
Post published:February 9, 2021
አዲስ አበባ ፣ የካቲት 2 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የተገነባው በሀገሪቱ የመጀመሪያው ትልቁና ዘመናዊ የእናቶችና ህፃናት ሆስፒታል ግንባታ ተጠናቀቀ ።
ሆስፒታሉ በ20 ሺህ ካሬ ላይ ያረፈ ሲሆን ከ400 በላይ ተኝቶ መታከሚያ አልጋዎች ያሉትና 100 የልህቀት ማዕከል አገልግሎት መስጫ ክፍሎችን ያካተተ ነው ተብሏል።
በተመሳሳይ ሰአት ለሰባት እናቶች የቀዶ ጥገና አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ዘመናዊና ወረቀት አልባ መስተንግዶ የሚሰጥ ሆስፒታል መሆኑም ተገልጿል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በጤናው ዘርፍ በተለይም በወሊድ እና ተያያዥ ጉዳዮች በእናቶች እና ህጻናት የሚደርሰውን የሞት ምጣኔ ለመቀነስ በአይነቱ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነ ሆስፒታል መሆኑም ነው የተነገረው።
ሆስፒታሉ ከነገ በስቲያ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ ተመርቆ ስራ የሚጀምር ይሆናል።
ግንባታው ቀድሞ ለመለስ ዜናዊ አመራር አካዳሚ ተብሎ የተጀመረ ሲሆን የከተማ አስተዳደሩም ካቢኔ በከተማዋ ትልቅ የአገልግሎት ችግር ያለበትን የእናቶችና ህጻናት ጤና ቅድሚያ በመስጠት 700 ሚሊየን ብር በመመደብ ተጨማሪ ግንባታ በማድረግ እና ነባሩን ግንባታ በማሻሻል ወደ ሆስፒታልነት እንዲቀየር አድርጓል።
Source: Link to the Post