ሲሳይ ሳህሉ

ቀን: September 14, 2022

አዲሱ የኬንያ ፕሬዚዳንት ዋሊያም ሳሞይ ሩቶ (ዶ/ር) በኢትዮጵያና በታላላቅ ኃይቆች ቀጣና  (Great Lakes Regions) አገሮች የጀመሩትን የሰላም ጥረት ሥራ ተሰናባቹ የኬንያ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ እንደሚያስቀጥሉ ተናገሩ፡፡

 ፕሬዚዳንቱ መስከረም 3 ቀን 2014 ዓ.ም. በበዓለ ሲመታቸው ላይ ባደረጉት ንግግር ‹‹ትልቁ ወንድሜና ሊመሠገን የሚገባ ሥራ የሠራው ኡሁሩ ኬንያታ የተጀመሩ ውይይቶችን በኬንያ ሕዝብ ስም በበላይነት እንዲመራው ተስማምተናል፣ እኔም የሚደረጉ ጥረቶችን እደግፋለሁ፤›› ብለዋል፡፡

 የኢትዮጵያ መንግሥት ከሕወሓት ጋር በገባው ጦርነት ላይ ለሚደረገው ድርድር፣ ሕወሓት በኬንያ ፕሬዚዳንት አማካይነት እንዲመራ በተደጋጋሚ ፍላጎቱን ሲገልጽ እንደነበር ይታወሳል፡፡

  ከአንድ ሳምንት በፊት የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት በድርድር ለመፍታት የአፍሪካ ኅብረት ከጀመረው ጥረት ውጪ ሌላ ተወዳዳሪ የሰላም ሒደት ለመጀመር የሚሞክሩ አካላት ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ መንግሥት ማሳሰቡ ይታወሳል፡፡

የሦስተኛ ዙር ጦርነት ከተጀመረ ጥቂት ሳምንታት በኋላ የአፍሪካ ኅብረትን አደራዳሪነት ላለመቀበል ዳር ዳር ሲል የነበረው ሕወሓት፣ መስከረም 1 ቀን 2015 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፣ በአፍሪካ ኅብረት ሥር ለመደራደር ዝግጁ መሆኑንና እንዲሁም በሁለቱ አካላት በሚደረግ ስምምነት በተመረጡ አደራዳሪዎችና ታዛቢዎች በመታገዝ ድርድሩ እንዲካሄድ እንደሚጠብቅ አስታውቋል፡፡

በነሐሴ 2014 ዓ.ም. በተካሄደውና ከፍተኛ ፉክክር በታየበት የኬንያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ ተቀናቃኛቸው የነበሩትን የቀድሞ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትርና የፓርላማው አባል ራይኤላ ኦዶንጋ በተቀራራቢ ውጤት በማሸነፍ የፕሬዚዳንታዊ ሥልጣን ማዕረግ የተቆናጠጡት ዊሊያም ሳሞይ ሩቶ (ዶ/ር) መስከረም 3 ቀን 2015 ዓ.ም. ካሳራኒ በተሰኘ ግዙፍ ሰታዲዮም በተዘጋጀ በዓለ ሲመት ቃለ መሐላ ፈጽመዋል፡፡

በፕሬዚዳንታዊ በዓለ ሲመቱ ላይ የኢትዮጵያ፣ የሩዋንዳ፣ ኡጋንዳ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ጂቡቲ፣ ዚምባቡዌና፣ታንዛኒያ፣ የአፍሪካ ኅብረት ሊቀመንበርና የሌሎችም አገሮች መሪዎች ተገኝተዋል፡፡ ቃለ መሐላ የፈጸሙት አዲሱ ፕሬዚዳንት ለአምስተኛ ጊዜ በተካሄው ምርጫ፣ ለአምስተኛ ጊዜ ለፕሬዚዳንትነት የተወዳደሩትና 48.8 በመቶ በመያዝ ተቀራራቢ ነጥብ ይዘው ሲከታተሉ የነበሩት ኦዲንጋ፣ ‹‹የምርጫ ውጤቱን አልቀበልም›› ማለታቸውን ተከትሎ የአገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የዊሊያም ሩቶን አሸናፊነት ካረጋገጠ አንድ ሳምንት ሆኖታል፡፡

የኬንያ ምክትል ፕሬዚዳንት የነበሩት ዊልያም ሩቶ (ዶ/ር) ከነበሩት አጠቃላይ ተወዳዳሪዎች በቅርብ ርቀት በነጥብ ሲከታተሏቸው የነበሩትን ኦዲንጋ 50.49 አብላጫ ድምፅ በመያዝ ነው ያሸነፏቸው፡፡

በናይሮቢ ከተማ በሚገኘው ትልቁ የስፖርት ማዕከል በተካሄደው በዓለ ሲመት፣ ነባሩ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ለአዲሱ ፕሬዚዳንት ዊልያም ሩቶ (ዶ/ር) ሥልጣናቸውን አስረክበዋል፡፡

በምርጫው ውጤትና ይግባኝ ባቀረቡበት የአገሪቱ ውሳኔ ያልተደሰቱት ኦዲንጋ በበዓለ ሲመቱ ላይ አለመገኘታቸው ተነግሯል፡፡