሆነ ንቀነው ነበር የምናልፈው፡፡ ሆኖም ግ ን በሕዝብ በጣም ተወዳጅ ከሆኑት ከአቶ ለማ ኝ ይሄን ስንሰማ ብዙዎቻችን ማዘናችን አልቀረም፡፡
አቶ ለማ “ የኦሮሞ ህዝብ ቆጥሮ የሰጠን አደራ አለ፡፡ የኦሮሞን ጥያቄ መጀመሪያ ማስፈጸም አለብን፡፡ የኦሮሞ ጥያቄ ደግሞ ሊያስፈጽም የሚችለው ኦዴፓ ነው” የሚል መልስ በመስጠት ነበር ከነ ዶ/ር አብይ ጋር ያላቸውን ልዩነት በይፋ የገለጹት፡፡
አቶ ለማ ያልተመለሰ የኦሮሞ ጥያቄ የሚሉት ምንድን ነው ? ያንን በቃለ ምልልሳቸው ግልጽ አላደረጉም፡፡ የኦሮሞ ማህበረሰብ መሰረታዊ ጥያቄዎች የሰላም፣ የፍትህ፣ የእክሉነትና የልማት ጥያቄዎች ናቸው የሚል እምነት ነው ያለኝ፡፡ እነዚህም ጥያቄዎች ደግሞ የኦሮሞ ማህበረሰብ ብቻ ሳይሆን የሁሉም ኢትዮጵያዉያን ጥያቄዎች ናቸው፡፡
ይመስለኛል አቶ ለማ መገርሳና በርካታ የኦሮሞ ብሄረተኞች “የኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄ አልተከበረም” ሲሉ አንዱ የሚያነሱት የኦሮሞ ባህል፣ ቋንቋ አልተስፋፋም የሚል ነው፡፡ ከዚህም ጋር ተያይዞ “ኦሮምኛ የፌዴራል ቋንቋ ለምን አልሆነም” ይላሉ፡፡ እስቲ ይሄን ቅሬታቸው ምን ያህል ሚዛናዊ እንደሆነ እንፈትሸው፡
- በአዲስ አበባ ፣ ስታዲየም ፊት ለፊት፣ ብዙ ፎቆችን የያዘ የኦሮሞ ባህል መዓከል አለ፡፡ በዚህ ባህል ማእክል የኦሮሞን ባህልና ስርዓት የሚገልጹ የተለያዩ ኤግዚቢሽኖች ፣ ስብሰባዎች፣ ሴሚናሮች …ይደረጋሉ፡፡
- ለሁለት ቀናት የከተማዋን ዋና ዋና መንገዶች በመዝጋት፣ ሌላው ማህበረሰብ ቤቱ እንዲቀመጥ ተደርጎ፣ ኢሬቻን በአዲስ አበባ ያለ ምንም ችግር ተከብሯል፡፡
- በኦሮሞ ክልል መንግስት ባጀት በኦሮምኛ(በላቲን) የሚያስተምሩ አራት ትምህርት ቤቶች እንዲከፈቱ ተደርጓል፡፡ የአዲስ አበባ መስተዳደር መሬት ሰጥቶ፣ ትምህርት ቤቶች ከሁለት አመታት በፊት ተገንብተው በኦሮምኛ ትምህርት እየሰጡ ነው፡፡ ከ120 በላይ ሌሎች ትምህርት ቤቶች፣ኦሮምኛ እንደ አንድ ትምህርት እየተሰጠ ነው፡፡
- የዶ/ር አብይ አስተዳደር ኦሮምኛ ብቻ ሳይሆን ትግሪኛ፣ ሶማሌኛ፣ አፋርኛና ሌሎችም ከአማርኛ ጋር የፌዴራል የስራ ቋንቋ ለማድረግ እቅድ እንዳለው በይፋ ገልጿል፡፡ያ ማለት ጥያቄውን ተግባራዊ ለማድረግ እየተሰራ ነው ማለት ነው፡፡
በአዲስ አበባ ብቻ አይደለም፡፡ ከተፈለገም በባህር ዳር፣ በጂጂጋ፣ በመቀሌ ..የኦሮሞና ባህልና ቅርስ የሚያስተዋወቁ ማእከላትን፣ በኦሮምኛ የሚያስተምሩ ት/ቤቶች ቢከፍቱ፣ ኢሬቻን ሆነ ሌላ ማንኛውም የኦሮሞ በዓላትን እናክብር ቢሉ የሚቃወማቸው ይኖራል ብዬ አላስብም፡፡፡ በአሁኑ ወቅት ኦሮሞዎች ባህላቸውን ቋንቋቸውን በማስፋፍት ረገድ ምንም አይነት መሰናክል የለባቸውም፡፡ ለማስታወስ ያህል እንደውም፣ ከአንድ አመት በፊት የቀድሞ የአማራ ክልል ረእሰ መስተዳደር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በባህር ዳር የኦሮሞ ባህል ማእከል ግንባታ መሬት ለመስጠት ፍቃደኛ እንደነበሩም ተገልጾ ነበር፡፡
አቶ ለማ “የኦሮሞ ማህበረሰብ የልማት ተጠቃሚ አይደለም፣ የስራ አጥነት ችግር አልተፈታም፡፡ ሰላም የለም” በሚል ከሆነ ደግሞ የኦሮሞ ጥያቄ አልተመለሰም የሚሉት ተገቢና አስፈላጊ ጥያቄ ነው የሚሆነው፡ ሆኖም ግን ሁለት ነጥቦችን ላስቀምጥ፡፡
አንደኛ፣ በክልሉ ሰላም እንዲጠፋ ያደረጉት ራሱ ኦዴፓና እንደ ኦነግ ያሉ ድርጅቶች ናቸው፡፡ ወለጋ፣ ጉጂና ቦረና የታመሱት በኦሮሞ ድርጅቶች ነው፡፡ በባሌ፣ ሃረርጌና አርሲ የሩዋንዳ አይነት እልቂት ያየነው በጅዋር ተከታይ ቄሮዎች ነው፡፡ የኦሮሞ ማህበረሰብ የሰላም ጥያቄ እንዲከበር በክልሉ ያሉ እንደ ኦነግ ያሉና፣ ተደራጅተው በሕዝብ ላይ ሽብር የሚፈጥሩ የጃዋር ተከታይ ቄሮዎች አደብ ማስገዛት አስፈላጊ ነው፡፡ ይሄንንም በውስጡ ኦነጋዊያንና ጃዋራዉያን ስለተሰገሰጉ ኦህዴድ/ኦዴፓ ያንን ማድረግ አልቻለም፡፡ የብልጽግና ፓርቲ መምጣት ግን፣ ሕኝ የማስከበር ውሳኔዎችን በተቀላጠፈ መልኩ ማስፈጸም የሚችልበትን አዲስ ሁኔታ ሊፈጥር ይችላል፡፡ ስለሆነም የኦሮሞ ማህበረሰብን የሰላም ጥያቄ ለመመለስ፣ አቶ ለማ እንዳሉት ኦዴፓን ማስቀጠል ሳይሆን የሚያስፈልገው፣ ኦዴፓን ማፍረስ ነው፡፡ ያም ነው የሆነው፡፡
ሁለተኛ፣ በልማትና ለወጣቶች የስራ እድልን በመፍጠር አኳያ የኦሮሞ ማህበረሰብ ያለውን ጥያቄ ለመመለስ ፣ ንግድ፣ ቱሪዝም፣ ኢንቨስትመንት ….. የመሳሰሉት መስፍፋት አለባቸው፡፡ ባለፉት 2 አመታት ዜጎች እንኳን በኦሮሞ ክልል ኢንቨስት ሊያደርጉ፣ እንደውም ያሉትም ለቀው እየወጡ ነው፡፡ ከመቀሌ፣ አዋሳ ፣ ባህር ዳር .ዚ..ይበልጡ የነበሩ እንደ ነቀምቴ፣ መቱ፣ አሰላ ..ያሉ ከተሞች እየሞቱ ነው፡፡ ዜጎች እንኳን እዚያ ለመኖርና ኢንቨስት ለማድረግ ቀርቶ፣ በኦሮሞ ክልል ለማለፍ እንኳን የሚፈሩበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ከዚህም የተነሳ የኦሮሞ ክልል ከተሞች በከተማነት ከማደግ የገበሬ ማህበር መንደሮች እየሆኑ ነው፡፡ ወጣቶችም በመቱ፣ ነቀምቴ፣ ጨርጨር፣ ሻምቦ …ስራ ስለማያገኙ ስራ ወደ ሚገኝባቸው ወደ አዲስ አበባና አዲስ አበባ ዙሪያ ለመሄድ እየተገደዱ ነው፡፡ የሚያሳዝነው ደግሞ በዚያም ሂደው ፣ አማርኛ ማንበብና መጻፍ ስለማይችሉ ስራ ማግኝት አልቻሉም፡፡
የኦሮሞ ማህበረሰብ የልማት ተጠቃሚ እንዳይሆን፣ የኦሮሞ ክልል ለኢንቨስተሮች ምቹ እንዳይሆን፣ የኦሮሞ ልጆች ስራ በሚገኝባቸው አካባቢዎች ስራ እንዲያገኙ የሚረዳቸውን አማርኛ ማንበብና መጻፍ እንዳይችሉ ያደረገው፣ አቶ ለማ መገርሳ የኦሮሞ ጥይቄ እንዲመለስ መፍረስ የለበትም ያሉት ኦህዴድ/ኦዴፓ ነው፡፡ኦህዴድ/ኦዴፓ የኦሮሞ ማህበረሰብን በዘላቂነት የሚጠቅም፣ የህዝቡን መሰረታዊ ጥያቄዎች የሚመለስ ስራ አልሰራም፡፡ ኦሮሞውን ትልቅ የማህበራዊ፣ የፖለቲካዊና የኢኮኖሚያዊ አዘቅት ውስጥ ነው የዘፈቁት፡፡የኦሮሞ ማህበረሰብ ከሌሎች ማህበረሰባት ጋር እንዲጋጭ ነው ያደረጉት፡፡
የኦሮሞ ማህበረሰብ ጥያቄዎች ከሌሎች ማህበረሰባት ጥያቄዎች ጋር ተመሳሳይ ስለሆኑ፣ በአንድ አገር አቀፍ ድርጅት ውስጥ ፣ አንዱ ከሌላው ሳይበልጥ፣ አንዱ የተለየ ልዩ ጥቅም ሳይሰጠው፣ በእኩልነት የሚመለሱበትን ሁኔታ መፈጠሩ አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን የኦሮሞ ማህበረሰብን ከድህነት የሚያወጣ ነው፡፡ ኦሮሞው ከሌላው ጋር እጅ ለ እጅ ሲያያዝ እንጂ ከሌላው ጋር በተቃርኖ ሲቆም ተጎጂ ነው የሚሆነው፡፡