October 19, 2020 – Konjit Sitotaw 

የፓስፖርት አገልግሎት ከጥቅምት 10 ጀምሮ መስጠት ይጀምራል ተባለ፡፡

በኢሜግሬሽን፣ ዜግነት እና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ የህዝብ ግንኙነት እና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ደሳለኝ ተሬሳ ለኢትዮ ኤፍ ኤም እንዳሉት በኦን ላይን አማካኝነት ፓስፖርት አገልግሎት ከነገ ጥቅምት 10 ቀን 2013 ዓ/ም ጀምሮ መስጠት ይጀመራል ብለዋል።

ኤጀንሲው ከዚህ በፊት ፓስፖርት እና ሌሎች ተያያዥ አገልግሎቶችን በኢንተርኔት አማካኝነት በኦንላየን እንደሚሰጥ አስታውቆ ነበር።አሁን ላይ በዋናነት ከጥቅምት 2 ቀን 2013 ዓ/ም ጀምሮ በኦን ላይን የቪዛ ማራዘም ና ጊዜአዊ የመኖሪያ ፍቃድ የመስጠት አገልግሎት ተጀምሯል፡፡

የፓስፖርት አገልግሎት በተባለው ቀን ያልተጀመረው ሌሎች የደህንነት እና የቴክኒክ ስራዎች በታሰበው ጊዜ ባለመጠናቀቃቸው መሆኑንም አቶ ደሳለኝ ነግረውናል።

ተገልጋዮች በኦንላይን www.Evisa.com ላይ በመግባት ቪዛ ማራዘምና ጊዜያዊ የመኖሪያ ፍቃድን የመሳሰሉ አገልግሎቶችን ማግኘት እንደሚችሉ ገልፀውልናል፡፡

በመዲናዋ የሚሰጠው አጠቃላይ መደበኛ የፓስፖርት አገልግሎት ህዳር 1 ቀን እንደሚጀምርም ነግረውናል፡፡