አማራ ሚዲያ ማዕከል / Amara Media Center

“በሽብርተኝነት የመፈረጁ እርምጃ በዘር ፍጅት ላይ በማስፈጸም በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የተሳተፉትን ማጠቃለል ይኖርበታል።” ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲአማራ ሚዲያ ማዕከል/አሚማ ጥቅምት 25 ቀን 2013 ዓ.ም አዲስ አበባ ሸዋባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ በወቅታዊ ጉዳይ የሰጠው መግለጫ:_በቅርቡ በወለጋ ዞን ጉሊሶ ወረዳ ባለፈው ሳምንት በጉራፈርዳ በአማራ ዜጎቻችን ላይ የተካሄደው ዘግናኝ የዘር ጭፍጨፋ ባልደራስ በጽኑ እንደሚያወግዝ ይገልጻል። እንዲሁም ይህንን ዘግናኝ የዘር ጭፍጨፋ የፈጸሙና ያስፈጸሙ ሀይሎች ለህግ እንዲቀርቡ ፓርቲያችን አበክሮ ይጠይቃል። ይህ የዘር ፍጅት እየተባባሰ በመምጣቱ እና ማቆሚያው ባለመታወቁ መንስኤውም የአስፈጻሚው የመንግስት አካል ዳተኝነት መሆኑን የተገነዘበው የህዝብ ተወካዬች ምክር ቤት ለዚህ የዘር ፍጅት አስፈጻሚው የመንግስት አካልን ተጠያቂ ማድረጉ ይታወቃል። የጠቅላይ ሚንስትር ዶ/ር አብይ አህመድ መንግስት በፓርላማው የተነሳበትን ተጠያቂነት መሰረት በማድረግ እና ህወሀት በሰሜኑ እዝ ላይ በከፈተው ጥቃት በህወሀት ላይ ጦርነት አውጇል። የህዝብ ተወካዬች ምክር ቤት አባላት በጠየቁት መሰረት እና ከጦርነቱ ጎን ለጎን ህወሃት በሽብርተኝነት እንዲፈረጅ እና አስቸኳይ እርምጃ ሊወሰድበት እንደሚገባ ፓርቲያችን በጽኑ ያምናል። ልክ በህወሃት ላይ እንደሚካሄደው ጦርነት የዘር ፍጅት እየፈጸመ በሚገኘው በኦነግ ሸኔ እና በኦሮሞ ጽንፈኞች እና ተመሳሳይ ተግባር በተለያዩ አካባቢዎች ላይ በሚፈጽሙት ሁሉ ላይ መደረግ ያለበት የዘገየ እርምጃ እንደሆነ የባልደራስ እምነት ነው። ይህም በሽብርተኝነት የመፈረጁ እርምጃ በዘር ፍጅት ላይ በማስፈጸም በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የተሳተፉትን ማጠቃለል ይኖርበታል። ሀገራችንን ለዚህ ሁሉ የዘር ፍጅትና ትርምስ ውስጥ የከተታት ህወሃት እና ኦነግ ያዘጋጁት ህገ መንግስት ለሀገር አንድነት እና ስጋት ምንጭ ስለሆነ ሊታገድ ይገባል። ከጦርነቱ በኋላ መንግስት ህገ መንግስቱ የሚታገድበትን እና ሁሉም ኢትዬጵያውያን የሚስማሙበት አዲስ ህገ መንግስት እንዲዘጋጅ ሁኔታዎችን ሊያመቻች እንደሚገባ ፓርቲያችን በጽኑ ያምናል። በመጨረሻም አሁን በሀገራችን በህወሀት ላይ የሚደረገው ጦርነት ተገቢ እንደሆነ ፓርቲያችን በጽኑ ያምናል። ዳሩ ግን ወንድም በሆነው በትግራይ ህዝብ ላይ እልቂት እንዳይፈጸም ፓርቲያችን ማሳሰብ ይወዳል። በጦርነቱ ላይ ለሚሳተፉት የመከላከያ ሰራዊትም ሆነ የአማራ ክልል ልዩ ሀይል ፓርቲያችን ልዩ ክብር አለው።
ጦርነቱንም የሚመሩ ባለስልጣናት ከእልህ እና ከቂም በቀል በራቀ ህግን በማስከበር ብቻ እንዲመሩ ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ጥሪውን እያቀረበ በሂደቱ መስዎዕትነት እየከፈሉ ለሚገኙ የመከላከያ ሰራዊታችን እና ለአማራ ልዩ ኃይል አክብሮት እና እድናቆቱን ዳግም እየገለጸ ሌሎችን ሀገራዊ ጉዳዬችን ከጦርነት ጎን ለጎን የሚፈቱበትን አማራጭ ላይ ሁሉም ስለኢትዮጵያ ያገባኛል የሚል ሀይል እንዲሳተፍ ያሳስባል።