(ኢዜአ)
በኢትዮጵያ የሚስተዋሉ ግጭቶች በአንድ ማኅበረሰብ ላይ ያተኮሩ ቢመስሉም አገር የማተራመስ ዕቅዶች በመሆናቸው በጋራ መመከት ይገባል ተባለ።
–

በአገራዊ ሠላምና ወቅታዊ የፖለቲካዊ ጉዳዮች ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የፖለቲካ ምሁራንና ፖለቲከኞች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአገሪቷ የሚታዩ ሕገወጥ ተግባራት አገር ለማተራመስ የታቀዱ ሴራዎች ስለመሆናቸው ይስማማሉ።
–
የነፀብራቅ አማራ ድርጅት ሊቀ መንበር አቶ ቸርነት አንዳርጌ ግጭቶቹና የሰው ሕይወት የማጥፋት ድርጊቶቹ ብሄር ተኮር ቢመስሉም ዓላማቸው ‘አገር ማተራመስ ነው’ ይላሉ።
–
እነዚህ ድርጊቶች ሲያጋጥሙ የእኔ ብሄር አልተነካም ብሎ ዝም ማለት የዋህነት ነው ያሉት አቶ ቸርነት ድርጊቶቹን ከወዲሁ ልናስቆማቸው ይገባል ብለዋል።
–
በኢትዮጵያ ሠላም ማጣት የሚያተርፉ ቡድኖች በማኅበረሰቡ ውስጥ መኖራቸውንና ሕዝቡም እንደሚያውቃቸው የተናገሩት ደግሞ ፖለቲከኛው ዶክተር አንጋሳ አህመድ ናቸው።
–
በመሆኑን ሕዝቡ ሕገወጥ ግለሰቦችም ይሁን ቡድኖችን በጋራ መከላከል አለበት ነው ያሉት።
–
ግጭቶችን ለማስቆም በችግሮቻችን ዙሪያ የመወያየት ልምድ ማዳበርና በሠላማዊ መንገድ የመፍታት ባህልን ማሳደግ ይገባናል ያሉት ደግሞ ዶክተር አንዳርጌ ታዬ ናቸው።
–
ችግሮችና ቅሬታዎችን በንግግር ለመፍታት እየተጀመሩ ያሉ ብሄራዊ ምክክሮች ሊጠናከሩ እንደሚገባም አመልክተዋል።
–
የፖለቲካ ምሁሩ ዶክተር ዲማ ነገዎ በበኩላቸው በርካታ ችግሮችን አልፈው ወደ ዴሞክራሲ ስርዓት ለሚገቡ እንደ ኢትዮጵያ ላሉ አገራት የሚያስፈልገው ሁሉን አቀፍ ምክክርና ፖለቲካዊ ተሳትፎ ነው ይላሉ።
–
በኢትዮጵያ ሠላም ለማስፈንና ለማንም የማይወግን ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለመገንባትም ዜጎች በ’ያገባኛል’ ስሜት መሳተፍ እንዳለባቸው ተናግረዋል።
