May 31, 2021


‹‹አሜሪካ ታረቁ እንጂ ጣልቃ ልግባ አላለችም ›› -ኦፌኮ  – Ethio FM

ኦነግ በበኩሉ ‹‹ የአሜሪካ ውሳኔ ችግሩ ለኢትዮጲያ ብቻ ሳይሆን ለአሜሪካም አደገኛ ስለሚሆን በጥንቃቄ እንዲይዙት ተናግረናል›› ብሏል፡፡

“አሜሪካዊያን ኢትዮጲያን ንቀዋታል ” የሚሉት ደግሞ የፖለቲካው ምሁር ዶ/ር አለማየሁ አረዳ ናቸው፡፡

የኦፌኮው ተቀዳሚ ሊቀመንበር ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና ‹‹አሜሪካዊያኑ ታረቁ ፣ ተስማሙ እንጂ ጣልቃ እንግባ ፣ ወታደር እና ጦር መሳሪያ እንላክ አላሉም ›› ይላሉ፡፡

‹‹ባለስልጣናት በየመድረኩ እና በየመገናኛ ብዙሃን ስለሚያስተላልፉት መልዕክት ሊጠነቀቁ ይገባል›› ብለዋል፡፡

ፕሮፌሰሩ ‹‹ባለስልጣናቱ የሚሉትና የአሜሪካ ሃሳብ ትርጉሙ ለየቅል ነው ፡፡ ጣልቃ ገቡ ወይስ አትጫረሱ አሉ ?›› ብለው ይጠይቃሉ፡፡ አያይዘውም የራሳቸውን አስተያየት ይሰነዝራሉ፡፡

‹‹ታረቁ እያሉ ነው መልዕክታቸው ብሔራዊ መግባባትን አስቀድሙ ነው ችግሩ የትግራይ ብቻ አይደለም በኦሮሚያም ፣ በአማራም ፣ በደቡብም ፣ በቤንሻንጉልም ችግሮች አሉ እርሱን ፍቱት እያሉ ነው ፡፡

ከዚህ በፊትም በሀገሪቱ አሁናዊ ችግሮች እና በምርጫ ጎዳዩች ላይ ከአሜሪካው ልዩ መልዕክተኛ ጋር መነጋገራቸውን የነገሩን ፕሮፌሰር መረራ ‹‹ስለ ብሔራዊ ዕርቅ ስንናገር አንዴ ‹ማን ከማን ተጣልቶ ነው የሚታረቀው? ›ሲሉን በሌላ ጊዜ ደግሞ ምንም እንዳልተፈጠረ ሲሆኑ ነበር አሁን በፈረንጅ አፍ ሲሆን ለምን ከበደ? ይላሉ፡፡

በአቶ አራርሳ ቢቂላ የሚመራው ኦነግ ቃል አቀባ አቶ ቀጀላ መርዳሳ በበኩላቸው ‹‹በሀገሪቱ ላይ እንዲህ አይነት ከባድ ችግር ሲጋረጥ በጋራ መቆም ያስፈልጋል እንጂ በውጪ ሀገር ሲለሚኖሩ ብቻ መፈንደቅ ነውር ነው ›› ብለዋል፡፡

‹‹መንግስትን መቃውም ይቻላል በሀገር አንድነት ግን መደራደር ፈጸሞ ተገቢ ያልሆነ አሳፋሪ ተግባር ነው›› በማለት ያክላሉ፡፡

‹‹ከአሜሪካዊያን ጋር እየተነጋገርን ነው ነገሮችን በጥንቃቄ እንዲይዙት አስጠንቅቀናል ›› ብለዋል አቶ ቀጀላ፡፡

ቃል አቀባዩ በትግራይ ጉዳይ የውጪ ሀይል ጣልቃ እንዳይገባ ጥንቃቄ እንዲደረግ ሲያሳስቡ እንደነበር ገልጸው የአሜሪካ ፍላጎትም በደንብ መጤን እና መታየት አለበት በማለት ያሳስባሉ፡፡

‹‹አሜሪካዊያን ኢትዮጲያን ንቀዋታል›› የሚሉት ደግሞ የፖለቲካው ሞሁር ዶ/ር አለማየሁ አረዳ ናቸው፡፡

ኢትዮጲያ የውስጥ ችግሮቿን ለመፍታት እየጣረች መሆኑን የሚናገሩት ዶ/ር አለማየሁ ኢትዮጵያን በግድ አንበረክካታለሁ ብሎ ማሰቡ ግን ስህተት ነው ብለዋል፡፡

‹‹የኢትዮጵያና የአሜሪካ ግንኙነት ረዥም ዘመናት ያስቆጠረ ከመሆኑ አንፃር ይሄንን በድጋሚ ያጤኑታል ብዬ አስባለሁ›› ብለዋል፡፡

የኤርትራ ወታደሮችና የአማራ ኃይሎች ከትግራይ ክልል በአስቸኳይ እንዲወጡም የአሜሪካው ፕሬዝደንት ጆን ባይደን በድጋሚ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

አሜሪካ በሕዳሴው ግድብ ዙሪያ የሁሉንም ሀገሮች ፍላጎት ያማከለ ስምምነት እንዲደረስ ጠይቀዋል፡፡

አምባሳደር ጄፍሪ ፌልትማን በድጋሚ ወደ ኢትዮጵያ እና ወደሌሎች የቀጣናው ሀገራት እንደሚያቀኑም ፕሬዝደንት ባይደን ገልጸዋል፡፡

Ethio FM