March 24, 2021 – Konjit Sitotaw

የኤርትራ ወታደሮች ከወሰዱዋቸው ንብረቶች ውስጥ የአክሱም ቤተ ክርስትያን ጳጳስ አቡነ መቃርዮስ ንብረት የሆነች ቶዮታ መኪና ወታደሮቹ ኅዳር 15 ቀን 2013 ዓ.ም. ወደ ሃገረ ስብከቱ ጽሕፈት ቤት ድረስ በመሄድ የወሰድዋት እና “የሃገረ ስብከቱ ንብረት የሆነች ኮድ 5 (ታርጋ ቁጥር 02223) መኪና 4 ጎማዎችንና አንድ የመኪናዋ ኮምፒተር በመፍታት እንደወሰዱ የቤተክርስትያኗ አገልጋዮች ለኮሚሽኑ ገልጸዋል። ሁኔታውን ለመከላከያ ሠራዊት አካላት ብናሳውቅም እስካሁን ምላሽ አላገኘንም” ብለዋል።
ታኅሳስ 14/2013 የኤርትራ ወታደሮች ወደ አክሱም ቅ/ማርያም ፅዮን ቤተ ክርስትያን ገብተው ለመዝረፍ ያደረጉትን ሙከራ የመከላከያ ሠራዊት አባላትና ህዝቡ ተባብሮ እንደተከላከለው ምስክርነታቸው የሰጡ ነዋሪዎችና የቤ/ክ አገልጋዮች አሉ።
‹‹ህዳር 21 ቀን የማርያም ፅዮን ዓመታዊ ክብረ በዓል በቤተክርስትያኑ ቅጥር ግቢ ታስቦ ቢውልም፤ በከተማው የደረሰው ሀዘን ግን ክብረ በአሉን በዘገቡት ሚዲያዎች አልተነገረም›› በማለት ነዋሪዎች ቅሬታቸውን ይገልጻሉ፡፡
በሲቪል ሰዎች ላይ ከደረሰው የሞት እና የአካል ጉዳት በተጨማሪ የሃይማኖት ተቋማትና የግለሰብ መኖርያ ቤቶችን ጨምሮ ሌሎች የንብረት ጉዳቶች ደርሰዋል። ኅዳር 19 ቀን 2013 ዓ.ም. ከጠዋቱ 2፡00 ሰዓት ገደማ እስከ ረፋዱ 11፡00 ሰዓት ቁጥራቸው ያልታወቁ የኤርትራ ወታደሮች በቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስትያን ውስጥ ባለው የመቃብር አከባቢ ሆነው የቤተክርስትያኑን ሕንፃ ለማፍረስ በትግርኛ “ህረሞ … ህረሞ … “ (በለው… በለው)እያሉ በጥይት ሲደበድቡት እንደዋሉ ቤተ ክርስትያኑ ውስጥ ተጠልለው የነበሩ የዓይን እማኞች ለኮሚሽኑ ገልጸዋል።
የአይን እማኞች እንዳስረዱት በርካታ ሲቪል ሰዎች ልጆቻቸው፣ ሚስቶቻቸው እና እናቶቻቸው ፊት ጭምር በአሰቃቂ ሁኔታ እንደተገደሉ ይናገራሉ። የኤርትራ ወታደሮች ቤት ለቤት እየዞሩ “ባልሽ የት አለ፣ ልጅሽ የት አለ፣ ወንድ ልጅ ካለ አውጪው” እያሉ በትግርኛ ይጠይቁ እንደነበርና ሲቪል ወንዶች “መሳርያ የለንም አልታጠቅንም እያሉ ቢማፀኑም ወንዶችን ከቤት እያስወጡ ሌሎች ደግሞ ቤት ውስጥ እያሉ ባሰቃቂ መንገድ ገድለዋቸዋል። የተጎጂዎች ቤተሰቦችና የአይን ምስክሮች አጥቂዎቹ የኤርትራ ወታደሮች መሆናቸውን በሚናገሩት የትግርኛ ቋንቋ ዘየ፣ በለበሱት የኤርትራ ወታደራዊ ዩኒፎርምና ጫማ፣ እንዲሁም አንዳንዶቹን ወታደሮች ፊታቸው ላይ ባላቸው ባህላዊ ምልክት ጭምር ማወቅ መቻላቸውን ገልጸዋል።