
ሐራ ዘተዋሕዶ
October 22, 2020
- ተቃራኒ ኃይሎችን ማስታረቅና ምእመናንን ከጥቃት መጠበቅ ቀዳሚ ትኩረቱ ነው፤
- ከቀትር በኋላ ውሎው፣ የመደበኛ ስብሰባውን 16 የመነጋገርያ አጀንዳዎች አጸደቀ፤
ከእኒኽም አጀንዳዎች ውስጥ፡-

- በየጊዜው ያሳለፋቸው በርካታ ችግር ፈቺ ውሳኔዎቹ፣ በአፈጻጸም የሚዳፈኑበትንና ጉዳዮች አድሮ ቃሪያ እየኾኑ የሚቀርቡበትን አዙሪት፣ በብርቱ በመገምገም ጥብቅ መመሪያ ይሰጣል፤
- ከእነርሱም መሀከል፥ የመሪ ዕቅድ ትግበራን አስመልክቶ፣ አጽድቆ እንዲተገበር ከወሰነበት ጥቅምት 2008 ዓ.ም. እና ጥቅምት 2011 ዓ.ም. ወዲህ በአስፈጻሚው አካል ምን እንደተሠራ የጠቅላይ ጽ/ቤቱን ሪፖርት ይሰማል፤ ይጠይቃል፤
- ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ፥ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ እና ዓለም አቀፋዊ ተልእኮ የበለጠ በሚያጠናክር፤ የአስተዳደር አካላቱን የግልጽነት እና የተጠያቂነት አሠራር በሚያረጋግጥ፤ በማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ መስኮች የደረሰችበትን ዕድገት ባገናዘበ እና የወቅቱን ጥያቄዎች በሚመልስ መልኩ ከመሠረቱ እንዲሻሻል በቀረበው ሐሳብ ዙሪያ ይመክራል፤
- የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ዩኒቨርሲቲን ደንብ ጨምሮ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የትምህርት ፖሊሲ ተወያይቶ አቅጣጫ ይሰጣል፤
- በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት፣ በምስካበ ቅዱሳን ቆጋ ኪዳነ ምሕረት ገዳም፣ የዶግማ እና የቀኖና ጥሰት አስመልክቶ ውሳኔ ያሳልፋል፤
- የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትን፣ የ2013 ዓ.ም. በጀት ረቂቅ እንዲሁም ልዩ ልዩ ቋሚ እና ጊዜያዊ የበጀት ጥያቄዎችን መርምሮ ያጸድቃል፤ የሚሉቱ ዐበይት ናቸው፡፡

በሌላ በኩል ምልአተ ጉባኤው፣ በአርቃቂው ኮሚቴ ተመጥነው የቀረቡለትን 16 የመነጋገርያ ነጥቦች፣ ዛሬ ከቀትር በኋላ በማጽደቅ፣ በአጀንዳዎቹ ላይ መነጋገር የጀመረ ሲኾን፤ የአጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ 39ኛ ዓመታዊ ስብሰባ የጋራ መግለጫ እና የውሳኔ ሐሳብ በንባብ አድምጧል፡፡ አስፈላጊ ማስተካከያዎችን በማከልም፣ የ2013 ዓ.ም. በጀት ዓመት የሥራ መመሪያ ኾኖ እንዲሠራበት፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቱ በኩል ለመምሪያዎች እና ድርጅቶች እንዲሁም ለመላው አህጉረ ስብከት እንዲሠራጭ ወስኗል፡፡