
በሰሜን ሸዋ ዞን በአጣዬ ከተማና አካባቢው ተከስቶ የነበረው ግጭት ተረጋግቶ አንጻራዊ ሰላም ቢፈጠርም ጠብአጫሪ ኃይሎች ማህበረሰቡ ወደ ጦርነት እንዲገባ እየሰሩ መሆኑ ተገለፀ፡፡በአካባቢው የተቋቋመው ኮማንድ ፖስት ከሰሜን ሸዋ ዞን እና ከኦሮሞ ማህበረሰብ አስተዳደር ዞን አመራሮች ጋር በመሆን የሰላምና ደህንነት እቅድ አፈፃፀሙን እየገመገመ ነው፡፡በዚህም በአካባቢው ግጭት ከተከሰተ በኋላ ኮማንድ ፖስቱ የሕግ የበላይነትን ለማስከበርና ዳግም ግጭት እንዳይከሰት ለመከላከል እንዲሁም ዜጎችን መልሶ ለማቋቋም እየሰራ ቢሆንም አንዳንድ አካላት የሀሰት ፕሮፖጋንዳ በመንዛት በተለይም በፋሲካና በዒድ በዓላት ላይ ግጭት እንዲፈጠር ሲሰሩ እንደነበር ተገልጿል፡፡በሰሜን ሸዋ ዞንና በኦሮሞ ማህበረሰብ አስተዳደር ዞን መካል የተለያዩ ውይይቶች መካሄዳቸውን የጠቀሱት የኮማንድ ፖስቱ አስተባባሪ ሌ/ ጄነራል ደስታ አቢቹ በውይይቶቹ የአካባቢው ማህበረሰብ ሰላም እንዲፈጠር እንደሚፈልግ መግለፁን ተናግረዋል፡፡ነገር ግን በሁለቱም ዞኖች አንዳንድ ወረዳዎች አመራሮችና ነዋሪዎች መካከል የነበረው የጣት መቀሳሰር ችግሮች መኖራቸውን ተማምኖ ወደ ሰላም ለመጓዝ እንቅፋት ሆኖ እንደነበር ገልጸዋል፡፡
–

በተለይም አመራሩ ከግጭቶች ጀርባ ሆኖ ችግሮች እንዲባባሱ ሲያደርግ እንደነበረ ተናግረዋል፡፡ተፈናቃዮች ወደ ቀዬአቸው እየተመለሱ መሆኑና ቀሪዎቹንም ለመመለስ ከስምምነት ላይ መደረሱ እንዲሁም ተፈናቀዮቹ የደህንነት ዋስትና እንዲረጋገጥ እየጠየቁ መሆናቸው ተገልጿል፡፡በግጭቱ እጃቸው አለበት ተብለው የተጠረጠሩ ግለሰቦችን ጉዳይ የሚመረምር ከሚመለከታቸው የክልልና የፌደራል አካላት የተውጣጣ ቡድን ወደ አካባቢው መግባቱ የተገለፀ ሲሆን በአመራሮች ዘንድ ግን ተጠርጣሪዎችን ለሕግ አሳልፎ ያለመስጠት አዝማሚያ እየተስተዋለ ስለመሆኑም ተነግሯል፤ ይህም አመራሮቹ በወንጀል ተሳታፊ በመሆናቸው እንደሆነ ነው የተጠቆመው፡፡
–
በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታና ግድም ወረዳ አጣዬ ከተማና በኦሮሞ ማህረሰብ አስተዳር ዞን አዋሳኝ ወረዳዎች ከሳምንታት በፊት በተፈጠረው ግጭት በሰው ሕይወት እና በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱ ይታወሳል፡፡EBC