November 03,2020

“የዜጎችን ሞት ማስቀረት ያልቻለ ፣ ህግ የማያስከብር ፓርላማም ሆነ መንግስት ምን ያደርጋል” ያሉት የተወካዮች ምክር ቤት ም/አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ሽታዬ ምናለ ፤ ” የቆምኩለት ህዝብ እየሞተ ነው ፤ ለውጡን ስንጀምር የነበረኝ ተስፋ ዛሬ የለም” ብለዋል።

Reporter Amharic : የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለዛሬ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓም በጠራው ስብሰባ ከፍተኛ ቁጣ አስነሳ።

በምክር ቤቱ የገነፈለው ቁጣ መነሻ በወለጋ በተፈጸመው የብሔር ጥቃት ቢሆንም ፤ ተመሳሳይ ጥቃቶች በየአካባቢው መፈጸም መቀጠሉ እና ስራ አስፈጻሚው መንግስት ንጹሀንን መታደግ እንዳልቻለ ፣ “ጥቃቱን በጠነሰሱት እና በነሱ አገልጋዮች” እርምጃ ለመውሰድ አለመቻሉን አምረው ተችቸዋል።

በዚህ ምክንያት የንጹሀንን ሞት መስማት በየቀኑ እየተለመደ መምጣቱን የገለጹት የምክር ቤት አባላቱ ፤ በሻሸመኔ ፣ በባሌ ፣ በቤንሻንጉል እና መሰል አካባቢዎች ብሔርን መሠረት ያደረገ አሰቃቂ ጭፍጨፋ ተፈጽሞ ምንም እንዳልተፈጠረ እየተረሳ በመሄዱ አንዱ የሚሞት አንዱ የሚኖርበት ሀገር እየሆነ ነው ብለዋል።

በምክር ቤቱ ቁጣቸውን መቆጣጠር የተሳናቸው በርካታ ተመራጮች የተስተዋሉ ሲሆን ከነዚህ መካከልም የምክር ቤቱ ምክትል አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ሽታዬ ምናለ አንዷ ነበሩ።

” የዜጎችን ሞት ማስቀረት ያልቻለ ፣ ህግ የማያስከብር ፓርላማም ሆነ መንግስት ምን ያደርጋል” ያሉት ምክትል አፈጉባኤዋ ፤ ” የቆምኩለት ህዝብ እየሞተ ነው ፤ ለውጡን ስንጀምር የነበረኝ ተስፋ ዛሬ የለም” ብለዋል።

ሌሎች የምክር ቤት አባላትም ተመሳሳይ ምሬት ያሰሙ ሲሆን በንጹሀን ላይ የሚፈጸመው ጭፍጨፋ ማብቃት አለበት ብለዋል።

ምክር ቤቱ ውስጥ መጠነኛ የሀሳብ መከፋፈል የተስተዋለ ሲሆን ፤ በስተመጨረሻም “የተጎነጎነው ሴራ መንግስትን ማፍረስ ነው ፤ ጥቃቱ የሚያም ቢሆንም በጥንቃቄ እናስተውል ፤ በተከፈተልን ቦይ ውስጥ መፍሰስ የለብንም” የሚሉ የሰከኑ ሀሳቦችም ቀርበዋል።

በወለጋም ሆነ በተለያዩ አካባቢዎች የደረሱትን ጥቃቶችን በተመለከተ ጠቅላይ ሚንስትሩ እና ሌሎች የሚመለከታቸው ባለስልጣናት ተጠርተው ማብራሪያ እንዲሰጡ እና ስር ነቀል መፍትሔ እንዲበጅለት ተስማምተዋል። Reporter