July 29, 2020

የአማራ ሕዝብ እንደ ጨቋኝ ሆኖ የተባለው ትርክትን የማንቀበለው ለፖለቲካ ትርፍ ብለን ዓይደለም፤ በተጨባጭ ትርክቱ የተሳሳተ ስለሆነ ነው”

ሙስታፋ ዖመር፤ የሶማሌ ክልል ፕሬዝደንት

የተወለድኩባት፤ ያሳደገችኝ፤ ዓለምን ስዘዋወር የምታኮራኝና እኔ “ኢትዮጵያዊ ነኝ” ስል ከችሌ እስከ ኢንዶኔዢያ፤ ከኤኳዶር

እስከ ደቡብ ኮርያ፤ ከማላየዢያ እስከ ተርኪ ወዘተ እኔነቴንና ማንነቴን በማያሻማ ደረጃ ተቀባይነት ያበረከተችኝ ኢትዮጵያ በጠባብ ብሄርተኞች፤ በብሄርና በሞሃቢስት ጽንፈኞች በተቀነባበረ ሴራ ልክ ዩጎስላቭያን እንድትሆን እልቂትና ሁከት ሲካሄድባት አያለሁ። “ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር” የሚለው የተቀደሰ መፈክር ተቀይሮ “ዳውን ዳውን ኢትዮጵያ” ፤ አሁን በተጨማሪ በ“ዳውን ዳውን  ለማ፤ ዳውን ዳውን ዐብይ” በሚሉ “የቄሮዎች፤ የወያኔዎች፤ ዮኦነግ ሸኔዎች እና የሌሎች ሽብርተኞችና አሸባሪዎች መፈክሮች ተተክተዋል። እነዚኅ ክስተቶች ተመሳሳይ የሚያደርጋቸው አስኳል ጉዳይ ምንድን ነው? የሚለውን ጥያቄ እያንዳንዳችሁ መልሱት።

ዋናው ተግዳሮት ምንድን ነው?

ህወሕትና ሌሎች የዘውግ ልሂቃን ጸንሰውና አቀናጅተው በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የጫኑት የብሄርና የቋንቋ መለያ ሕገ መንግሥት እና ሕዝቡን ከሕዝብ ያናከሰው የክልል አስተዳደር መሰረታዊ፤ ተቋማዊና መዋቅራዊ ተግዳሮቶችን ፈጥሯል። ይህ የጥቂት ልሂቃን አገዛዝ በተደጋጋሚ ባሳያቸው እልቂቶች ሲገመገም፤ ከህዝቡ የዜግነት መብት፤ ያለ ምንም ስጋት በየትኛውም ኢትዮጵያ የመኖር ፍላጎትና መብት፤ ከአገራችን ሉዐላዊነትና ደህንነት ጋር ሊመጣጣን የማይችል ስርዓት ነው። ይህ ስርዐተመንግሥት ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን አይመጥንም።

ሕገ መንግሥቱና የክልሉ አስተዳደር ካልተቀየሩ በስተቀር፤ ችግሩን እንደ እሳት አደጋ ብቅ ጥልቅ ሲል ከመከላከል ባሻገር ሰላምና እርጋታ በዘላቂነት የሚፈጠርበት ሁኔታ ለኔ አይታየኝም። ዜጎችን በዘውጋቸውና በኃይማኖታቸው እየለዩና እያደኑ መጨፍጨፉ አያቆምም። የውጭ ጣልቃገብነት አይገታም። በተጨማሪ፤ መልካም አስተዳደር በሌለበት ሁኒታ ፍትሃዊና ዘላቂነት ያለው ልማት ለማካሄድ አይቻልም። በቅርቡ በሻሸመኔና በሌሎች አካባቢዎች የተካሄደው እልቂትና የመዋእለ ንዋይ ፈሰስ ውድመት የችግሩን ጥልቀትና ስፋት አሳይቷል። እያንዳንዱን ኢትዮጵያዊ የሚያሳዝነውና የሚያሳፍረው የንጹሃን ህይዎት እልፈት በኢትዮጵያ ታሪክ ጥቁር ነጥብ መሆኑን እያሰመርኩበት፤ የወደመውን ንብረት ለመተካት ብቻ ፈሰስ የሚሆነው መዋእለንዋይ ግዙፍ ስለሆነ አስርት ዓመታት ይወስዳል።

ይህን ግልጽና አጥፊ የሆነ የሕገ መንግሥትና የክልል አስተዳደር ተግዳሮት ከመሰረቱ ለመፍታት መጀመሪያ እትዮጵያን እንደ ሃገር ተቀብለን፤ በችግሩ ትርጉም ላይ እንስማማ። ከተስማማን በኋላ ደግሞ፤ አማራጮችን ከባለድርሻዎች ጋር በመመካከር፤ በጋራ ሆነን እንድንሰራ አሳስባለሁ። ብሄራዊ መግባባት የሚለው ጥሪ ትርጉም የሚኖረው የጋራ የሆነችውን አገራችን ኢትዮጵያን ያለ ማመናታት ስንቀበል ነው። አገር ከሌለ ድርድር ሊኖር አይችልም።

ህወሓቶችና ተባባሪዎቻቸው ሥልጣን ከያዙበት ወዲህ ያለው ከ 65-75 በመቶ የሚገመተው ትውልድ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት የሚባሉ እሴቶችን ታቅዶበት፤ እንዳያውቁ ተደርጓል። ይህ ትውልድ የተማረውና የታነጸው በብሄርና በኃይማኖት ማንነት ዓለም ብቻ ነው። ይህን መለያ የሚከተል ትውልድ፤ እንኳን ለንብረት፤ ለሰው ህይወትም ደንታ የለውም። ራስ ወዳድነትና ስግብግብነት በክለውታል። ሀወሓት ያስለመደው ቅጥፈትን፤ ጥላቻን፤ ጭካኔን፤ ጥፍር መንቀልጥን፤ ሌብነትን፤ ሙስናን እና ሌሎች ግድፈቶችን ስለሆነ እንኳን የሕግ የበላይነትን ለይቶ ለማወቅ ቀርቶ ሰብአዊ ፍጥረት የተቀደሰና የተከበረ መሆኑን አያውቅም። ቢያውቅም፤ አይቀበልም። ውጭ ያሉትን የጃዋርን መስመር የሚሰብኩትን “ምህራን” ተብየዎች ብቻ ተመልከቱ። ዩንቨርስቲ እያስተማሩ የዘውግ ጥላቻን ያሰራጫሉ፤ ሕዝብ ለእልቂት እንዲነሳ ይቀሰቅሳሉ። ይህን የወንጀለኞች ሴራ ዝም ብለን ማየት የለብንም።

ህወሓት/ኢህአዴግ የፈጠረውና ያሰለጠነው ትውልድ፤ አገርንና የመንግሥት ባለሥልጣናትን ለይቶ አያውቅም። ለምሳሌ፤ የአማራው ሕዝብ በበላይ ሆኖ የማይገዛ መሆኑን የማያውቀው ብዙ ነው። የሰጡትን ሁሉ ሳይለይና ሳያመዛዝን የሚያምነው ብዙ ነው። ማመዛዘን ቢኖርማ ሰውን እንደ እንስሳ ማረድ፤ መስቀልና ሬሳውን በመንገድ መጎተት አይታሰብም ነበር። የት አገር ነው እንደዚህ ያለ ጭካኔ በወጣቶች የሚካሄደው? ይህ ጭካኔ ከአይሲስ በምን ይለያል? አይለይም።

ይህን ስል፤ በዚህ ትውልድ መካከል በየሁሉም ዘውጎችና እምነቶች መካከል በመልካም ስነ ምግባር ያደጉና የታነጹ፤

አገራቸውንና መላውን ሕዝብ የሚያከብሩ የሉም ማለቴ አይደለም። አሉ። ተስፋ የሚሰጠኝ ይህ ሁኔታ መኖሩ ነው።

በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊያን ላይ የሚካሄድውን ግፍና በደል ስመለከት ይህች የነጻነት ተምሳሌት ኢትዮጵያ በምን አይነት ከሃዲዎች እና አጥፊዎች ተበከለች? ወደሚል ጭንቀት እሄዳለሁ። የችግሩ መሰረት ግን ዛሬ አልተፈጠረም፤ ወደ አምሳ ዓመታት ሆኖታል። እኛ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊነት የምናምነው ግን ከእንቅልፋችን ስላልነቃን ትኩረት አልሰጠነውም ነበር። አሁንም ጩኸትና ምሬት የምናሰማው በጋራና በአንድነት አይደለም።

በኔ እምነት፤ ፀረ-ኢትዮጵያና ፀረ-ኢትዮጵያዊነት አገራችን ያጠፏታል። በተመሳሳይም ባይሆን፤ ሌብነት፤ ሙስናም አገር ያጠፋሉ። የተዘረፈው ኃብት ለእልቂቶች ግብአትና አቅም እየሆነ፤ ለጠባብ ብሄርተኞችና ለጀሃዲስቶች መሳሪያ ሆኗል። ስርዓት ወለድ ድርጅታዊ ምዝበራ አገራችንን ኢትዮጵያንና ንጹህ ዜጎቿን እንደሚበክሉ በተደጋጋሚ አሳስቤ ነበር። ከላይ የተከበሩት ላቤል እንዳሳሰቡት፤ “ሙስናን የምንዋጋበት መሰረታዊ ምክንያት ለፍትህ፤ ለሰላምና ለእርጋታ ጠንቅ ስለሆነ ነው።”

የብዙ የበለጸጉ አገሮች ልምድና ታሪክ የሚያስተምረን አስኳል ጉዳይ ድህነትን ቀርፎ ፍትሃዊ፤ ሁሉን አሳታፊና ሚዛናዊ ገቢና

ኑሮን የሚያንፀባርቅ የልማት ፈር ለመመስረት አስፈላጊ ከሆኑት ጉዳዮች መካከል ጠባብ ብሄርተኛነትን፤ ጉቦን፤ አድልዎን፤ ሙስናንና ሕገ ወጥና ወነጀል መሆኑን በድርጊት ማሳየትና ከአገር ተሰርቆ የሚወጣን ግዙፍ ኃብት በዘዴና በብልሃት ከተደበቀበት ማስመለስ ወሳኝ መሆኑን ነው። ጉቦና ማንኛውም አይነት አድልዎ በየተኛውም አገር አለ ቢባልም ስርዓት ወለድ የሆነ፤ የአገርን ስራ የመፍጠርና ምርትን የማሳደግ አቅም የሚያመክን ግን በሕግ የተከለከለ መሆኑ አያከራክርም። የኢትዮጵያ መንግሥት ይኼን ማድረግ አለበት።

ለሃያ ስምንት ዓመታት ያህል፤ ህወሓት ኢህአዴግ የተባለውን የዘውግ ኃይሎች ንቅናቄ ፓርቲ መስርቶና በበላይነት እያሽከረከረ ኢትዮጵያን እንደ ሃገር፤ የኢትዮጵያን ድሃ ሕዝብ እንደ ዜጋ መዝብሮታል፤ ከፋፍሎታል። በተጨማሪ፤ የአማራውን ሕዝብ ለይቶ “ጨቋኝና ነፍጠኛ” ብሎ የከሰሰውና ለእልቂት ያጋለጠው ህወሓት ነው። በዘመነ ህወሓት፤ የኢትዮጵያ ፖለቲካና ኢኮኖሚ በጣምራ ተማርከው ነበር። ይህን የተማረከና የደቀቀ ኢኮኖሚ ነው የጠቅላ ሚንስትር ዶር ዐብይ አህመድ መንግሥት የተረከበው። የመንግሥቱ ስርዓት ጠባብ ብሄርተኝነትንና እየለየዩ መግደልን ስር እንዲሰዱና ሌብነት፤ ሙስናና ብልግና የተለመዱ እንዲሆኑ ያደረገው ህወሕት አሁንም ሙሉ በሙሉ ተወግዷል ለማለት አይቻልም። ህወሓት የመሰረተውን ወጥመድ ለመገርሰስ ጊዜ ይወስዳል፤ ህብረትንና የህዝብን ተሳትፎ ይጠይቃል።

የዚህ ሃተታ ዋና አላማ የህወሓት ድርጅታዊ ምዝበራ የገንዘብ መጠን፤ ለአገራችን ለኢትዮጵያ ነቀርሳ፤ ለአገራችን የርስ በርስ ግጭቶች መሰረት መሆኑን፤ ጠንካራና የማያሽማ እርምጃ ለመውሰድ ካልተቻለ ሁኔታው እየተባብሰ የሚሄድ መሆኑንና የገንዘብና የውጭ ድጋፍ አቅም ያላቸው ኃይሎች፤ በተለይ ህወሓት፤ ሽኔ ኦነግ፤ አክራሪ ቂሮ፤ ዋሃቢስቶችና ሌሎች ጽንፈኛ ኃይሎች በመደጋገፍና በመመሳጠር፤ አገራችን እንደ ከበቧት ለማሳየትና አቅጣጫዎች ለመጠቆም ነው።

ሙስናን ለምን መታገል አስፈለገ?

  1. ሙስና፤ ሌብነትና ምዝበራ ተደጋጋፊ ግድፈቶች ናቸው። በልዩ ልዩ የሥልጣን እርከን የተሰማሩ፤ የፓርቲ፤ የክልል፤ የፌደራል ባለሥልጣናት ተቀናጅተው ያለ አግባብ ከውጭ የሚገኘውን እርዳታና ባገር ውስጥ የተመደበውን ባጀትና ሌላ ገቢ በልዩ ልዩ መንገዶች ከሕዝብ አገልግሎት እየነጠቁ ወደ ግልና ወደ ቡድን ጥቅም ሲያውሉት፤ ከሃገርና ከሕዝብ እየደበቁ ሲያሸሹት ለኢንቨስትመንት የሚቀረው ኃብት ይቀንሳል።
  1. ይህ ምዝበራ ኢ-ፍትሃዊ ከመሆኑ በተጨማሪ፤ ማህበረሰባዊና ፖለቲካዊ ቀውሶችን ያስከትላል። ሕዝቡ በመንግሥቱ፤ በባለሥልጣናቱና በተቋማቱ ላይ ያለው እምነት ይኮላሻል፤ ይዳከማል። አለመተማመን ይነግሳል። በአገር ውስጥ ያለው ሰላምና እርጋታ ይናጋል። ማህበረሰብዊ ቀውስ አመች ስለሚሆንላቸው፤ የውጭ ጠላቶች ሁኔታውን ለራሳቸው ብሄራዊ ጥቅም ያውሉታል። ግብፅ የምታደርገው ይህንኑ ነው። ኢትዮጵያን በቀጥታ ለመውረር ሞክራ አንድ ጊዜም አልተሳካላትም። ሌላው ዘዴዋ የውክልና ጦርነት ማካሄድ ነው።

የሕወሓት ገፅታ ምን ይመስላል?

በሃገር ውስጥ፤ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ለማጥፋት ቀን ከሌት ከሚሰሩት አፍራሽ ኃይሎች መካከከል የመጀመሪያውን ደረጃ የያዘው ህወሓት ነው። ለሌሎች ዘግናኝና አጥፊ ቡድኖች ቀስቃሽና አመቻች ሁኔታዎችን የፈጠረላቸውም ይኼው ቡድን ነው። ለማስታወስ በቀለ ገርባ፤ ጃዋር ሞሃመድና ሌሎች የኦሮሞን ሕዝብ “እንወክላለን” ብለው ይሯሯጡ የነበሩት አገር አጥፊዎች፤ የኦሮሞን ወጣት የጨፈጨፈውን፤ የኦሮሞዎችንና የሌሎችን የፖለቲካ እስረኞች ጥፍር የነቀለውንና ሌሎችን ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶች የፈጸመውን ህወሓትን እንዴት ወዳጅና አጋር ሊሆኑት ወሰኑ? ጃዋርን፤ ደብረፅዮንንና ግብፅን ማን አቆራኛቸው? ለምን ዓላማ?

ጥናቶች፤ ምርምሮች፤ በአገር ቤትና በውጭ ሁኔታውን የሚከታተሉ ምርጥ ምሁራንና ተመራማሪዎች እንደሚሉትና እኔም እንደ ተመራመርኩት፤ ይህ አጥፊና ዘራፊ ቡድን ካልጠፋ በስተቀር ኢትዮጵያና የኢትዮጵያ ሕዝብ ሰላም አይኖራቸውም።

የግብፅን ተንኮልና የውክልና ጦርነት በቀላሉ ለመፍታት አይቻልም። ቢያንስ ቢያንስ ከፍተኛ ዋጋ ያስከፍላል።

በተጨማሪና ዋናው ክስተት፤ በዜግነት መብት ላይ የተመሰረተ ዲሞክራሳዊ ስርዓት ለመመስረት አይቻልም።

የህወሓት ክፋት፤ ተንኮለኛነትና አጥፊነት ዛሬ አልጀመረም። ራሱ ስሙ ተንኮልና ጠባብ ብሄርተኛነት ያሳያል። ይህን

ገጽታ በራሱ በህወሓት ተግባሮች ለማሳየት ይቻላል። ህወሓት ሥልጣን ከመያዙ በፊትና ከያዘ በኋላ ባደረግኋቸው ጥናቶችና ምርምሮች የተማርኳቸውን ጥፋቶች ከዚህ በታች አቀርባለሁ።

  1. ሀወሓት ሥልጣን ከመያዙ በፊት የተከተለው መርህ፤ “የአማራው ሕዝብ ከውጭ ገዢዎች ባላነሰ ደረጃ የትግራይ ሕዝብ ዋና ጠላት” ብሎ የሰየመ ነው መርህ ተከትሎ ይህ ሕዝብ ለብሄርና ለኃይማኖት ጽንፈኞች፤ ለውጭ ጠላቶች ኢላማ እንዲሆን አድርጓል። አማራውን የተለየ አጥቂ፤ ጨካኝ፤ ጨቋኝ፤ ቅኝ ገዢ ሕዝብ ነው በሚል የሃሰት ትርክት “ነፍጠኛ” ብሎ በመሰየምና በማስተጋባት፤ ህወሓት ሥልጣን ከመያዙ በፊትና በኋላ አማራው በገፍ እንዲጨፈጨፍ አድርጓል። በቅርቡ በተካሄደው እልቂትም ተባባሪ እንደሆነ አልጠራጠርም።
  1. ህወሓት “ታላቋን ትግራይን” ለማስፋፋት በተለመው እቅድ መሰረት፤ የአማራው ክልል መሬት እንዲሸነሸን፤ ወደ ትግራይ ክልል እንዲጠቃለል አድርጓል። እስካሁን ድረስ የአማራውን ሕዝብ ላደረገው ግፍና በደል ይቅርታ አልጠየቀም፤ የሚጠይቅም አይመስለኝም። በወንድማማቹ የአማራውና የትግራዩ ሕዝብ መካከል ያለውን ወዳጅነት በክሏል፤ አሁንም እይበከለው ነው። መለስ ዜናዊ በቀየሰው ዘዴ መሰረት፤ የአማራውና የኦሮሞው ወንድማማች ሕዝብ “እሳትና ጭድ” ሆኖ እርስ በርሱ እንዲጋጭ፤ እንዳይተማመንና በጥርጣሬ እንዲተያይ አድርጓል። በኔ እምነት፤ የአማራና የትግራይ ሕዝብ ከአብሮ መኖር ውጭ ሌላ አማራጭ የለውም።
  1. ህወሓት የአማራውን ሕዝብ ሽባና መሪ አልባ ለማድረግ በቀየሰው ዘዴ መሰረት ለራሱ ታዛዢና አጎብዳጅ የሆነውን ብአዴንን ፈጥሮ ነበር። በረከት ሰምኦን አጎብዳጅ፤ ሆድ–አደሮችንና ለጥቅማቸው ብቻ የሚሰሩ አማራዎችን በካድሬነት በማሰልጠን የአማራውን ክልል ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥሮት ነበር። ህወሓት የፈጠረው ድርጅት ያገለግል የነበረው ህወሓትን ነው። በክልሉ የኢኮኖሚ የበላይነትንም የያዙት ህወሓትና የህወሓት ታማኝ አማራዎች ናቸው። በረከት በሙስና የተከሰሰበት ዋና ምክንያትም ሌባና ሙሰኛ ስለሆነ ነው።
  1. ህወሓት ከፋፋይ እንደ ነበር ተመልካቾች ያምናሉ። የአማራውና የኦሮሞው ወንድማማች ሕዝብ “እሳትና ጭድ” እንዲሆን በማመቻቸት ሕዝቡ በፍቅር እንዳይኖር፤ ድህነት እንዳይቀርፍ፤ እርስ በርሱ እንዲጋጭ አመቻችቷል፤ አማራውን በተከታታይ “መጤና ነፍጠኛ” እየተባለ እንዲጨፈጨፍ ሌት ተቀን ሰርቷል፤ አሁንም ይሰራል።
  1. ህወሓት ፀረ-ኢትዮጵያ ነው። ኢትዮጵያ የሚለውን በዓለም ደረጃ መለያና ከፍተኛ እውቅናና ዝና ያላተን አገር ስም ለመጥራት ደፍሮ አያውቅም። የኢትዮጵያ ታሪክና ኢትዮጵያዊነት በካሪኩለም እንዳይሰጡ አድርጓል። የኢትዮጵያ ታሪክና የሕዝብ አብሮነት እንዲደመሰስ በማሰብ በዘውግና በቋንቋ የተመሰረተ ሕገ መንግሥት፤ የክልል አስተዳደርና የከፋፍለህ ግዛው ስርዓት ተቋማዊ እንዲሆን አድርጓል። ይህ ፀረ-ኢትዮጵያና ፀረኢትዮጵያዊነት ብሂል ስር እንዲሰድ ለማድረግ የትምህርቱን ይዘት ሙሉ በሙሉ ቀይሯል፤ ጠባብ ብሄርተኝነት እንዲነግሱ አድርጓል።
  1. ለዚህ አፍራሽ ትርክት ስር ነቀል የአስተሳሰብ ለውጥ ያስፈልጋል። እትዮጵያዊነት መልሶ እንዲለመልም ከህጻንነት ጀምሮ፤ በትምህርትና በሥልጠና ላይ በተቋማትና በመረጃ የተደገፈ እንቅስቃሴ መጀመር ወሳኝ ነው። ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት የሁሉም የሃገሪቱ ዜጎች እሴቶች መሆናቸውን በማያሻማ ደረጃ ማስተጋብት አስፈላጊና ወሳኝ ሆኗል። ይህ የሃገር ህልውና ጉዳይ መሆኑን አምናለሁ። ኢትዮጵያን ያወረሱን ከሁሉም ዘውጎችና ኃይማኖቶች የተወጣጡት ጀግኖች መስዋእት የሆኑላትን አገር ራሳቸውን ዝቅ አድርገው ይህችን የጀኖች አገር ዝቅ እንዲያደርጓት መፍቀድ የለብንም። እነዚህ ጀግኖች ከሁሉም በላይ ይከተሉት የነበረው ሰብሳቢ እሴት (Overarching value) ኢትዮጵያዊነት፤ አንድነትና በራስ መተማመንን ነው። ዓለም ባንክ፤ የትራምፕ መንግሥት ወይንም ሌላ እርዳታ ሰጠን ወይንም ነፈገን የኢትዮጵያን ክብር፤ ነጻነትና ሉዐላዊነት ስኬታማ የሚያደርገው ብሄራዊ አንድነት ነው።
  1. የቅርቡን ታሪካችን እንደ ምሳሌ ላቅርብ። የኢትዮጵያ ሕዝብ በጋራ ሆኖ ህወሓት ጉረሮውን አንቆ የያዘውን አገዛዝ በብዙ መስዋእትነት አስወግዶታል። ተመልሶ ደደቢት ሳይሆን መቀሌ በድሎት የመሸገው ህወሓት ሰላማዊና ዲሞክራሳዊ ለውጥ አያስፈልግም በሚል እብሪት ራሱን ከሌላው የኢትዮጵያ ታላቅ ህዝብ ለይቶ በመቀሌ መሽጎ መዶለቱንና ጠብ ጫሪነቱን ቀጥሏል። ከሁሉም በላይ ድህነትን ለመቅረፍ፤ ሰላምንና ልማትን የሚፈልገውን የትግራይን ሕዝብ እያስገደደ ወደ ጦርነት እሄዳለሁ እያለ ያስፈራራል። በቅርቡ በአማራው ክልል እንዲሰልሉና ግምገማ እንዲያደርጉ ያሰማራቸው ከሰማንያ በላይ “የህወሓት ሰላዮች” መያዛቸው የሚያመልክተውን ማጤን አስፈላጊ ነው። የውስጥ ተመልካቾች እንደሚሉት ከሆነ፤ “ህወሓት ቢያንስ ሁለት መቶ አምሳ ሽህ የሚሆን ወታደር አሰልጥኖ ለጦርነት አዘጋጅቷል።” ይህን አቅም ወደ ለልማት ቢጠቀምበት ኖሮ እኔም እደግፈው ነበር። ጥያቄው ግን፤ የጦርነቱ ኢላማ ማነው፤ ለምን? የፌደራሉን መንግሥት ለመቀየር ከሆነ ለምን ሰላማዊ በሆነ መንገድ ፉክክር አይካሄድም? ጭንቅላት ያለው ሰው ማሰብ ያለበት፤ ጦርነት ቢካሄድ ማን አሸናፊ፤ ማን ተሸናፊ ይሆናል? የሚለው ነው። የሚጎዳው የትግራይ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን፤ መከረኛው መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው። ኢትዮጵያዊያን ዋና ትኩረት ማድረግ ያለባቸው ድህነትንና ኋላ ቀርነትን ለማሸነፍ እንጅ የሚያመክን የርስ በርስ ጦርነት አይደለም። ጥሪው የድንቁርናና የእብድነት ነው። ታላቁንና በኢትዮጵያዊነቱ የሚታወቀውን የትግራይን ሕዝብ አደራ የምለው ይህንን የእብዶች ጥሪ አልቀበልም እንዲል ነው፤ በተለይ ወጣቱ ትውልድ።
  1. ህወሓት ኢትዮጵያን በተደጋጋሚ ክዷታል። መለስ ዜናዊ በኤርትራ ጉዳይ ላይ ከሻብያ አባላት ጋር ስለ አሰብ ሲነጋገር፤ “ኢትዮጵያ ወደብ ኑሯት አያውቅም” ብሏል። አሰብን አሳልፎ የሰጠው ለዚህ ነው። ህወሓት ሥልጣን ከያዘ በኋላ ራሱ የፈጠረውን አዲስ ታሪክ ስኬታማ ለማድረግ፤ መለስ ዜናዊ ለተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሃፊ፤ ለግብፃዊው ቡትሮስ ቡትሮስ ጋሊ ደብዳቤ ጽፎ ኤርትትራ ከእናት አገሯ ከኢትዮጵያ እንድትገነጠል አድርጓል። ከጥቂት ዓመታት በኋላ ደግሞ በወንድማማቹ በኢትዮጵያና በኤርትራ ሕዝብ መካከል በተደረገው አላስፈላጊ ጦርነት ምክንያት ከሰማንያ ሺህ በላይ ወገኖቻችን እንዲሞቱ መርቷል። እስካሁን ድረስ ያልተተካ የመዋእለ-ንዋይ ፈሰስ ወድሟል። ይህን ግጭት በስልትና በጥበብ እንዲፈታ ያደረጉት ጠ/ሚንስትሮ ዶር ዐብይ አህመድና ፕሬዝደንት ኢሳይያስ አፈወርቂ ናቸው። ይህ መላው ዓለም እውቅና ያስገኘው ስምምነት ለጠቅላይ ሚንስትር ዶር ዐብይ የኖቤል ሽልማት መሰረት መሆኑ ተገቢ ነው። የኦሮሞን ሕዝብ “እንወክላለን” የሚሉ በውጭ የሚኖሩ “ባለሞያዎች” በሻሸመኔ፤ በባሌና በሌሎች አካባቢዎች የተፈጸመውን የሚዘገንን ጭፍጨፋና የኃብት ውድመት የፈጸሙትን ግለሰቦችና አካላት ሳይተቹ በተገላቪጦሽ የኖቤል ድርጅት ሽልማቱን እንዲስብ ያቀረቡት አቤቱታ እነዚህን ግለሰቦች ታሪክ ለማይረሳው ትዝብት አጋልጧቸዋል።
  1. የህወሓት የክህደት ባህል አሁንም ቀጥሏል። ህወሓት ከኢትዮጵያ አፍራሽና አጥፊ መንግሥት፤ ከግብፅ ጋር ሴረኛ በመሆን ኢትዮጵያ ሃገራችን ወደ አደጋ እንድትገባ ወግኗል። ይህን በሚመለከት የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚንስትርና በቻይና አምባሳደር የነበረው ስዩም መስፍን እኛን ለማዘንጋትና በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ እንድንጠራጠር በሚል ስሌት “የሕዳሴን ግድብ በ $10-13 ቢሊየን ዶላር ሊሸጡት ነው” ብሎ ማስወራቱን ለማስታወስ እገደዳለሁ። ይህን አራብቶ ያሰራጨው ደግሞ የወያኔ “የሳይበር ጦርነት” አካል ነው። ይህ ቡድን በተደጋጋሚ ያሳየው የሜድያ ጦርነት የተቀዳው ከጃዋር ኦኤሜኤንና ከጃዋር የፌስቡክ ልምድ ነው።
  1. በቅርቡ የሆነውን እንመልከት። ህወሓት ከኦሮሞ ፅንፈኞችና ጠባብ ብሄርተኞች ጋር ወግኖ “ሕገ መንግሥቱ ፈረሰ፤ የፌደራል ስርዓቱ በማእከላዊያንና በነፍጠኞች ተማርኳል፤ የክልል አስተዳደር ሊፈርስ ነው” በሚሉ ትርክቶች፤ ከኦነግ ሽኔ፤ ከአክራሪው ጃዋር፤ ከ ቄሮዎችና ከግብፅ ጋር በመወገን እጅግ የሚዘገንን እልቂትና ውድመት አካሂደዋል። በሻሸመኔ ከተማ ብቻ የወደመው ኃብትና የሞቱት ወገኖቻችን ለዚህ አጥፊነት ምስክሮች ናቸው። መረጃዎች እንደሚያሳዩት፤ የተገደሉት ወገኖቻችን፤ ቅድመ ዝግጂት በሚያሳይ መልኩ፤ ስማቸውና ማንነታቸው በዘውግና በኃይማኖታቸው ተለይቶ ተጨፍጭፈዋል። ጭፍጨፋው የተካሄደው በድንገት አይደለም። ታስቦበትና ታቅዶቦት ነው። ከላይ እንደ ጠቆምኩት፤ “ነፍጠኛ” የሚል መለያ የተሰጠው አማራው ነው። አብረው የተጨፈጨፉት ጉራጌዎች፤ ወላይታዎች፤ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ ኦሮሞዎች ናቸው። ግን፤ ዋናውና በምንም መስፈርት የማያሻማው ኢላማ አማራው ነው። ይህ አማራውን እየለዩ መጨፍጨፍ ተባባሰ እንጅ ከተጀመረ ቆይቷል።
  1. የተቀነባበረው እልቂትና ውድመት ኢ-ሰብ አዊና የሚዘገንን ጭካኔን ከማሳየቱ ባሻገር፤ በኢትዮጵያ ላይ ያስከተለው የልማት እንቅስቃሴ መሰናክል ከወደመው ኃብት በላይ ነው። ጨካኞቹና ጨፍጫፊዎቹ ምንም ያላጤኑት፤ የልማቱ ውድመት የአካባቢውን ተራ ድሃ ሕዝብም እንደ ጎዳውና ወደፊትም እንደሚጎዳው ነው። ኃብት ያላቸው ግለሰቦች ወደፊት የመዋእለ ንዋይ ፈሰስ እንዳያደርጉ ይገታቸዋል። ይህ ሲሆን የስራ እድል ይጠፋል። ኑሮ ይወደዳል። ሽብርተኞች ለተራው ሕዝብ ደንታ እንደሌላቸው እየታወቀ ሲሄድ ሕዝቡ መሸሸጊያ ቦታ እንደማይሰጣቸው እገምታለሁ። ቁም ነገሩ ግን፤ እነዚህ ጨካኞችና አጥፊዎች ሙሉ በሙሉ የሚደመሰሱበትን ዘዴ መቀየስና አጥፊዎቹን በሙሉ በሃላፊነት መቅጣት ነው። ቸልተኛነት እንደማያዋጣ ከጥፋቱ ለመማር ይቻላል።
  1. በኢትዮጵያ የርስ በርስ የዘውግ ጦርነት አልተካሄደም። የዘውግ እልቂት መካሄዱ ግን ሊካድ አይችልም። ጥንቃቄ ማድረግ ያለብን፤ ጥቂት የተደራጀና ጠባብ ብሄርተኛ፤ ጽንፈኛና ሽብርተኛ አካል የፈጸመው ወንጀል በጅምላ በኦርሞና በአማራ ሕዝብ መካከል የተደረገ የዘውግ ጦርነት ነው ብሎ ለመናገር አይቻልም። መባልም የለበትም። የሚበጀው ወንጀለኞቹን ለይቶ በመከታተል ይህ አይነት ወንጀል እንዳይደገም ማድረግና በማያሻማ ደረጃ ወንጀለኞቹን መቅጣት ነው። ቅጣት ስል፤ ተራ ወንጀለኞችን ብቻ ሳይሆን፤ ከጀርባ ሆነው በውጭ አገርም ሆነ በውስጥ፤ ጭፍጨፋው እንዲካሄድ የቀሰቀሱትንና ያመቻቹትንም ጭምር ለፍርድ ማቅረብ ማለቴ ነው። እዚህ ላይ የኢትዮጵያ መንግሥት እንዳያመነታ አሳስባለሁ፤ እመክራለሁ።
  1. ይህንን የቅርብ የጀኖሳይድ እልቂትና ውድመት የተለየ የሚያደርገው ከአማራው ንጹህ ህይወት በተጨማሪ “ኦሮሞ ያልሆኑት” ሁሉ መጨፍጨፋቸው ነው። የአማራው፤ የጉራጌው፤ የወላይታው፤ የክርስቲያን ኦሮሞውና የሌላው ህዝብ ተለይቶ ኢላማ የሆነውና “ተባባሪ” ተብሎ መጨፍጨፉና ኃብትና ንብረቱ መውደሙ የጭካኔውን ስፋትና ጥልቀት ያሳያል። አማራውን ለይቶ መጨፍጨፍ እንዳለ ሆኖ (የተለመደ ሆኗል)፤ በተጨማሪ ደግሞ ፀረ–ኢትዮጵያና ፀረ–ኢትዮጵያዊነት ይዘት ይታያል። “ዳውን ዳውን ኢትዮጵያ” የሚል መፈክር ለመጀመሪያ የታየው በዚህ አጥፊ ወቅት መሆኑ ራሱ አሳሳቢ ነው። ይቅርታ የማይደረግለት ወንጀል ነው። የግብፅን ሰንደቅ አላማ የያዙትስ የማነን አላማ ስኬታማ ለማድረግ ነው?
  1. በዚህ አጋጣሚ ልጠቅሰው የምፈልገው ክስተት፤ እልቂት እየተካሄደ ሽብርተኞችን በማውገዝ ፋንታ፤ አንዳንድ የውጭ የሰብአዊ ድርጅቶች በኦሮምያ ኢንተርኔት ተከለከለ ብለው ሲተቹ ሚዛናዊ የሆነ ትችት አለማቅረባቸው ለትዝብት ዳርጓቸዋል የሚለውን ነው። ለምን ለተጨፈጨፉት ወገኖቻችን ድምጽ አያሰሙም?
  1. ህወሓትና ተባባሪዎቹ የሚያካሂዱት እልቂት ባይነቃበት ኖሮ ዛሬ ኢትዮጵያ ልክ እንደ ሶርያ፤ እንደ የመን፤ እንደ ሶማልያ ትሆን ነበር። ይህ የፖለቲካ ቁማር እንደ ገና ቢከሰት ማንም እንደማይተርፍ እገምታለሁ። ህወሓትም ሆነ ተባባሪዎቹ በተለይ ሽኔ ኦነግ፤ አክራሪው ቄሮና ሌሎች ጽንፈኞች የመጨረሽ አድላቸው በኢትዮጵያ ሊሆን አይችልም። አጥፍተው ራሳቸውም ይጠፋሉ። የፈጸሙት ወንጀል በዓለም ደርጃ ለክስ የሚቀርብ ወንጀል ነው።
  1. የህዳሴን ግድብ መለስ መጀመሩ የሚፈለግና የሚመሰገን ፕሮጀክት መሆኑን ገልጫለሁ። ሆኖም፤ ይህ ፕሮጀክት ይህን ያህል ጊዜ የወሰደበት አንዱ ምክንያት ሜቴክ የተባለው የህወሓት ድርጅት ለሙስና ስለ ተጠቀመበት መሆኑ በሰፊው አልተነገረም። ይህ በአገራችን ላይ የተፈጸመ የኢኮኖሚ ወንጀል ነው።
  1. ህወሓት የኢኮኖሚ ወንጀል ፈጽሟል። ህወሓቶች ሥልጣን ከያዙበት ጀምሮ ከማረኩት የፖለቲካ ሥልጣንና ኢኮኖሚ የዘረፉት ገንዘብ በውጭ ምንዛሬ ሲሰላ አስርት ቢሊየን ዶላሮች ይሆናል። ይህ በኢትዮጵያና በድሃው ህዝቧ ስም የተገኘው ድጎማ፤ እርዳታ ቢያንስ ቢያንስ አስር የህዳሴ ግድቦችን ያሰራል። ይህ ግዙፍ ኃብት ተሰርቆ የተደበቀው በምስራቅ ኤዢያ፤ በመካከለኛው ምስራቅ፤ በሰሜን አሜሪካ፤ በአውሮፓ፤ በፓናማና በካሪቢያን ደሴቶች መሆናቸው ይጠቀሳል።
  1. ይህ ግዙፍ ኃብት እንዴት ሊወጣ ቻለ የሚለው ጥያቄ ከተመለሰ ቆይቷል። ለምሳሌ አመቻች የነበሩት የኢትዮጵያ ኤምባሲዎች የህወሓት ምሽጎት ሆነው ማገልገላቸው ከስሌቱ ወስጥ እንዲገባ አሳስባለሁ። ይህ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ተሰርቆ የወጣው ግዙፍ ኃብት ለህወሓቶችና ለሚቀጥሯቸው አጥፊ ኃይሎች ከፍተኛ አቅም እየገዛላቸው ነው።

የተዘረፈው የውጭ ምንዛሬ ወደ መሳሪያነት ሲቀየር

ብር ይቀየር ወይንስ ይቆይ የሚለው ጥያቄ አከራካሪ ነው። ብር ሲቀየር ወጭ ያስከትላል። ይህ ወጭ ለመንግሥት ኪሳራ

ነው። ጥቅሙ ከፍ ያለ ቢሆን ኪሳራን ያካክሳል። ግን፤ ህወሓት የዘረፈው ብዙ ቢሊየን የውጭ ምንዛሬ ገንዘብ ተሰርቆ ውጭ አገሮች ነው ያለው። ህወሓት የሚፈልገውን የውጭ ምንዛሬ በድብቅ ወደ አገር እያስገባ በጥቁር ገበያ ይለውጠዋል። ስለዚህ፤ ብር ቢቀየርም ችግሩን አይፈታውም። ምንጩ አይደርቅም። መፍትሄው ምንጩን ማድረቅ ነው።

እልቂትን፤ ግጭትን፤ ሁከትንና ሌሎች ተንኮሎችን ለማካሄድ ገንዘብ ወሳኝ ነው። የተደበቀው ግዙፍ ገንዘብ ተንኮለኞችንና

መሳሪያዎችን ለመግዛት ያስችላል። አጥፊ ሜድያዎችን ለማንቀሳቀስ ያስችላል። ግዙፍ ገንዘብ ያለው ኃይል ግዙፍ ተንኮል

የመስራት አቅሙን ያመቻቻል።

ሽብረተኞች በስማቸው ይለዩና ይጠሩ።

የህወሓትንና የተመሳሳይ አጥፊ ኃይሎች ለማምከን የሚቻለው የኢኮኖሚና የፋይናንስ አቅማቸውን በማፍረስ ነው። የኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት መሪዎች ማድረግ ያለባቸውም ይህንኑ ነው። ሌላው አማራጭ ደግሞ፤ ህወሓት፤ ሽኔ ኦነግ፤ አክራሪ ቄሮና እንደ አል ሸባብ የሆኑ መሰል የእስልምና አክራሪ ኃይሎች ለሕዝብ እልቂት ቀስቃሽ የሆኑ አካላት በሙሉ፤ የኦሮሞ ሜድያ ኔትወርክን ጨምሮ፤ በአፍሪካ አንድነት ድርጅት፤ በተባበሩት መንግሥታትና በሌሎች ተቋማት ተገምግመው “አሸባሪ ወይንም ሽብርተኛ ድርጅቶች ናቸው” ተብለው እንዲሰየሙ ማድረግ ነው። ይህ ሲሆን ያላቸውን የኢኮኖሚና የፋይናንስ አቅማቸውንም አብሮ ለማምከን የሚቻልበት ሁኔታ ይፈጠራል።

ማንም ሽብርተኛ ወይንም ዘውግን በዘውግ ላይ እልቂት እንዲያካሂድ የሚቀስቅስ ኃይል በወንጀለኛነት መሰየም አለበት። ይህን የማያሻማ አቋም መውሰድ ያለበት የኢትዮጵያ መንግሥት ነው። ለዚህ መረጃ የሚሰጡና ተባባሪ የሚሆኑ ብዙ ኢትዮጵያዊያን አሉ፤ መጠቀሙ ግን የኢትዮጵያ መንግሥት ሃላፊነት ነው። በምእራብ አገሮች በድብቅና በይፋ እልቂት የሚቀሰቅስ ግለሰብና ቡድን ወንጀለኛ መሆኑን ማሳየት የእያንዳዳችን ሃላፊነትም ጭምር ነው። መረጃ ሰብስበን ወደ ክስ የመሄድ ግዴታ አለብን። ክስ የጀመሩትንም የመርዳት ሃላፊነት አለብን። ከሸሸን አገር ትፈርሳለች፤ ሕዝብ ይጨፈጨፋል።

የህወሓት የገንዘብ አቅም ግዙፍ ነው ያልኩበት መረጃ ምንድን ነው?

ህወሓት ከጂምር መርዘኛ እባብ ነው። ይህ መርዝ ተከታታይ ትውልድን በክሎታል፤ መዝብሮታል። ታላቋን አገራችን አድክሟታል። የዘረፈውን ግዙፍ ኃብት እነደ ወንጀል ስለምመለከተው ገጽታውን በመረጃ ተደግፌ ላቅርበው።

ጠቅላይ ሚንስትር ዶር ዐብይ ሥልጣን ከመያዛቸው ቀደም ብሎ ፎርብስ በተባለው የካፒታሊስቱ መገናኛ ዴቪድ

ስታይንማን የ “ Money, Blood and Conscience” ደራሲ በኢትዮጵያ የተካሄደውን ምዝበራ “Ethiopia’s Cruel Game”

በተባለው አርእስት አቅርቦት ነበር። ከውጭ የሚለገሰው ግዙፍ እርዳታ መባከኑን ተመልክቶ የሚከተለውን ጥያቄ

አቅርቧል። “Why, despite ever-increasing amounts of foreign support, can’t this nation of 100 million clever, enterprising people feed itself? Other resource-poor countries facing difficult environmental challenges manage to do so.” መልሱ ቀላል ነው። ለጋሶች የሚሰጡት የውጭ ምንዛሬ ከተዘረፈ ሌሎች ተመሳሳይ አገሮች የተለገሰውን የውጭ ምንዛሬ ለልማት–መሰረተ ልማት፤ የስራ እድል ፈጠራው፤ የምርት እድገት ወዘተ ላይ ለማዋል ሲችሉ ለኢትዮጵያ የተሰጠው ግን ተዘርፏል።

ህወሓት በበላይነት ሲያሽከረክረው የነበረው ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘበት ከ 1991 ወዲህ ለኢትዮጵያ ድሃ ሕዝብ በኦፊሴል ደረጃ የተለገሰው የውጭ ምንዛሬ በትክክል ባይታወቅም ከ$50 ቢሊየን በላይ ነው። ስታይንማንን ዘገባውን በ 2017 መጨረሻ አካባቢ ሲያቀርብ፤ ከአሜሪካ መንግሥት ብቻ የተለገሰው ገንዘብ መጠን $30 ቢሊየን ነበር። ገንዘቡን ማን ሰረቀው? የት ሄደ? ለማን ጥቅም ዋለ?

“ “The amount stolen by Ethiopia’s leaders since it took power is $30 billion.” This figure “is based on the UN’s own 2015 report on Illicit Financial Outflows by a panel chaired by former South African President Thabo Mbeki and another from Global Financial Integrity, an American think tank. These document $2-3 billion—an amount roughly equaling Ethiopia’s annual foreign aid and investment— being drained from the country every year, mostly through over- and under-invoicing of imports and exports.” How do you eradicate poverty when thieves of state and government snatch aid from the society?

ኢትዮጵያ በያመቱ ከምትለገሰው የውጭ ምንዛሬ መካከል፤ ጥናቶች ያሳዩት በያመቱ በአማካይ፤ ከ$2–$3 ቢሊየን ከተዘረፈች ድህነትን ለመቅረፍ ምን ያህሉ ተረፋት። መልሱ ባዶ ነው። ዝቅተኛውን በአማካይ $2 ቢሊየን ብንወስድ እንኳን፤ ህወሓት ሥልጣን ከያዘበት ጀምሮ እስከ ለቀቀበት ጊዜ ወደ $50 ቢሊየን ተሰርቆ ከኢትዮጵያ እንዲሸሺ ተደርጓል። ይህን የኢኮኖሚ ወንጀል አይደለም የሚል ግለሰብ ካለ መከራከራያ ሃስቡን ለኢትዮጵያ ድሃ ሕዝብ እንዲያቀርብ አሳስባለሁ።    ይህን ግዙፍ ኃብት ማን ነጠቀው?

እኔ የምተቸውን ወደ ጎን ልተወውና የስታይማንን መልስ ላቅርብ።

ኢትዮጵያን በበላይነት የገዛው አንድ የዘውግ ልሂቃኖች ፓርቲ ነው። የበላይነቱን የያዘው ህወሓት ነው። ተፎካካሪ ፓርቲ፤ ነጻ የመገናኛ ብዙሃን፤ ነጻ የማህበረሰብ ድርጅት በህግ የተከለከለ ነበር። ለኢትዮጵያና ለመላው ድሃ ሕዝብ ተቆርቋሪና ተሟጋች የለም ነበር፤ አሁንም አለ ለማለት አልችልም። ግን አሁን ያለው ከህወሓት ይለያል፤ ቢያንስ ድርጅታዊ ዝርፊያ አይካሄድም። ደካማና የተበታተኑ ይሁኑ እንጅ “ተፎካካሪ ፓርቲዎች አሉ፤ መገናኛ ብዙሃንም የተሻሻሉ ናቸው።  በህወሓት ዘመን፤ ፍርድ አውጭው፤ ዳኛውና ፈራጅ ቆራጩ ህወሓት ነበር። ስታይንማን እንዲህ በሚል አስቀምጦታል።

““Ethiopia’s far-left economy is centrally controlled by a small ruling clique that has grown fantastically wealthy. Only they could be responsible for this enormous crime. In other words, the same Ethiopian leadership that is begging the world for yet another billion for its hungry people is stealing several times that amount every year.” ለወንጀሉ ተጠያቂ ህወሓት ነው።  “An accountable Ethiopian government would have to allow more relief to reach those who truly need it and reduce the waste of U.S. taxpayers’ generous funding.”

ዓለም ባንክ፤ አይ ኤም ኤፍ፤ የአሜሪካ መንግሥት ባለሥልጣናትና ሌሎች ሌብነቱን፤ ሙስናውንና ከአገር በገፍ ተሰርቆ የሚሸሸውን ግዙፍ ኃብት ልክ እንዳላዩ አልፈውት ነበር። የተባበሩት መንግሥታትና ፕሬዝደንት ኦባማ የነበረውን መንግሥት በፀረ-ሽብርተኛነቱ መስፈርት ብቻ በመገምገም የምእራብ አገሮች ወዳጅ አድርገውት እንደ ነበር ማስታወስ ተገቢ

ነው።  “Like Mr. Guterres, past U.S. presidents have been afraid to confront the regime, which even forced President Barack Obama into a humiliating public defense of its last stolen election. The result has been a vicious cycle.”

ለጋስ አገሮች ሙስናን ችላ የሚሉት በራሳቸው ጥቅም ላይ ምንም ጉዳት ስለሌለው ነው። የተሰረቀውና የሚሸሸው ገንዘብ የሚደበቀው፤ በአብዛኛው በምእራብ አገሮች ስለሆነም ጭምር ነው። አሜሪካ የለገሰው $30 ቢሊየን ሲሰረቅ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ለምን ዝም አሉ? ብለን የመጠየቅ ግዴታ አለብን፤ ዓለም ባንክም መጠየቅ አለበት።

ቢያንስ ቢያንስ፤ ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ስኬታማ ለማድረግ ትችል ነበር። የህወሓት ትኩረት ድህነትን ከማጥፋት ላይ አልነበረም። ራሱንና ደጋፊ ሆዳሞችን ኃብታም ከማድረጉና ግዙፍ ኃብት ከማሸሹ ላይ ነበር።      ድርጅታዊ ምዝበራውን ማን አካሄደው?

ከላይ ስታይናማን እንዳቀረበው፤ ምዝበራውን ያካሄደው ህወሓትና ታማኞቹ ናቸው። በ August 2018, እንደ ገና ፎርብስ ባወጣው ዘገባ ከሁለት መቶ ሚሊየን ዶላር ባለ ኃብታቸው መስፈርት ብቻ የታወቁትን ቱጃሮች ብቻ ጠቅሶ እነማን  እንደሆኑ ስማቸውን ይፋ አድርጎታል።  “Even though Ethiopia is classified as one of the developing countries in the world there are still rich people who are living and enjoying life like the westerns do.”

ወንጀሉን አስቡት። የኢትዮጵያ እናቶችና ወጣት ሴቶች ምግብ ለማብሰል በጀርባቸው እንጨትና ኩበት ይሸከማሉ። ህጻናት በጠለላ ይማራሉ። ስድሳ አምስት ሚሊየን የሚሆኑ ኢትዮፕያዊያን የኤሌክትሪክ መብራ ስለሌላቸው በጨለማ ይኖራሉ። በብዙ ሚሊየን የሚቆጠሩት ረሃበተኛ ናቸው ወዘተ ወዘተ። ጥቂት ኃብታሞች ግን በፖለቲካ ሥልጣን የተነሳ ልክ የም እራባዊያንን ኑሮ ይኖራሉ፤ ልጆቻቸውን በውጭ አገር ያስተምራሉ። ህክምና ሲያሥፈልጋቸው ዱባይ፤ ቻይና፤ ታያልንድ፤ አሜሪካ ይሄዳሉ። ወጣት ኢትዮጵያዊያን ባገራቸው የስራ እድል ስሌሌላቸው ወደ አረብ አገሮች ይሰዳድሉ።

የነፍስ ወከፍ ገቢን እንመልከት፤ በ2019 በዓመት $867 ነበር። የግብፅ ግን $3,022 ነው። በተመሳሳይ፤ በማህበረሰባዊ ልማት ሚዛን በ 2018 ኢትዮጵያ ከ 189 አገሮች መካከል እርከኗ 173ኛ ነበር።

ይህ የድህነት ገጽታ እንዳለ ሆኖ በ ፎርብስ የ 2018 ስሌትና መረጃ በድሃዋና የምግብ ዋስትና በሌላት ኢትዮጵያ ህወሓት ኃብታም እንዲሆኑ ካመቻቸላቸው መካከል አስሩ ኃብታሞች የሚከተሉት ናቸው።

ከዚህ ላይ ልጠቅሰው የምፈልገው አባባል አግባብ ስላለው ይኼው። “”ኢትዮጵያ ሃገሬሞኝ ነሽ ተላላ፤ የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ

የቱጃሮቹ ፎቶግራፎች አዲስ ስታር የተባለው ጋዜጣ በ August 26, 2018 ባወጣው ህትመቱ ያሳያቸ ናቸው።.

ከዝቅጠኛ ወደ ከፍተኛ ኃብታም በሚለው ይነበብ።

10ኛ፤ ወይዘሮ ሱሁራ ኢስማኤል ካን፤ ነጋዴ፤

9ኛ፤ አቶ እዮብ ማሞ

8ኛ፤ አቶ ኦመር አሊ ሽፋው

7ኛ፤ አባይ ጸሃይ

6ኛ፤ ሳሙኤል ታፈሰ

5ኛ፤ ስዩም መስፍን

4ኛ ፤       ስብሃት ነጋ፤

3ኛ፤ ብርሃነ ገብረኪርስቶስ

2ኛ፤ አዜብ መስፍን

1ኛ፤ ሞሃመድ አል-አሙዲ

ለማጠቃለል፤

ሰርቶ፤ አምርቶ፤ ለዜጎች የስራ እድል ፈጥሮ፤ ድህነትን ቀርፎ፤ ለሃገር ከፍተኛ አስተዋፆ አድርጎ፤ የህዝብን አክብሮትና አድናቆት ተቀናጅቶ ሃብታም መሆን አግባብ አለው፤ አስፈላጊም ነው። ግን የፖለቲካ ሥልጣንን ተጠቅሞ ድርጅታዊ ምዝበራ ማድረግና የሕዝብንና የሃገርን ኃብት በተለያዩ መንገዶች ከአገርና ከሕዝብ ማሸሺ ህሊና ቢስነት የሚያሳይ ወንጀል ነው። ያንን ግዙፍ ኃብት እየተጠቀሙ እልቂት፤ ሽብርተኛነትና ሌሎች ወንጀሎችን መፈጸም ደግሞ ከወንጀል የባሰ ወንጀል ነው።

  1. ህወሕትና ተባባሪዎች የኢዮጵያን ኢኮኖሚ ማርከው አባሎቻቸውን፤ ቤተሰብና ወዳጆቻቸውን በህልማቸው አስበውት የማያውቁትን ኃብት ለማካብት በቀየሱት ስልት፤ ኃብት ከኢትዮጵያ ድሃ ሕዝብ መዝብረዋል፤ ግዙፍ የውጭ ምንዛሬ ህገ-ወጥ በሆነ መንገድ አሽሽተው በልዩ ልዩ ቦታዎች፤ በልዩ ልዩ ስሞች ደብቀዋል:: ይህ ግዙፍ ኃብት ለኢትዮጵያ ድሃ ሕዝብ፤ የትግራይን ሕዝብ ጨምሮ መመለስ አለበት።
  1. ይህ ግዙፍ የገንዘብ ኃብት ክምችትና ሽሽት በተጨማሪ ያስከተለው ክስተት፤ አሁን ለሚካሄደው የሽብርተኞች የእልቂትና አገርን የማፈራረስ ሴራ አቅም እየገዛላቸው ነው። የኢኮኖሚ ወንጀል ሌላ ተጨማሪ ወንጀል እንዲፈጸም እያመቻቸ ነው።
  1. በስልጣን ብልግና ራሳቸውን፤ ቤተሰባቸውንና ወዳጆቻቸውን ኃብታም ያደረጉት ህወወሓቶችና አጋሮቻቸው ልጆቻቸውን፤ ቤተሰባቸውንና ኃብታቸውን ወደ ውጭ አውጥተው መላውን የኢትዮጵያን ጥሮ ግሮ የሚያድረውን ሕዝብ በሰላም እንዳይኖርና ኑሮውን እንዳያያሻሽል ማድረጋቸው በራሱ ሊወገዝ ይገባል። ለወገኑ የሚቆረቆር ይህን ግፍና በደል አያደርግም። ከሕዝብና ከሃገር አይሰርቅም።
  1. ዘገባዎቹ እንዳስዩት፤ ህወሓት የኢኮኖሚ ወንጀል ፈጽሟል። ሥልጣን ከያዙበት ጀምሮ ህወሓቶችና ሌሎች የቀን ጅቦች ከማረኩት የፖለቲካ ሥልጣንና ኢኮኖሚ የዘረፉት ገንዘብ በውጭ ምንዛሬ ሲሰላ አስርት ቢሊየን ዶላሮች ይሆናል። ይህ በኢትዮጵያና በድሃው ህዝቧ ስም የተገኘው ድጎማ፤ እርዳታ ቢያንስ ቢያንስ አስር የህዳሴ ግድቦችን ያሰራል። ይህ ግዙፍ ኃብት ተሰርቆ የተደበቀው በምስራቅ ኤዢያ፤ በመካከለኛው ምስራቅ፤ በሰሜን አሜሪካ፤ በአውሮፓ፤ በፓናማና በካሪቢያን ደሴቶች መሆኑ ይጠቀሳል። ይህ ግዙፍ ኃብት ለድሃው ለኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲመለስ ከፍተኛ ጥረት መደረግ አለበት፤ ይቻላል፤ ናይጀሪያ አድርጋዋለች። መንግሥት መሪ ሚና ይጫዎት። በተጨማሪ፤ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊነት የሚያምነው ሁሉ በመረጃው ላይ ይረባረብ። ቁጭ ብሎ መተቸት ጊዜው አልፎበታል።
  1. የኢትዮጵያ መንግሥት ትኩረት ሊሰጥባቸው ከሚያስፈልጉት ፕሮግራሞች መካከል አንዱ፤ የህወሓትን፤ የሽኔ ኦነግን፤ የእስልምና ኃይማኖት ጽንፈኞችን፤ የጽንፈኛ ቄሮዎችን ከሰላማዊው ቄሮ እየለዩ፤ የጃዋሪያን መገናኛ ትሥስርንና ተመሳሳይ የሽብርተኞች የሳይበር ጦርነት መረብ፤ የኢኮኖሚና የፋይናንስ ሰልት አቅሞችን ከምንጫቸው ማድረቅና ማፍረስ ወሳኝ ሆኗል። ማንኛውም ሽብርተኛ ኢትዮጵያን ምሽግ ሊያደርጋት አይችልም እንበል።
  1. የህዳሴ ግድብ የህልውና ጥያቄ ነው። ድጋፋችን በያለንበት እናሰማ፤ ለግድቡ ስኬት የድርሻችን እንወጣ። ድሃው ሕዝብ ቦንድ እየገዛ ለኛ ምሳሌ ሆኗል፤ እኛም ቦንድ እንግዛ፤ ግድቡን ስኬታማ እናድርገው።
  1. በቅርቡ ጀኔራል ካሳየ ገመዳ በአንድ ቃለ መጠይቅ እንዳሳሰቡት፤ የኢትዮጵያ የፌደራል መንግሥት “ራሱን ከውስጥ አጥፊዎች የማጽዳት” ግዴታ አለበት። በተጨማሪ፤ ንጹሃንን የጨፈጨፉትን፤ በሻሸመኔና በሌሎች አካባቢዎች ግዙፍ ኃብት ያወደሙትን፤ ከኢትዮጵያ የውጭ ጠላቶች ጋር ሴራ ያደረጉትን ግለሰቦችና ከጀርባቸው የዶለቱትን፤ ያመቻቹትን አጥፊዎች ሁሉ ያለ ምንም ማመንታት ለፍርድ እንዲቀርቡ ማድረግና ቅጣቱን ለሕዝብ ይፋ ማድረግ አስፈላጊ ነው። ይህ ጉዳይ የመንግሥት ብቻ ሳይሆን፤ የአገር ህልውና ጥያቄም ሆኗል። የማያዳግም እርምጃ ካልተወሰደ አሁን የተከሰተው ችግር ይደገማል፤ ሊባባስም የሚችልበት ሁኔታ ይታያል።
  1. እኛ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊነት የምናምነው በተናጠል ፍይዳ ቢሶች ነን። ፋይዳ ያለው ጉዳይ ለመስራት የምንችለው በአንድነት ስንሰራ ብቻ ነው። ባንድነት ለመስራት ደግሞ መጀመሪያ ለማዳመጥና ከሌላው ወንድምና እህታችን ለመማር ስንችል ነው።
  1. መምህር ታየ ሲናገር፤ “የኢትዮጵያን ሕዝብ ከቋንቋው ውጭ” በመልኩ ሊለየው የሚችል የለም ያለውን ሙሉ በሙሉ እጋራለሁ፤ መለያየትን ትተን የጋራ እሴቶቻችን እናጠናክር።
  1. በመጨረሻ፤ ኢትዮጵያዊያን የአገር ፍቅርን መልሰን የምናድስበት ወቅት ዛሬ ነው። ጥቃቅን ልዩነቶችን ወደ ጎን ትተን፤ በኢትዮጵያና በእውነተኛ ሁሉን አሳታፊ በሆነ ኢትዮጵያዊነት መረብ የመሰብሰብ ግዴታችን እንድንወጣት ጥሪ አቀርባለሁ። ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለድርድር አይቀርቡም ለማለት እንድፈር!!

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትንሩ!! የኢትዮጵያ ሕዝብ እንድነት ይለምል!!

July 29, 2020