ፖለቲካ

4 May 2022

በጋዜጣዉ ሪፓርተር

እናት ፓርቲ በሰሞኑ ግጭት የተሳተፉ፣ ያባባሱ፣ የዕልቂት አዋጅ ነጋሪዎች፣ ባለሥልጣናት፣ ተቋማትና የመገናኛ ብዙኃን ያላቸው ተሳትፎ በውል ተጣርተው ሕግ ፊት እንዲቀርቡ ጥያቄ አቀረበ፡፡

በተለይም የሰሞኑ ክስተት ጉዳይ ሃይማኖታዊ ይመሰል እንጂ በጥንቃቄ የተቀናበረና ዓላማውም ኢትዮጵያን የማፍረስ ተልዕኮ መሆኑን ተረድቶ፣ ሁሉም አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ አገሩን ከጥፋት ጠንሳሾች ሴራ ለመታደግ ያለማንም ቀስቃሽ ዘብ እንዲቆም ፓርቲው ጠይቋል፡፡

ባለፈው ሳምንት በጎንደር ከተማ በተፈጸመ ጥቃት ሰዎች መሞታቸውንና ንብረት መውደሙን ፓርቲው ማክሰኞ ሚያዝያ 25 ቀን 2014 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ የተዳሰሰ ሲሆን፣ ይህንኑ ተከትሎ ጉዳይን በውል በማይረዱ፣ በዓላማ ጭምር መንግሥታዊ መዋቅርን ለጥፋት ተልዕኮ በሚጠቀሙ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የሃይማኖት አክራሪዎች የዕልቂት ድግስ ቅስቀሳዎች፣ ከፍተኛ መናበብና የቀደመ ዝግጅት መኖሩን በሚያረጋግጥ መንገድ በማግሥቱ ስልጤ ዞን፣ ወራቤ ከተማና አካባቢው አብያተ ክርስቲያናት እንደተቃጠሉና ምዕመናን በግፍ እንደተገደሉ አስረድቷል፡፡

ፓርቲው እንዳስታወቀው በአዲስ አበባ፣ በድሬዳዋ፣ በሐረር፣ በጅግጅጋ የሴራው ጭስ የታየ ቢሆንም በክርስቲያኑና በሙስሊሙ ትብብር ከስሟል፡፡ ክስተቱ የመጪው ጊዜያት የአገሪቱን ዕጣ ፈንታ ፍንትው አድርጎ ያሳየ ሆኗል ያለው እናት ፓርቲ፣ በክስተቱ የተሰማውን አዘኔታ ገልጾ፣ በዚህ የጥፋት ዘመቻ ወቅት በጎንደርና ወራቤ ከተማ ጥቃት የተሰነዘረባቸው ወገኖች ሲሳደዱ በየቤታቸው አስገብተው ከጥቃት በመታደግ ኢትዮጵያዊ ከፍታቸውን በመከራ ወቅት ላሳዩ ወገኖች ምሥጋና አቅርቧል፡፡

እንደ ኢትዮጵያ የቆዩና ዘለግ ያለ ታሪክ ያላቸው አገሮች  በአንድ ገጽ ብቻ የሚነበብ ሳይሆን በተለይ በሁለቱ ቤተ እምነቶችና ምዕመናን ዘንድ ያለ፣ የነበረና የሚኖር መከባበርና መፋቀር፣ ጥልቅ የሰዋዊና ሥነ ምግባር አስተምህሮቶች፣ አብረሃማዊ መሠረቶችን አጽንቶ የማቆየትና የማስቀጠል ልማድ በልዩነት ሊጠቀስ የሚችል እንደሆነ ፓርቲው አስታውሷል፡፡

በዚህ ወቅት በእነ ግብፅ፣ አልሸባብና መሰሎቻቸው ረዥም እጆች፣ በሌላ በኩል  ደግሞ ትሕነግ፣ በሕጋዊና ሃይማኖተኝነት ጭንብል የሚንቀሳቀሱ መሰል የቅርብ ግን ደግሞ የጭቃ ውስጥ እሾኮች እንዲሁም ከሃይማኖት አባቶች ተግሳጽ መጓደል የሃይማኖተኝነት እሴት በአደገኛ ሁኔታ እየተሸረሸረ ጭራሽ አገርን ወደ ከባድ አዘቅት ለመወርወር እያኮበኮበ እንደሚገኝ በፓርቲው መግለጫ ተመላክቷል፡፡

መንግሥት እንደ ተቋም በባለሥልጣናት በኩል በንግግርም ሆነ በተግባርም በሃይማኖት ተቋማት መሀል በሚፈጠር ግጭት ፖለቲካዊ ትርፍ የማትረፍ አዝማሚያውን በአፋጣኝ እንዲያቆም ያሳሰበው እናት ፓርቲ፣ ለግጭት ሰበብ የሚሆኑና መደላድል የሚፈጥሩ ምክንያቶችን በአብያተ እምነት ሊቃውንት በኩል በውል ተጠንተው በዳበረው የፍልስፍናና ችግር መፍቻ ዘዬ ተመክሮና ተዘክሮ ችግሩ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መፍትሔ የሚያገኝበትን ፍኖት እንዲተለም ጠይቋል፡፡

እናት ፓርቲ የሰሞኑን የጥፋት ድግስ ያለውን ጉዳይ በቅርበት ሲከታተለው እንደቆየ አስታውቆ፣ አሰባሰብኩት ባለው ማስረጃ መሠረት ሰሞነኛው ጉዳይ ለአገር አንድነት የሚቆሙ የሃይማኖት ተቋማትን በማፍረስ አገርን ወደ ማፍረስ የሚወስድ ተልዕኮ እንጂ ሃይማኖታዊ ግጭት አለመሆኑን አስረድቷል፡፡

በተያያዘም ፓርቲው ባወጣው መግለጫ በደቡብ ክልል በደራሼ ልዩ ወረዳ፣ ጊዶሌ ከተማና አካባቢው በዚሁ ሰሞን ‹‹የጠየቅነውና ቃል የተገባልን ለምን አይፈጸምም?›› በሚል መነሻና በአስተዳደሩ እንዝህላልነት ችግር የሰው ሕይወት መጥፋቱና ንብረት መውደሙ እንዳሳዘነው ገልጿል፡፡

ደራሼና መሰል የመዋቅር ጥያቄ ያላቸው አካባቢዎች የምርጫ ካርድ ለማግኘት ሲባል አጓጉል ቃል በመግባት ሳይሆን ጥያቄዎቹ ሕግንና ሕግን ተከትሎ አፋጣኝ ምላሽ እንዲያገኙ፣ ብሎም የአካባቢው አስተዳደር ሰላማዊ ጥያቄዎችን በአፈሙዝ ከማስተናገድ እንዲቆጠብ በአጽንኦት ጠይቋል፡፡

ፓርቲው አክሎም ደራሼና መሰል የመዋቅር ጥያቄ ያላቸው አካባቢዎች የምርጫ ካርድ ለማግኘት ሲባል አጓጉል ቃል በመግባት ሳይሆን፣ ጥያቄዎቹ ሕግንና ሕግን ተከትሎ አፋጣኝ ምላሽ እንዲያገኙ፣ እንዲሁም የአካባቢው አስተዳደር ሰላማዊ ጥያቄዎችን በአፈሙዝ ከማስተናገድ እንዲቆጠብ ጥያቄ አቅርቧል፡፡