መነሻ ገጽ
መንግሥት ለሩዝ ምርት አመቺ የሆኑ መሬቶችን በማመቻቸት የአገሪቱን ከምርቱ ተጠቃሚነት እንዲያሰፋ ተጠየቀ

ማኅበራዊ

መንግሥት ለሩዝ ምርት አመቺ የሆኑ መሬቶችን በማመቻቸት የአገሪቱን ከምርቱ ተጠቃሚነት እንዲያሰፋ ተጠየቀ

23 May 2021 ኤልያስ ተገኝ

በኢትዮጵያ አንዱ የሥርዓተ ምግብና የገቢ ምንጭ  አካል እየሆነ ለመጣው የሩዝ ሰብል ምርት፣ መንግሥት አስፈላጊ የሆኑ መሬቶችን በማመቻቸት የአገሪቱን ከምርቱ ተጠቃሚነት እንዲያሰፋ ተጠየቀ፡፡

የምሥራቅ አፍሪካ ሩዝ ልማት ኮንፍረንስ ከግንቦት 10 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ለሦስት ተከታታይ ቀናት በጃፓን ዓለም አቀፍ የትብብር ኤጀንሲ (JICA)፣ ቅንጅት ለአፍሪካ የሩዝ ልማት (CARD) እና ሌሎች ተቋማት አመቻችነት በበይነ መረብ ሲከናውን ቆይቷል፡፡

በኮንፍረንሱ ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ ሌሎች የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች በሩዝ ልማት እንቅስቃሴ ላይ በየአገራቸው ያለውን ተሞክሮና ቀሪ የቤት ሥራዎች አንስተው አቅርበዋል፡፡

በአፍሪካ የግብርና ፖሊሲ ምርምር ተቋም (APRA) የኢትዮጵያ ቢሮ ኃላፊ የሆኑት ዳዊት ዓለሙ (ዶ/ር) እንዳስታወቁት፣ በኢትዮጵያ የሩዝ ምርት የተሻለ የተጠቃሚነት ዕድል እያገኘ ቢመጣም፣ ዘርፉን እንዲስፋፋ የሚረዳ የምክር አገልግሎትና በቂ የሆነ የሩዝ ማቀነባበሪያዎች አለመኖራቸውን አስረድተዋል፡፡

አገሪቱ ለሩዝ ምርት ምቹ የሆነ የአየር ፀባይ እንዳላት ያስታወሱት ዳዊት (ዶ/ር)፣ ነገር ግን መንግሥት ዘርፉ ከምግብ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ እንዲቀርብ ለኢንቨስትመንት ምቹ የሆኑ ሰፋፊ የእርሻ መሬቶች የሚቀርብበትን ዕድል ሊያመቻች እንደሚገባ አስታውቀዋል፡፡

በኢትዮጵያ ሩዝን ከግል ባላሀብቶች ጋር አጣምሮ የመሥራቱ ልምድ ዝቅተኛ እንደሆነ በበይነ መረብ ስብሰባው ወቅት የተገለጸ ሲሆን፣ የግል ባለሀብቶች በዘርፉ ላይ መሰማራታቸው በፋይናንስም ሆነ ሜካናይዝድ የሆነ ምርትን ከማምረት አንፃር አስተዋጽኦው ከፍተኛ እንደሆነ ተገልጿል፡፡

በግብርና ሚኒስቴር የሰብል ልማት ዳይሬክተርና የብሔራዊ ሩዝ ልማት ቴክኒካል ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ኢሳያስ ለማ እንደገለጹት፣ መንግሥት ወጣቶችና ሴቶችን ማዕከል ያደረገ የሩዝ እርሻ ልማት ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸው፣ እነዚህ ወጣቶችና ሴቶች ግን በቂ የሆነ የብድርና ሌሎች ድጋፎችን ባለማግኘታቸው ምርታማነታቸው በቂ ነው የሚባል እንዳልሆነ አስታውቀዋል፡፡

በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ በአነስተኛ ደረጃ የሚገኙ ዜጎች በሩዝ እርሻ ልማት የመሰማራት ፍላጎታቸው ከፍተኛ እንደሆነ ያስረዱት አቶ ኢሳያስ፣ ከፋይናንስ ተቋማት በተለይም ከባንኮች የሚያገኙት ድጋፍ ምንም አለመሆኑ አንዱ ሳንካ እንደሆነ ገልጸው፣ በአገር አቀፍ ደረጃ የተቋቋመውን ብሔራዊ በሩዝ ዙሪያ የሚመለካተቸው አካላት ያሉበትን መድረክ ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡

መንግሥት በተለያየ መልኩ ከውጭ የሚገባውን የሩዝ  ምርት በአገር ውስጥ ለመተካት ብሔራዊ የሩዝ ምርምር እንዲሁም የሩዝ ዘርፍ ልማት ስትራቴጂ እንዳዘጋጀ የተገለጸ ሲሆን፣ ከሰው ኃይል ብቃት፣ መሠረተ ልማትና ተቋማት መጠናከር ጋር በተያያዘ አተገባበሩ ላይ ችግር እንዳለ በመግለጽ፣ በቀጣይ ይህንን ከክልል እስከ ማዕከላዊ ድረስ የማጠናከር ሥራ እንደሚሠራ ተጠቁሟል፡፡

ሩዝ የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ አንፃር ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ እንደሚገኝ የተገለጸ ሲሆን፣ በኢትዮጵያ እንደ ፎገራ ባሉት አካባቢዎች በምግብ ዋስትና ራሳቸውን ካልቻሉ አከባቢዎች በሸገር የምግብ ዋስትና ችግር በሌለባቸውም አካባቢዎች ጭምር አንዱ መሠረታዊ የምግብ እህል እየሆነ እንደመጣ  ተገልጿል፡፡

አፍሪካ በዓለማችን ቁጥር አንድ የሩዝ ተጠቃሚ ያለባት አኅጉር ስትሆን፣ በየዓመቱም ሩዝን ከውጭ አገሮች ለማስገባት ከአምስት እስከ ስድስት ቢሊዮን ዶላር እንደምታወጣ ጥናቶች ያሳያሉ፡፡FacebookTwitterTelegramGmail