ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አህመድ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት እየተነሱላቸው ላሉ ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ላይ ይገኛሉ።
ለጠቅላይ ሚንስትሩ ከተነሱላቸው ጥያቄዎች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል።
ስለ ታገቱት የደምቢ ዶሎ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች
ተማሪዎቹን ያገተው ማነው?፣ የታገቱት ተማሪዎች ተለቀዋል ተብሏል፤ የት ነው የሚገኙት? ማነው ያገታቸው? የሚለው ጥያቄ ይገኝበታል።
ሕግ ወጥ የመሬት ወረራ፣ ታዳጊዎችን አግቶ ገንዘብ መጠየቅ
ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ታዳጊዎችን አግቶ ገንዘብ የመጠየቅ እና ገንዘቡ የማይከፈል ከሆነ የመግደል እርምጃ ተስተውሏል። ይህን አይነት ሕገ–ወጥነት ለመግታት ምን እየተደረገ ነው?
የጸጥታ ችግር
በምዕራብ ኦሮሚያ፣ ጉጂ እና ቦረና አካባቢ ዘላቂ ሰላም ለማስፈን መንግሥት እንዴት ተዘጋጅቷል?
ምርጫ 2012
ምርጫ በነሐሴ፤ በክረምት ወር እንዲካሄድ መወሰኑ ምን ያህል ትክክለኛ ነው?
የ‘ክልል እንሁን‘ ጥያቄ
በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦች እና ሕዝቦች መካከል በርካታ ብሄረሰቦች የክልል እንሁን ጥያቄ እያነሱ እንደሆነ በማስታወስ፤ የብሄረሰቦች ጥያቄ ምላሽ ማግኘት ያለበት በሕገ–መንግሥቱ መሠረት እንጂ ሌላ ጥናት ማድረግ አስፋለጊነት የለውም።
የትግራይ ተወላጆችን ማግለል
ወደ ትግራይ ክልል ሊያመሩ የነበረ የቻይና ልዑካን ቡድን ወደ ትግራይ እንዳይሄድ ተከልክሏል፤ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሚገኙ የትግራይ ክልል ተወላጆችም ከሥራ ተገለዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ
የታላቁ ህዳሴ ግድብን በሚመለከት ከሰሞኑ የተደረገው ውይይት ይዘት ምን እንደሆነ እና የተደረሰበትን ደረጃ ጠቅላይ ሚንስትሩ እንዲያብራሩ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል።
የጠቅላይ ሚንስትሩ ምላሽ
ጠቅላይ ሚንስትሩ ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽ እና ማብራሪያ ከመስጠታቸው በፊት፤ ወደ ሥልጣን ከመጡ ወዲህ መንግሥታቸው ምን አይነት ችግር ገጥሞት እንደነበረ እና ችግሮቹን ለመፍታት እየመጣበት ያለውን መንገድ አስረድተዋል። ከእርሳቸው በፊት የነበረው መንግሥት በውስብስብ ‘ኔትወርክ” ተይዞ እንደነበረ እና እርሳቸውም ወደ ሥልጣን ከመጡ ወዲህ ይህን ‘ኔትወርክ ለመበጣጠስ‘ ጥረት ሲደረግ መቆየቱን፤ ይሁን እንጂ ይህ ለመንግሥት ከፍተኛ ፈተና ሆኖ መቆየቱን ጠቁመዋል።
“እስከታችኛው የመንግሥት እርከን ድረስ የተዘረጋው ይህ ኔትወርክ፤ ሲፈለግ ማንም እንዳይንቀሳቀስ የማድረግ አቅም አለው” ብለዋል።
• የግዙፉ ግድብ ግንባታ፡ የኢትዮጵያና ግብፅ ቅራኔ
“ይህ ውስብስብ እና ጥልፍልፍ ኔትወርክን መገንዘብ ችግር ነበር። ኔትወርኩን መበጣጠስ መከራ ነው። ይህን ኔትወርክ ማግኘት እና መበጠስ ስንጀምር ደግሞ ኔትወርኩ እስከ ታችኛው የመንግሥት እርከን ድረስ ትስስር እንዳለው ተረድተናል” ብለዋል።
“ሕዝቡ እንዲረዳ የምፈልገው አሁን ያለንበት ጊዜ የመጨረሻ ከፍተኛ ፈተና የተሞላ ወቅት መሆኑን ነው።” ሲሉ ተናግረዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ “የሴራ ፤ የደባ ፖለቲካውን ማስቆም ፈተና ሆኗል፤ ነገር ግን ኢትዮጵያን የምናስቀጥል መሆኑን ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ። ይህ የሚታለፍ ፈተና ነው።” ሲሉም ተደምጠዋል።
የደምቢ ዶሎ እገታ
“ቦኮ ሃራም ሰው ሲያግት ኃላፊነት እወስዳለሁ ብሎ ያውጃል፤ እዚህ ግን እስካሁን ኃላፊነት እወስዳለሁ ያለ የለም” በማለት እገታውን ማን እንዳከናወነ እንደማይታወቅ ግልፅ አድርገዋል።
በውል የማይታወቁ ግለሰቦች አሉ። ተጎድተዋል እንዳይባል በእገታው የተጎዳ የለም። ተማሪ ያልሆኑ፤ መኖሪያቸው ሌላ ቦታ የሆኑ ተቀላቅለው አሉ።
ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር፣ የሰላም ሚንስትር እንዲሁም ከሁሉም የጸጥታ አካላት የተውጣጣ ኮሚቴ ምርመራ ላይ ነው፤ ምርመራ ሲጨርሱ የሚደርሱበትን ግልጽ ያደርጋል።
• የታገቱት ተማሪዎች፡ የቤተሰብ ሰቀቀንና የመንግሥት ዝምታ
“ባልተሟላ መረጃ መግለጫ መስጠት ስላልነበረብን ነው መረጃ ሳንሰጥ የቆየነው” በማለት ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ መንግሥት በጉዳዩ ላይ ምንም ሳይል የቆየበትን ምክንያት ለማብራራት ሞክረዋል።
በምዕራብ ወለጋ እና በጉጂ ስላለው የጸጥታ ችግር
በጉጂ ተከስቶ የነበረው የጸጥታ ችግር እየተቀረፈ እንደሚገኝ በመግለጽ ያለው የጸጥታ ችግር አስጊ የሚባል እንዳልሆነ ገልፀዋል።
በምዕራብ ወለጋ ያለውን የጸጥታ ችግር ለመፍታት ግን ብዙ ሥራ እንደሚጠይቅ ተናግረዋል።
“ሁሌም መፍትሄው ሰላማዊ ነው። ነገር ግን ለዲሞክራሲ እጇን በከፈተች አንድ አገር ሁለት የታጠቀ ኃይል ሊኖር አይችልም” ያሉ ጠቅላይ ሚንስትሩ፤ “አሁን ላይ መንግሥትን በሁለቱም ጫፍ ጫና ውስጥ የሚስገባ ሥራ ነው እየተሠራ ያለው” ብለዋል።
ጠቅላይ ሚንስትሩ በአንድ በኩል መንግሥት ሰላም የማስከበር ሥራን ለመስራት ጸጥታ አስከባሪ ወደ ሥፍራው ሲያሰማራ “‘ኦፕሬሽን ወሰዳችሁ‘ እንባላለን“፤ በሌላ በኩል ደግሞ መንግሥት በምዕራብ ወለጋ ሕግ የማስከበር ሥራን እየሰራ አይደለም እየተባለ ይወቀሳል ብለዋል።
በትግራይ እና በፌደራል መንግሥት መካከል ስላለው ግነኙነት
ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ የትግራይ ክልል ተወላጆች በማንነታቸው እየተለዩ ከሥልጣን እንዲነሱ ተደርገዋል የተባለው ስህተት ነው ብለዋል።
“ከ10 በላይ ሚንስትር ዲኤታዎች አሉ፤ አንድም አልተነሳም፤ ሌላ ሚንስትር እና የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈጉባኤም አልተነሱም። . . . የትግራይን ሕዝብ ያገለለ መንግሥት በኢትዮጵያ ሊኖር አይችልም። እኛም እንዲሆን አንፈቅድም” ብለዋል።
ጠቅላይ ሚንስትሩ አክለውም፤ “ብልጽግና የፈለገውን ማድረግ ይችላል። ጠቅላይ ሚንስትሩ የራሱን ካቢኔ መርጦ ማቋቋም ይችላል። ስትፈልጉ ጠቅላይ ሚንስትሩን አንሱ” ብለዋል።
ህወሃት በፌደራል መንግሥቱ ተገፍቷል መባሉን ያስተባበሉት ጠቅላይ ሚንስትር “ህውሃት አልተገፋም፤ ወደፊት አብረን ልንሰራ እንችላለን” ብለዋል።
ምርጫ 2012
ምርጫው በክረምት መካሄዱ ትክክል አይደለም ለሚለው ቅሬታ፤ ምክር ቤቱ “ምርጫ ቦርድ ተጠሪነቱ ለምክር ቤቱ እንደመሆኑ ቦርዱን ጠርታችሁ አናግሩ” ሲሉ ጠቅላይ ሚንስትሩ ምላሽ ሰጥተዋል።
“መንግሥት ከመመስረቱ አንድ ወር ቀድሞ ምርጫ መካሄድ አለበት። ይህ ሕገ–መንግሥታዊ ነው። ግንቦት ወይስ ነሐሴ የሚለውን ምርጫ ቦርድን ጠይቁ። ሥልጣኑ የእናንተ ስለሆነ” ያሉ ሲሆን፤ መንግሥት ከመመስረቱ አንድ ወር ቀደም ብሎ ምርጫ መካሄድ አለበት ብለዋል።
የክልል እና የዞን እንሁን ጥያቄዎች
ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ ክልል የመሆን እና የልማት ጥያቄ አብሮ የሚሄዱ ጥያቄዎች አይደሉም ብለዋል። “ክልል፣ ዞን እና ወረዳ በበዛ ቁጥር ደሞዝተኛ ነው የሚበዛው እንጂ የሕዝብ የልማት ጥያቄ አይደለም የሚመለሰው” ብለዋል።
ጠቅላይ ሚንስትሩ ጨምረውም የሕገ መንግሥቱን አንቀጽ 47 በመጥቀስ ሕገ–መንግሥቱ በራሱ ይህን በማስፈጸም ረገድ ክፍተት መኖሩን ጠቁመዋል።
በተጨማሪም ክልል እንሁን ጥያቄዎችን በአሁኑ ሰዓት ምርጫ ቦርድ እንዲያስፈጽም መጠበቅ ስህተት ነው ብለዋል።
“ምርጫ ቦርድ አሁን ላይ ይህን ሁሉ ማስፈጸም ይችላል ብሎ መጠበቁ ትክክል አይሆንም“
በተጨማሪም ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ ኢቲዮ ቴሌኮም፣ መብራት ኃይል እና ሌሎች የመንግሥት ተቋማት ያስመዘገቡትን ውጤት ተናግረዋል።
ኢትዮ ቴሌኮም 8 ሚሊዮን ተጨማሪ ደንበኞችን መመዝገቡ እና ለመንግሥት ከፍተኛ ገቢ ማስገኘቱን ጠቅሰዋል።
መብራት ኃይልም ብዙ ስኬቶችን ማስመዝገቡን ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም በመብራት ኃይል እጥረት ለተጠቃሚዎች በፈረቃ አገልግሎት እንደሚሰጥ አስታውሰው ዘንድሮ ግን ተጨማሪ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ በሌለበት የኤሌክትሪክ ኃይል “በአስተዳደር ብቃት ነው ያለ ፈረቃ እንዲሠራጭ እየተደረገ ያለው” ብለዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ
ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ ባለፉት 8 ዓመታት በሦስቱ አገራት መካከል ድርድር ሲካሄድ መቆየቱን አስታውሰዋል።
የአሜሪካ መንግሥት እና ዓለም ባንክ ‘ለማደራደር‘ ጥያቄ አቅርበው ‘ሲያደራድሩ‘ ቆይተዋል ብለዋል ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ።
“ለአሜሪካ እና ዓለም ባንክ ምስጋና ማቅረብ የሚያስፈልገው፤ በሚያውቁን እና አቅም ባላቸው ፊት ስንነጋገር መስማማት ጀምረናል” ብለዋል።
ሦስቱም አገራት የመጨረሻ የተባለለትን ስምምነት ለመፈረም ከተዘጋጁ በኋላ፤ ጠቅላይ ሚንስትሩ ስምምነቱ ከመፈረሙ በፊት “ዝርዝር ዕይታ እና ውይይት ስለሚያስፈልገው [እንዳይፈረም] የሚል አቅጣጫ በመስጠቴ ፊርማው ቆይቷል” ማለታቸውን ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ ተናግረዋል።
በዚህም ፕሬዝደንት ትራምፕ፣ የዓለም ባንክ እና የአሜሪካ ፋይናንስ ሚንስትሩ ጋር በስልክ ተገናኝተው ረዘም ላለ ጊዜ መነጋገራቸውን ተናግረዋል።
“እስካሁን የነበርነው ጠቅላይ ሚንስትሮች በግድቡ ዙሪያ የአቋም ልዩነት አላሳየንም” ያሉ ሲሆን፤ “ግብጽን ሳይጎዳ ኢትዮጵያን ተጠቃሚ በሚያደርግ መንገድ እንሄዳለን። በዚህ ላይ የአሜሪካም ሆነ የዓለም ባንክ አቋም ይሄ ነው። ይህ የሚሆን ከሆነ ብዙ እርዳታ ቃል ተገብቷል” ብለዋል።
“የግድቡ መጠን ሳይሆን አሁን ላይ አሞላል እና እንዴት ይለቀቅ የሚባለው ጉዳይ ላይ ተደርሷል። ሁለቱ ሚንስትሮች [የውሃ፣ መስኖ እና ኢነርጅ ሚንስትር እና የውጪ ጉዳይ ሚንስትር] ያደረጉትን ማድነቅ እፈልጋለሁ” ብለዋል ጠቅላይ ሚንስትሩ።
“ከየትኛውም መንግሥታት ጋር በሁለትዮሽ ግንኙነት ላይ ስንወያይ ቀድሞ የሚመጣው የአባይ ጉዳይ ነው” ያሉት ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ ድርድሩ በአጭር ጊዜ ይቋጫል ብለው እንደሚያስቡ ተናግረዋል።