December 6, 2020

በሸዋ የደራ አማራ ላይ የሚደርሰው ግፍ እና በደል መቋጫ እንዲኖረው መንግስትን ጨምሮ የሁሉንም አካላት እርብርብ የሚጠይቅ መሆኑ ተገለፀ።

አማራ ሚዲያ ማዕከል/አሚማ

ህዳር 28 ቀን 2013 ዓ.ም

አዲስ አበባ ሸዋ

ካለፉት በርካታ ዓመታት ጀምሮ በአማራዊ ማንነቱ የተነሳ ተደራራቢ ግፍና በደል እየደረሰበት ያለውን በሸዋ የደራ አማራ ጥያቄ ተገቢ ምላሽ ያገኝ ዘንድ መንግስትን ጨምሮ የሁሉም አካላት እርብርብ አስፈላጊ መሆኑን የገለፁት በሸዋ የደራ አማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ ሊቀመንበር መ/ር ሀይለ ሚካኤል አርዓያ ናቸው።

መ/ር ሀይለ ሚካኤል ሲቀጥሉ በሸዋ የደራ እና የመተከል አማራ አስታዋሽ በማጣቱ እጅግ ዘግናኝና አሳዛኝ ጥቃት እየተፈፀመበት መሆኑን ጠቅሰዋል።

በተለይ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ኃላፊነቱን ባለመወጣቱና መዋቅሩን በተገቢ ሁኔታ ባለመፈተሹ እንዲሁም በየበርሃው በሚንቀሳቀሱ ሽፍቶች በንፁሃን ላይ የሚፈፀመውን ግድያ፣ እገታና ዝርፊያ ማስቆም አልተቻለም ሲሉ ወቅሰዋል።

በደህንነት ስጋት ምክንያት በደራ አያሌ የቱቲ ዞን አማራዎች ከእለት እለት የመኖሪያ አካባቢያቸውን ለቀው ለመሸሽ ተገደዋል ነው የተባለው።

እንደአብነትም በጥቅምት ወር 2013 ዓ.ም ወ/ሮ አልማዝ መኮንን የተባለች አንዲት ሴት በሽፍታ ታግታ ቤተሰቦቿ 40 ሽህ ብር ከፍለው ተለቃለች ያሉት መ/ር ሀይለ ሚካኤል በተመሳሳይ ህዳር 23 ቀን 2013 ዓ.ም በደራ የአቶ ደምሰው ዳኘ ልጅን አግተው አንድ መቶ ሽህ ብር አስከፍለው ስለመልቀቃቸው ተናግረዋል።

ህዳር 25 ቀን 2013 ዓ.ም አማረ አይተንፍሱና አቶ አድማሱ ወንዴ የሚባሉ አርሶ አደሮች ወደ አዝመራቸው ባቀኑበት በሽፍታዎች ተገድለዋል ነው ያሉት።

የመንግስት አካላት ለጉዳዩ ትኩረት በመንፈጋቸው ህ/ሰቡ ተቸግሯል ለየትኛው መገዛት እንዳለበት ግራ ተጋብቷልም ብለዋል።

በዛሬው እለትም ወካይ እና ሁሉን አካታች ባልሆነ መልኩ አማራ መውጣት አለበት ሲሉ የነበሩ አካላትን አስታራቂ በማለት የሰላም ኮንፈረንስ ብለው ተቀምጠዋል፤ ይህም ማስመሰል ስለሆነ ለውጥ አያመጣም ሲሉ አክለዋል።

አያይዘውም በተከፈለው ከፍተኛ መስዋዕትነት ወልቃይት፣ጠገዴና ራያ ከከሃዲው ሕወሓት ነጻ በመውጣታችሁ ከፍተኛ ደስተኛ ተሰምቶናል፤ እንኳን ደስ አላችሁ ያሉት መ/ር ሀይለ ሚካኤል በቀጣይም በተባበረ ትግል የመተከልና በሸዋ የደራ አማራ ከጭቆና ነጻ እንደሚወጣ ነው የገለፁት።

ሙሉ ዝግጅቱን በአሚማ የዩቱብ አድራሻ የምናጋራ ይሆናል።