15 መጋቢት 2021

NATIONAL ELECTION BOARD OF ETHIOPIA
ኢትዮጵያ ስድስተኛ አገር አቀፍ ምርጫን ለማካሄድ ቀን ቆርጣ በዝግጅት ላይ ናት። በአሁኑ ወቅት የአገሪቱ ምርጫ ቦርድ በያዘው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት የፖለቲካ ፓርቲዎች ዕጩ ተወዳዳሪዎችን የማስመዝገቢያ ጊዜ ተጠናቋል።
በ673 የምርጫ ክልሎች ላይ ለሚከናወነው ስድስተኛው አገር አቀፍ ምርጫ የቀረው ጊዜ 12 ሳምንታት ገደማ ነው።
ለሦስት አስርት ዓመታት ለሚጠጋ ጊዜ አገሪቷን የመራው የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) ስልጣን ከተቆጣጠረ በኋላ በ1984 የብሔራዊ፣ ክልላዊ፣ የዞን እና የወረዳ ምክር ቤት ምርጫ ተካሂዷል።
ይህም በሽግግር መንግሥቱ ለነበረው የተወካዮች ምክር ቤት አባልነት መንግሥት ምስረታ ሲሆን በወቅቱ የነበረው የብሔራዊ፣ ክልላዊና የወረዳ ምክር ቤት አባላት ምርጫ አስፈፃሚ ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅም ምርጫውን አስተባብሯል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሕገ መንግሥቱ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ አገሪቷ በአጠቃላይ አምስት ጠቅላላ ምርጫዎችን አካሂዳለች። ከዚህም በተጨማሪ የማሟያና የአካባቢ ምርጫዎችን ጨምሮ ስድስት ሕዝበ ውሳኔዎች በአጠቃላይ 14 ምርጫዎች ተካሂደዋል።
ወደ ኋላ መለስ ብለን አገሪቱ ባደረገቻቸው አምስት ጠቅላላ ምርጫዎች ምን ያህል ሕዝብ መርጧል፣ የተወዳዳሪ ፓርቲዎች ብዛት፣ በምርጫዎቹስ ማን አሸነፈ የሚለውን ታሪካዊ ዳራ እንቃኛለን።
- የፖለቲካ ፓርቲዎችና ያልተመለሰው የሴቶች አካታችነት ጥያቄ
- “ማንም መብታችንን ሊሰጠን ስለማይችል፤ ሴቶች ማንንም ሳይጠብቁ በራሳቸው መታገል አለባቸው”
- “ትውስታዎቼ መራር ናቸው”- ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ
ምርጫ 2007
ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት ለማካሄድ እየተዘጋጀችበት ካለው ምርጫ በፊት ያደረገችው የመጨረሻ ምርጫ ነው።
- በመራጭነት የተመዘገበ ሕዝብ 36 ሚሊዮን 851 ሺህ 461 ነው።
- ከተመዘገበው ሕዝብ ውስጥ የመረጠው ቁጥር 34 ሚሊዮን 351 ሺህ 444 ሲሆን፤ በመቶኛ ሲሰላ 93.2 በመቶ ድምፅ ሰጥቷል።
- በምርጫው ላይ የተወዳደሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ብዛት 58 ነበር።
- 1 ሺህ 828 ተወዳዳሪ ዕጩዎች ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበዋል።
- 3 ሺህ 991 ተወዳዳሪ ዕጩዎች ለክልል ምክር ቤቶች ቀርበዋል።
- ከላይ የተጠቀሱት የዕጩዎች አሃዝ የተለያዩ ፓርቲዎችን ወክለው ሲሆን በግል ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዘጠኝ እና ለክልል ምክር ቤት ሦስት ተወዳዳሪ ዕጩዎች ቀርበዋል።
- ውጤቱን በምንመለከትበት ጊዜ ኢህአዴግ 500 ወንበሮችን፣ በመቶኛ ሲሰላ (82.4) አግኝቷል። ከዚህ ቁጥር ውስጥ 212 ወይም 38.8 በመቶው ሴቶች ናቸው።
- የክልል ምክር ቤቶችን ስንመለከት ደግሞ ኢህአዴግ እና የተለያዩ አጋር ድርጅቶች ሁሉንም መቀመጫዎችን አግኝተዋል።
- ከነዚህም ውስጥ 800 ወይም 40.3 በመቶው የሚሆኑት ሴቶች ናቸው።
ምርጫ 2002
ታሪካዊ የሚባለውን ምርጫ 1997ን አልፎ የተደረገው የ2002 አራተኛው ዙር ጠቅላላ ምርጫ የተከናወነው ግንቦት 15/2002 ነበር። ምርጫው በሁሉም ክልሎችና በሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች ተከናውኗል።
- 63 የፖለቲካ ፓርቲዎች ተሳትፈዋል።
- እነዚህ ፓርቲዎች 2 ሺህ 188 ተወዳዳሪ ዕጩዎችን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አቅርበዋል።
- ለክልል ምክር ቤቶች ደግሞ 4 ሺህ 746 ዕጩዎች አቅርበዋል።
- 34 የግል ዕጩዎች ለተወካዮች ምክር ቤት በተወዳዳሪነት ቀርበዋል።
- 11 የግል ዕጩዎች ለክልል ምክር ቤቶች በተወዳዳሪነት ቀርበዋል።
- በመራጭነት የተመዘገበ ሕዝብ ብዛት 31 ሚሊዮን 926 ሺህ 520 ነው።
- ከተመዘገበው ውስጥ የመረጠው 29 ሚሊዮን 832 ሺህ 190 ወይም 93.4 በመቶ የነበረ ሲሆን፤ የሴት መራጮች ቁጥር 47.6 በመቶ ነው።
- በአጠቃላይ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ ምርጫ በተካሄደባቸው 547 የምርጫ ክልሎች ኢህአዴግ በአራቱ የግንባሩ ድርጅት እና አጋር ድርጅቶች በኩል 99.6 በመቶ መቀመጫዎችን አሸንፏል።
- ቀሪው በአንድ ፓርቲ ተወካይ እና በግል ተወዳዳሪ ተይዟል።
- የክልል ምክር ቤቶችን ስንመለከት ኢህአዴግ እና አጋር ድርጅቶች ሙሉ በሙሉ መቀመጫዎችን አግኝተዋል።
- ከእነዚህም መካከል በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሴቶች አሃዝ 12.4 በመቶ ነበር።
- በክልል ምክር ቤት ደግሞ መቀመጫ ያገኙ ሴቶች ቁጥር 15.3 በመቶ ነበር።
ምርጫ 1997
በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የ1997 ዓ.ም ምርጫ እንደ ትልቅ ምዕራፍ የሚታይ ነበር።
የፖለቲካ ምሀዳሩ ከሌላው ጊዜ በተለየ ከፈት ማለቱና በተለያዩ የፖሊሲ አማራጮች ዙሪያ የተካሄዱት የጦፉ ክርክሮች፣ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተጣምረው ጥምረቶችን ፈጥረው መምጣትና የምርጫ ቅስቀሳዎች ሂደቱን አጓጊ አድርገውት ነበር።
- በመራጭነት የተመዘገበ ሕዝብ 27 ሚሊዮን 372 ሺህ 888 ነበር።
- ከተመዘገበው ውስጥ የመረጠው ሕዝብ ቁጥር 22 ሚሊዮን 610 ሺህ 690 ነው።
- ኢህአዴግ 327 የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫን አሸንፏል።
- ቅንጅት ለአንድነት እና ለዴሞክራሲ (ቅንጅት) 109 መቀመጫዎችን፣
- የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ኅብረት (ኅብረት) 52 መቀመጫዎችን፣
- የኦሮሞ ፌዴራሊስት ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኦፌዴን) 11 መቀመጫዎችን አሸንፈዋል።
- የኢህአዴግ አጋር ድርጅቶች እና ሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች የተቀሩትን መቀመጫዎች አግኝተዋል።
- የክልል ምክር ቤቶች በተመለከተ በኦሮሚያ ክልል ኢህአዴግ/ኦህዴድ 387፣ ኅብረት 105፣ ኦፌዴን እና ቅንጅት 43 መቀመጫዎችን ማግኘት ችለዋል።
- በአማራ ክልል ኢህአዴግ (ብአዴን) 187፣ ቅንጅት 107 መቀመጫዎችን አግኝተዋል
- በትግራይ ኢህአዴግ (ህወሓት ) 151 መቀመጫዎቸን አሸንፏል።
- በአፋር አብዴፓ 84፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ ጋምቤላ፣ ሶማሌ እና ሐረሪ የኢህአዴግ አጋር ድርጅቶች አብዛኛውን መቀመጫዎች ሲያገኙ በጋምቤላ፣ ቤንሻንጉል እና ሐረሪ ቅንጅት ስድስት መቀመጫዎችን አሸንፏል።
ምርጫ 1992
- በመራጭነት የተመዘገበ ሕዝብ 21 ሚሊዮን 655 ሺህ 752 ነበር።
- ከተመዘገበው ውስጥ የመረጠው ሕዝብ ቁጥር 19 ሚሊዮን 602 ሺህ 783 ነው።
- የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫን በዋነኝነት ያሸነፈው ኢህአዴግ ሲሆን በአራቱ የግንባሩ ፓርቲዎች መካከል የነበረው የድምፅ ክፍፍልም ኦህዴድ 176፣ ብአዴን፣ 124፣ ህወሓት 38፣ ደኢህዴን ሁለትመቀመጫዎችን ማግኘት ችለዋል።
- 13 ቀሪዎቹ መቀመጫዎች የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች አሸንፈዋል።
- የክልል ምክር ቤት መቀመጫዎችን ስንመለከት ደግሞ ኢህአዴግ 1 ሺህ 102 መቀመጫዎችን በሁሉም ክልሎችና እና አስተዳደሮች ሲያሸንፍ፤ 27 የግል ተወዳዳሪዎች በተለያዩ ክልሎች ላይ መቀመጫዎች አግኝቷል።
ምርጫ 1987
- በመራጭነት የተመዘገበ ህዝብ 21 ሚሊዮን 337 ሺህ 379 ነበር።
- ከተመዘገበው ውስጥ የመረጠው ሕዝብ ቁጥር 20 ሚሊዮን 68 ሺህ 513 ነው።
- በአጠቃላይ የፖለቲካ ፓርቲዎችንና የግል ተወዳዳሪዎችን ጨምሮ 536 ወንዶች የምክር ቤት መቀመጫ ሲያገኙ፣ 10 ሴቶች ደግሞ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫን ማግኘት ችለዋል። ከአጠቃላዩ ተመራቾች መካከል 10ሩ የግል ተወዳዳሪዎች ነበሩ።
- የክልል ምክር ቤቶችን ስንመለከት 1 ሺህ 355 ወንዶች እና 77 ሴቶች በዘጠኙ ክልሎች ባሉ የክልል ምክር ቤቶች ውስጥ መቀመጫ ማግኘት ችለዋል።
- ከእነዚህ መካከልም 47 የግል ተወዳዳሪዎች ነበሩ።
- በዚህ ምርጫ 43 የፖለቲካ ፓርቲዎች ተሳትፈዋል ።
ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ