November 8, 2020 – Konjit Sitotaw
ወታደራዊ መረጃ – ሻለቃ ማሞ ለማ
–
ወያኔ ጦርነት ከመቀስቀሱ ጋር ተያይዞ ሰሞኑን ኢትዮጵያውያን በሶሻል ሚዲያ ላይ የሚቀባበሉት ሚሳኤልና ሮኬትን የተመለከተ ጉዳይ አንዳንድ ከእውነት ጋር የማይገናኙ የተጋነኑ መረጃዎች በመተላለፍ ላይ ስለሚገኙ ያንን ማጥራት አስፈላጊ ሆኗል።
–

1ኛ፡ “MR300” ወይም “MR400” የሚባል ሚሳኤል ተብሎ ሲወራ የነበረው በዚህ ዓይነት የሚጠራ ሚሳኤል በኢትዮጵያም ሆነ በዓለም የለም።
–
2ኛ፡ በአሁኑ ወቅት ሰሜን ዕዝ ታጥቋቸው በወያኔ እጅግ ሊገቡ ችለው ይሆናል ተብለው ከሚጠረጠሩ የረጅም ርቀት መሣሪያዎች ውስጥም 600፣ 700፤ አና እስከ አንድ ሺህ ኪሎ ሜትር የሚሄድ ሚሳኤል አለ የተባለውም እንዲሁ ሙሉ በሙሉ ውሸት ነው።
–
3ኛ፡ ይኸው MR300 የሚል ስያሜ ያገኘው ሚሳኤል ደግሞ የማውደም አቅሙ ሦስት ኪሎ ሜትር ክልል ውስጥ ያሉ ነገሮችን ሁሉ ይደመስሳል ተብሎ የተወራለት ሲሆን እውነቱ ግን እንኳን ይህ ምንነቱ ያልታወቀ ሚሳኤል ኒኩለር (nuclear warhead) ያለው ካልሆነ በስተቀር በሦስት ኪሎ ሜትር ክልል ውስጥ ያለን ነገር በአንድ ጊዜ የሚያወድም ሚሳኤል የለም።
–
እውነተኛው መረጃ

አሁን ባለው መረጃ መሠረት፤ ሃገሪቱን ከውጪ ጠላት ለመከላከል ሲባል በኢትዮጵያ ሕዝብ ገንዘብ ተገዝተው የኢትዮጵያ ሃገር መከላከያ ኃይል ታጥቋቸው በሰሜኑን የሃገሪቱ በኩል የሚመጣን የውጪ ጠላት ለመከላከል ሲባል በትግራይ ምድር ተጠምደው የነበሩ ረዘም ያለ ርቀት ተጓዥ ምድር ለምድር (surface to surface) የሮኬትና የሚሳኤል ሲስተሞች ቀጥለው የተመለከቱት ናቸው።
–
1ኛ፡ A300 ሮኬት አወንጫፊ መድፍ ሲስተም (artillery rocket systems)
ይህ ሮኬት አወንጫፊ መድፍ የቻይና ስሪት ሲሆን ሊጓዝበት የሚችለው የመጨረሻ ርቀቱ 300 ኪ/ሜ ነው። በትላንትናው ዕለት በዜና ላይ በተገለፀው መሠረት ይህ መሣሪያ ይኖርበታል የተባለው ቦታ ላይ በተካሄደው የአየር ድብደባ መውደሙ ተዘግቧል። የተረፈም ካለ መልሶ ለባለንብረቱ የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲመለስ ይደረጋል፤ ያም ካልሆነ በተገኘበት ይወድማል። ከዚሁ ጋር ከA300 በፊት የነበረው A200 የተባለው ሮኬት አወንጫፊ ሊጓዝ የሚችለው 200 ኪ/ሜ ብቻ ነው።
–
2ኛ፡ M20 ቻይና ሰራሽ የአጭር ርቀት (short-range) ballistic missile ነው።
–

በወያኔ እጅ ወድቆ ነበር የተባለ ሚሳኤል ካለ ይህ M20 ሊሆን ከቻለ ይህ ሚሳኤልም ሊጓዝ የሚችለው 280 ኪ/ሜትር ነው። ይህ ሚሳኤልም በአየር ድብደባ እንደተመታ በዜና ተነግሯል።
–
ከላይ የተጠቀሱት በትግራይ መሬት ወያኔ በእጁ ነክቷቸው ይሆናል ተብለው የተጠረጠሩ የምድር ለምድር ሮኬትና ሚሳኤል ሲስተም ናቸው። በሌላ በኩል እዚህ ላይ መግለፁ አስፈላጊ አይደለም እንጂ በተለይ ከለውጡ በኋላ ኢትዮጵያ እንደ ሃገር ከዚህ የላቀና የገዘፈ የሚሳኤል ሲስተም እና የአየር ኃይል አቅም አዳብራ እንደምትገኝ ሁሉም ሊረዳው ይገባል።
–
ሻለቃ ማሞ ለማ Via Petros ashenafi kebede