December 22, 2020 – Konjit Sitotaw

EBC : የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከቅርብ አመታት ወዲህ የህዳሴው ግድብ መገንባትን ተከትሎ ኢትዮጵያ ከጎረቤት ሀገራት ጋር ግጭት ውስጥ እንድትገባ ወጥኖ የሚሰራ ኃይል መኖሩን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ገልጿል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ዛሬ ለጋዜጠኞች ሳምንታዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
የምስራቅ አፍሪካን ሰላም የማይሹ ኃይሎች ሱዳን እና ኢትዮጵያ መሃል ክፍተት መፍጠር እንደ ትልቅ ሎተሪ እየተመለከቱት በመሆኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጉዳዩን በትኩረት እየተከታተለው እንደሚገኝም ነው አምባሳደር ዲና የገለፁት። ኢትዮጵያ እና ሱዳን በሚጋሯቸው ድንበሮች ሰሞኑን እየተሰሙ ላሉ ግጭቶች አንዱ የዚህ ኃይል በጉዳዩ አጀንዳውን ለማስረፅ የሚሞክር እንደሆነ የጠቆሙት የድንበር ማካለሉ ስራ በትእግስት የሚሰራ ስለመሆኑም አንስተዋል።
ባለፈው ሳምንት የተከናወኑ አበይት ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮችን በተመለከት መግለጫ የሰጠው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ የሰባት ሀገሮች ዲፕሎማቶችን የሹመት ደብዳቤ የተቀበሉ እንደሆነ ተገልጿል። አምስት የኤዥያ ሀገራት እና ሁለት የአፍሪካ ሀገራት በኢትዮጵያ የተካሄደው የህግ ማስከበር ዘመቻ በተሳካ መልኩ በመጠናቀቁ የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት ማስተላለፋቸውም ነው የተገለፀው።

የሰባት ሀገራት ዲፕሎማቶችን ሹመት ማስተናገድ ከህግ ማስከበር ጎን ለጎን ኢትዮጵያ በትክክለኛ የዲፕሎማሲ ጎዳና ላይ መሆኗን እና ከዓለም አቀፉ የዲፕሎማሲ ስርአት ጋር በመናበብ እየተንቀሳቀሰች መሆኗን ያጎላ ነው ብለዋል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ።
ከኢጋድ 38ኛው አስቸኳይ የመሪዎች ጉባኤ ጋር በተያያዘ አባል ኃገራቱ ችግሮቻቸውን ካለማንም ጣልቃ ገብነት በውይይት የመፍታት ባህል የማዳበር አቅጣጫ ተቀምጦ በስኬት መጠናቀቁንም አስረድተዋል። አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በመግለጫው በለተለያዩ ሀገራት መሪዎችና ተቋማት በተለይም በህግ ማስከበር ዙሪያ መንግስት ግንዛቤ በሚገባ ያስጨበጡ ስራዎች እንደተሰሩ የተገለፀ ሲሆን እንደ ፊንላንድ ያሉ ሀገራት በህግ ማስከበር ጉዳይ ከመግባባት ባለፈ በቀጣይ ለሚሰሩ ስራዎች የገንዘብ ድጋፍ ለማድረግ ፈቃደኝነታቸውን አሳይተዋል።
ከዚህ ባለፈም በዚህ ሳምንት ብቻ 327 ኢትዮጵያውያን ከሳውዲ አረቢያ እንዲመለሱ የማድረግ ስራ መሰራቱንም አምባሳደሩ ጠቁመዋል።በኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ረገድም ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ጋር ስራዎች የተሰሩበት ሳምንት መሆኑን የገለፁት አምባሳደር ዲና የኢትዮጵያ እና ግብፅን የንግድ ግንኙነት የተሻለ ለማድረግም የኢትዮ-ግብፅ የንግድ ስምምነቶችን የተሻለ ለማድረግም ጥረቶች ተደርገዋል ብለዋል።የአውሮፖ ህብረት ለኢትዮጵያ ይሰጥ የነበረውን ዘጠና ሚሊየን ዶላር ተሰረዘ ተብሎ የተወራው ኃሰት ስለመሆኑም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አስታውቋል።

