አማራ ሚዲያ ማዕከል/አማሚ
ታህሳስ 6 ቀን 2013 ዓ.ም
አዲስ አበባ ሸዋ

የአማራ ወጣቶች ማህበር ሊቀመንበር ወጣት አስናቀ መንገሻ እንደገለፀው የፌደራልና የአማራ ክልል መንግስት በመተከል እና በኦሮሚያ ክልል ወለጋ እና ሆሮ ጉድሮ ዞን የተለያዩ ወረዳዎች በአማራ ላይ እየተፈፀመ ያለውን የጅምላ ፍጅት የማስቆም ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጠይቋል።
አስናቀ ሲቀጥል በቅርቡ በዘር አጥፊው ትሕነግ ላይ የተወሰደው ህግ የማስከበር እርምጃ በመተከል፣ በምስራቅ ወለጋ ጊዳ እና በምዕራብ ወለጋ ግንቢ እንዲሁም በሆሮ ጉድሮ ዞን አሙሩ ወረዳዎች መደገም አለበት ብሏል።
ከ30 ዙር በላይ ልዩ ሀይል አሰልጥኖ ያስመረቀው የኦሮሚያም ሆነ የቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል መንግስታት የአማራ ህዝብን ሰላምና ደህንነት ሊያስከብሩ አለመቻላቸውን አልቻሉም ሲል ወቅሷል።
የፌደራል መንግስት ለዜጎች እኩልነት የሚሰራና አገር አፍራሾችን ማስተካከል አለብኝ የሚል ከሆነ በትሕነግ ላይ የወሰደውን ህግ የማስከበር እርምጃን በመውሰድ አማራዎችን መታደግ አለበት ሲልም አክሏል።
ይህ የማይሆን ከሆነ ግን በመተከልም ሆነ በኦሮሚያ የአማራ ክልል መንግስት ገብቶ በማንነታቸው ምክንያት በጅምላ እየተጨፈጨፉ ያሉ አማራዎችን እንዲታደግ የሚያደርግ ታሪካዊ፣ሞራላዊና ህጋዊ መሰረት አለው ብሏል።የፌደራል መንግስትም የአማራ ክልል መንግስት ገብቶ ንፁሀንን ከአሸባሪዎች እንዲታደግ መፍቅድ ይኖርበታል ሲልም አስተያየት ሰጥቷል።
ይህ በአማራ ላይ በኦሮሚያና በመተከል እየተፈፀመ ያለው የፖለቲካ አሻጥር መቆም አለበት ያለው ወጣት አስናቀ ጄኔራል ብርሀኑ ጁላም በትሕነግ ላይ ከተወሰደው ህግ የማስከበር እርምጃ ማግስት በሁሉም የአገራችን ክፍሎች ሰላም ሰፍኗል ማለታቸውን የአማራ ወጣት ማህበርን አስቆጥቷል፤ አንቀበለውም ትክክልም አይደለም ነው ያለው።
በመተከል፣ በወለጋ፣በሆሮ ጉድሮ አማራ በጅምላ በፅንፈኛው ኦነግ ሸኔና በተባባሪ ቄሮዎች እየታረደ ባለበት ሁኔታ በመላ አገሪቱ ሰላም ሰፍኗል መባሉ ለገዳዮች በማገዝ በአማራ ላይ እንደመሳለቅ እንቆጥረዋለን ሲልም ወቅሷል።