May be an image of 4 people and outdoors

Mulualem G. Medhin 

 · የኢትዮጵያ አዕማድ-ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ!

በዐዲስ አገር አላሚዎች የገጠማት ፈተና ምንድነው?…

(በሙሉዓለም ገ/መድህን)

***

ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን የታሪክ ሊቃውንት መዛግብት አጣቅሰው እንደሚያስተምሩት፣ ክርስትናን የተቀበለችው በመጀመሪያው ምዕተ-ዐመት ይሁን እንጂ፤ በሲኖዶስ ሕግ የኤጲስ-ቆጶስ መንበር የተሰጣት በአራተኛው ምዕተ-ዐመት ነው፡፡ በ350 ዓ.ም. ደግሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሃይማኖት ሆኖ ከተተከለ በኋላ፣ እስከ 1966 ዓ.ም. ቆይቷል፡፡

ሀገረ-መንግሥቱን በማበጀቱ ሂደት የነበራት አበርክቶም የትየሌለ ነው። በአልቦ-መንግሥታዊ ተቋማቱ ዘመንም፣ እልፍ-አእለፍ የሕዝብ አስተዳዳሪዎችን አብቅታለች። የዳኝነት ሥራውንም ያሳለጡ ፍርድ አዋቂዎች አፍርታለች። ተጽዕኖዋ በበዛበት በዛ ገናና ዘመኗም፣ ከአገራቸው ተገፍተው የተሰደዱ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮችን፣ ከእነ ዐዲሱ አስተምህሮቻቸው ከተወነጨፈባቸው ቀስት ከለላ ሆናለች።ይህ እንግዲህ የዴሞክራሲ ስሙ እንኳ በማይታወቅበትና ባህላዊ ሥልጣኔ በነገሠበት ድሮ መሆኑ፣ ለማመን ቢቸግርህ አይደንቅም።

ቤተ-ክርስቲያን በእነዚህ ዘመናት ሁሉ የኢትዮጵያ አዕማድ በመሆን ግዙፍ ማኀበራዊ ተቋምነቷን ያስመሰከረች አምሳለ-ሀገር ነች፡፡

በተለይ፣ የጠላት ወረራን ለመመከት በተደረጉ ተጋድሎዎች ከነበራት አበርክትዎ በተጨማሪ፤ እንግዳን ተቀብሎ በማስተናገድና የአገር ባለቤት በማድረጉ ረገድ ዓለም በኩራት የሚጽፍላት ክቡድ ታሪኳ ነው፡፡ በአፍሪቃም የሚተካከላት ጥንታዊ ተቋም አለመኖሩን ልብ ይሏል።

ይች የባህል አዋሃጇ እናት ቤተ-ክርስቲያን፡- በአህጉሪቱ ብቸኛ የሆነውን የሳባ ፊደል በመጠቀም፣ ግዕዝን የመንፈሳዊ አገልግሎቷ ቋንቋ በማድረግ፣ የጽሕፈት ባህልን በማዳበር፣ የራስ መለዮን እና የወል-ማንነትን በመቅረጽ አቻ-የለሽ ናት፡፡

በሥነ-መለኮት እና በዓለማዊ ዕውቀት የተራቀቁ ፓትርያርኮችን፣ ሊቃነ-ጳጳሳትን፣ ኤጲስ-ቆጶሳትን፣ ካህናትን፣ ሰባኪያንን፣ ዲያቆናትን፣ መምህራንን… የቀለም ቀንድ አድርጋለች። በአብነት ትምህርት የተጓዘችበት ርቀት ደግሞ፣ እጅግ ዘግይተን በ1900 ዓ.ም በዳግማዊ ዐፄ ምንሊክ በኩል የተዋወቅነው ዘመናዊ ትምህርት በቀላሉ መሬት እንዲረግጥ የነበራት አበርክቶዋ በአገር ባለውለታነት ያስጠራታል፡፡

እስከ 1935 ዓ.ም ድረስ ትምህርት ሚንስቴር ሆና፣ ከሁሉም እምነት ተከታዮች የወጡ ተማሪዎችን በአስኳላው ገርታለች፡፡ ማተሚያ ቤቶች ባልነበሩበት እልፍ ዐመታትም፣ አያሌ መነኮሳት መጽሐፍትን በራሳቸው መንገድ አባዝተው አሰራጭተዋል። ታሪካዊ ሰነዶችን፣ መንፈሳዊና ዓለማዊ መዛግብትን ሰንደው ዘመናትን አሻግረዋል። የኢትዮጵያን ብዝሃ-ታሪክ እና ቅርስን በማስፋፋቱ ረገድም ብሔራዊ ተቋም ነበረች፡፡

በረዥሙ ታሪኳም፣ ገዥዎች በተቀያየሩ እና የሕዝብ እንቅስቃሴዎች ገፍተው በመጡ ቁጥር የተፈራረቁ ፈተናዎችን ተቋቁማ፣ በካህናቶቿ ሐዋርያዊ ትጋት ክርስትናን በአራቱም ማዕዘናት በማስፋፋት የአገር ህላዊ አስቀጣይ ሆና ዘመናትን ዘልቃ፣ ለዛሬ ደርሳለች፡፡

ይህም ሆኖ፣ በውስጣዊም ሆነ በውጫዊ ጥንካሬና ድክመቶቿ የራሷን ወርቃማም ሆነ የጨለማ ዘመናት ማሳለፏ ባይካድም፤ በዚህ ልክ ለሁለንተናዊ ጥቃት ተጋላጭ መሆን ከጀመረች ግማሽ ክፍለ ዘመን እያካለለች ነው፡፡

ከአምስት ዐመቱ የጣሊያን ወረራ በኋላም የለጠቀው ፈተናዋ፣ በአገር በቀል ፋሽስቶች ተደግሞባታልና። የደርግ የዐሥራ ሰባት ዐመታት ፀረ-ሃይማኖት ፖለቲካዊ አስተዳደር ፈተናዎች ሳይዘነጉ፤ ቀኖናዊ ሥርዐቷን በሚጥስ መልኩ የፖለቲካ መዋቅሩ ጣልቃ-ገብነት ማየል የጀመረው ከድኀረ-1983 ወዲህ ነው፡፡

በርግጥም፣ ሕወሓት ለተጠናወተው ከፋፋይ የብሔር ፖለቲካ አደናቃፊነቷን አስልቶ፣ በነፍጥም በፍልጥም ከደርግ እኩል ታግሏታል። በመደብ ጠላትነት ፈርጆም አሳድዷታል። ይህን ተከትሎም፣ ቤተ-ክርስቲያን ፍሬ ነገሯን ለማስቀጠል የህልውና ትግል ላይ ናት፡፡ ኧረ እንዴውም ስደት ላይ ከርማለች።

በተለይ፣ የአስተምህሮት መምታታት እና መንፈሳዊ ተልዕኮን በቅጡ ያለመለየት ችግሮች የውስጣዊ ፈተናዋ አካል ሆነው ጎልተው መውጣታቸው፣ የቤተ-ክርስቲያኗን የህላዌ ትግል ጽኑ አድርጎታል፡፡

ይህ የከረረ የዘውግ-ብሔርተኝነት አራጋቢና ፀረ-ኦርቶዶክስ አገዛዝ፣ ቤተ-ክርስቲያኗን በብርቱ ቢፈትናትም፤ እጅ አለመስጠቷ፣ መከራዋን አክፍቶታል፡፡ በግልባጩ፣ የሀገረ-ስብከት አወቃቀሯ ለዘመናት የተሻገረው መልክዓ-ምድራዊነትና የመንፈሳዊ አገልግሎት አመችነትን ታሳቢ ያደረገ መሆኑ፣ ውስጣዊ አስተዳደሯን በብቸኝነት የምትመራው ቃለ-ዓዋዲን (ሕገ-ቤተ-ክርስቲያንን) መሰረት ያደረገ በመሆኑ፣ ለአክራሪ የዘውግ-ብሔረተኞች እንዳትመች አድርጓታል፡፡ በዚህም ሰርገው በገቡ ኃይሎች እና በተለያየ የፍላጎት ተቃርኖ በቆሙ የውጭ ቡድኖች የማያባራ ጥቃት ሲፈጸምባት ቆይቷል፡፡

ድኀረ-2010 አሕዛቡ ኢሕአዴግ ተነቅሎ፣ አንድ እግሩን ቤተ-መንግሥት ሌላውን ቤተ-እምነት የተከለው እና ፓርቲ ይሁን የሃይማኖት ድርጅት ግራ አጋቢው ‹ብልጽግና› ተተክቷል። ይህንን ተከትሎም፣ በአገሪቷ የፖለቲካ ዐደባባይ የታየው የለውጥ ተስፋ ቤተ-ክርስቲያንንም የጎበኘ ቢሆንም፤ ተስፋዋ ግምጃ በሚቀድ፣ ማቅ በሚያስለብሱ ፈተናዎች የተሞላ ሆኖ ለመታየት ሁለት ክረምት አልወሰደበትም።

በአጭር ጊዜ ውስጥ፣ በአንድ በኩል ኢትዮጵያን ለማፈራረስ፤ በሌላኛው ጫፍ ዐዲስ አገር የመሥራት ፕሮጀክት የያዘ ‹ተረኛ ነኝ› ባይ ኃይል በሁለት ጽንፍ ዒላማ እንዳደረጓት ይፋ ወጥቷልና።

በተለይ፣ ቤተ-ክርስቲያኗ ትኩረቷን የአገር አንድነት ላይ አድርጋ ስትሠራ የኖረች ግዙፍ መንፈሳዊ ተቋም ከመሆኗ አኳያ፣ ዐዲስ አገር የመሥራት ፕሮጀክት ያነገቡ አክራሪ ኃይሎች የጥቃት ሰይፍ መሰንዘራቸው ተገማች ነበር፡፡ ውስጣዊ አንድነቷን በማናጋት የሺሕ ዘመን ታሪኳን ለማውደም የቋመጡ የፖለቲካ ቡድኖች፣ የሃይማኖት ለምድ ለብሰው ከስር-መሰረቷ ሲገዘግዟት ስለመክረማቸውም ከ2010-2015 ዓ.ም ዐቢይ የምስክር ዘመናት ናቸው፡፡

በተለይም፣ ድምፅ-የለሹ የቅባት ኃይል የማንሰራራት ሙከራ (ቤተ-ክርስቲያኗ በአባቶች ብርታት የተሻገረችውን የአስተምህሮ ልዩነት ከተቀበረበት ለመፈልፈል መውተርተሩ) እና ‹‹የኦሮሚያ ቤተ-ክህነት አደራጅ ኮሚቴ›› ተብየው የአንድ ሰሞን ግርግርን ጨምሮ፤ አሁናዊው አቻ ሲኖዶስ ምስረታ… ዐዲስ አገር የማዋለድ ፕሮጀክት ማሳለጫዎች ናቸው።

አንዱ ሲከሽፍ በሁለተኛው፣ ሁለተኛው ሲዘጋ ሦስተኛ ቀውስ እየፈለፈሉ በብዙ ንጠዋታል፡፡ አምስተኛ ረድፉ ጽንፈኛም ከውስጥ ለመሰንጠቅ ሲጋጋጥ፣ ከደጃፏ ያደፈጠው ‘የስንዴ ሃይማኖት’ መዶሻ እያቀበለ ፈተናዋን አበርትተውታል።

እዚህ ጋ ብዥታ መኖር የሌለበት፣ አፍራሹ ቡድን ቁጥሩ የማይናቅ ቢሆንም፤ መዳረሻቸው ያፈጠጠና ያገጠጠ ኢ-ፍትሐዊነትን በብዙሃን ኢትዮጵያዊ ላይ መጫን ነው፡፡ የሁሉም ቡድኖች አምበል ደግሞ በተረኝነት ስሜት የተወጠረው ኃይል ነው፡፡

ይህ ኃይል፣ “ኢትዮጵያ ሐበሻ-ኦርቶዶክሳዊ ቀለም ያላት አገር በመሆኗ፣ ቀለሟን ለመቀየር አዕማዷን መናድ ይገባል፤” የሚል ግብ ካስቀመጠ ሰንብቷል። በተሰበረ ልብ ስንታዘባቸው የከረምነው አስጨናቂ ጊዜያቶችም የሚያስረግጡት ይህንኑ ነው።

የኦሮሙማው ቡድኑ ከሱታፌ ይልቅ፣ ሁሉንም የመጠቅለል ሰልቃጭነትን መለያው በማድረጉ፣ ተመክሮም ተዘክሮም የሚድን አይደለም፤ በእጁ የገባውን ሥልጣን ጭምር እንደ አጥፍቶ ጠፊ በራሱ ላይም እየተጠቀመበት ነውና።

በርግጥ፣ ይህ የአጥፍቶ የመጥፋት ጉዞ፣ በእነሱ የፖለቲካ ስሌት ዐዲስ አገር የማበጀቱ ቁልፍ አካል ተደርጓል።

በአጭሩ፣ “ኦሮሚያ” የተባለውን የኢትዮጵያ አንድ ግዛት የሚያስተዳድረው አካል State Terror elementsን እንዳሟላ ራሱን ያጋለጠባቸው የአብያተ-ክርስቲያናት ውድመት፣ ስለነገ ምን እንደሚያልም በግላጭ ያመላክታሉ።

[ተመክሮም ተዘክሮም የማይታረመው] የዐቢይ አህመድ አውዳሚ መንገድ…

ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አራት ኪሎን ከረገጠ ጀምሮ፡- ሲያሻው እንደ መሪ፣ ሲያሻው እንደ አክቲቪስት፣ ሲያሻው እንደ “ተቃዋሚ”፣ ሲያሻው እንደ ፓስተር… እየተወነ ወሳኝ ኃላፊነቶቹን ባለመወጣቱ፣ አገሪቱ ለተነከረችበት ቀውስ ዋንኛ መነሾ ነው፡፡ ለዚህም፣ ለፓርላማው “ተጠያቂነት የለብኝም” በሚል የሰጠው ንቀት-ወለድ ምላሽ፣ እነ ሊቀ-ሰይጣን ስብሃት ነጋን የፈታው ጌታ ነግሮት እንደሆነ ለማሳመን የሄደበት ርቀት፣ “በአዲስ አበባ ኦሮሞ ጠል ተከማችቷል” ሲል ግጭት ለመፍጠር መሞከሩ፣ ከአፈንጋጮቹ ጳጳሳትም በከረረ መልኩ ሰሞነኛውን ሁነት በቋንቋ የመጠቀም ጥያቄ በማስመሰልና ማኀበረሰቡን በሚያስቆጣና ለዐመጽ በሚገፋፋ ሁኔታ በመንግሥት ሚዲያ ልፋፌ መደጋገሙን ጨምሮ፣ አያሌ ማሳያዎችን መጠቀስ ይቻላል።

በዚህ መርህ-የለሽ ዝማሜው ሚሊዮኖች ተፈናቅለዋል፣ አስር ሺዎች ለመንጋ ፍረድ ተንጋልለዋል፡፡ በቢሊዎን የሚቆር የሀገር ሃብት ወድሟል፣ በመንደር የተደራጁ ወሮበሎች ሲሳይ ሆኗል፡፡ (ይህ ከአንድ ዙር በላይ [ከጥቅምት 24 እስከ ሕዳር 19/2013] መሻገር ያልነበረበትን የሰሜኑን ጦርነት መነሻና አሁናዊ መቋጫ የለሽነት ስውር ደባ አይጨምርም) ሌላው ሳይጠቀስ የማይታለፈው የጠቅላዩ አደገኛ አካሄድ፣ ለሁሉም ጥፋቶች ወይም ችግሮች “አቻ” ፈልጎ የማድበስበስና የጅምላ ፍጅትን ሳይቀር የማቃለል አባዜው ነው፡፡

ለቡራዩው ጭፍጨፋ፥ የግንቦት 7 አቀባበል ኮሜቴን፤ ለጃዋር መሐመድ፥ እስክንድር ነጋን፤ ለኦነግ፥ አብንን፤ ለሸኔ፥ ፋኖን… አቻ ማድረጉ የሙግቴ መደገፊያ ነውና፡፡

ሰሞኑን ደግሞ፣ በዚሁ በሚታወቅበት ፍርደ-ገምድልነቱ፣ የአገር ምስረታ ቅዥት ማስፈፀሚያ የሆነውን የተወገዘ ቡድን፣ የቅዱስ ሲኖዶሱ አቻ አድርጎታል።

የአካሄዱን መሰሪነት ለመረዳት፣ በሲኖዶሱ ካሉ 75 ጳጳሳት፣ 18ቱ ኦሮሞ ሲሆኑ፤ ያፈነገጡት ሦስት ብቻ መሆናቸውን ማየቱ በቂ ነው፡፡ በተቀረ፣ በላይኛው የመጨረሻ መዋቅር የሌሉ 3 “ጳጳሳት” መነጠላቸውን ይዘህ፤ ፓትርያርኩን ጨምሮ 72ቱ በኃላፊነታቸው መቀጠላቸውን እያየህ፤ ችግር ፈጣሪዎቹ ጳጳሳትም በቤተ-ክርስቲያኒቷ የቀኖና ሕግ ተወገዘው ከተባረሩ በኋላ፣ ጉዳዩን የሁለት አቻ ቡድን አድርጎ በድፍረት ለመናገር ዐቢይ አህመድን እና የ“መደመር”ን ሰባራ ካልኩሌተር መሆን ይጠይቃል፡፡

በአጭሩ፣ አቻ ሲኖዶስ ምስረታን በኃይል የበላይነት ለመደገፍ ቃታ እስከመሳብ የተለጠጠው እርምጃ፣ የቀውሱ ቡራኬ ሰጪ ማንነትንም ሆነ የጠቅላዩን የጥፋት ስልት በደንብ አፍታቶታል፡፡

በተረፈ፣ የግል “ነባያቶቹ”፡- “ማኀበሩ ለሁለት ይሰነጠቃል”፣ “በ2015 የእነሱን መከፋፈል እናያለን” ገለመሌ… እያሉ ስውሩን ሥራ አማናዊ ለማስመሰል የሄዱበት ርቀት እንደ ጀማሪ ዳይሬክተር ቀሽም ድራማ ነውና፣ ንቆ ማለፉ የተሻለ ነው፡፡

የ‹ጽድቅ እና ኩነኔ› ሚዛንንም፣ የግሉ ማድረጉን ዘንግቼው አይደለም፡፡ ይህ ኃይል ግን፣ የጥፋት አቻ ፍለጋን ‘የፖለቲካ ጥበብ’ አድርጎ በመውሰዱ፣ ከስህተቱ ለመማር ዕድል እንደሌለው ልብ ይሏል። በዚህ ላይ፣ የሚለኮሰው እሳት ዐይነቱም ተዋናዩም ብዙ ነው። በዋንኛነትም፣ የሜጫና ቱለማ (የሸዋ ኦሮሞ) ልሂቃን ቀዳሚ የቀውሱ መሃንዲስ ሆነው መታየታቸውን- እኛም ታሪክም መዝግበነዋል።

በጥቅሉ ግን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ፡- የአንዲት ቤተ-ክርስቲያን፣ የአንድ ሲኖዶስ፣ የአንድ ፓትርያሪክ ቀኖናዋ ዳግም ፈተና ውስጥ የገባባበት ችግር መነሾን በሁለት ክፍሎ ማየት ይገባል፡፡

የመጀመሪያው፣ ጠ/ር ዐቢይ አሕመድ፡- እንደ ዐፄ ኃይለሥላሴ፣ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያም እና መለስ ዜናዊ የራሱን ፓትርያርክ እንዲያመጣ ‹ሽቷል› አልያም ‹ሹክ ያለው ሴጣናዊ ምክር አለ› ተብሎ ከሾለከው መረጃ ጋ ይያያዛል፡፡

ሁለተኛው፣ የጋራ ቤት ከሆነችው ከቤተ-ኢትዮጵያ ይልቅ፣ ኦሮሙማ መደበቂያ ምሽጉ የሆነው ጠባብ የብሔሩ ልሂቃን ዐዲስ ሀገረ-መንግሥት የማዋለድ ድብቅ ዓላማን የተንተራሰ ከመሆኑ አኳያ የሚመዘዝ ነው፡፡ ይህን ለማስፈጸም ደግሞ፣ ፓትርያሪክ ጽ/ቤት ድረስ የተዘረጉ የልዩነት ክሮች መገመዳቸው በግላጭ ቀጥሏል፡፡

ቤተ-ክርስቲያን የሌላት አደረጃጀት በእጅ ጥምዘዛ እንዲፈጠር ጫና ሲያደረግ ቆይቷል፡፡ በኦሮምኛ ቋንቋ መንፈሳዊ አገልግሎት በመስጠት የሚቀድማት አንድም ሃይማኖት ባይኖርም፣ በመምሪያ ደረጃ ለብዝሃ-ታሪክ ከፍ ያለ ቦታ ሰጥታ ብትንቀሳቀስም፣ የበረታ መዋቅራዊ ጥቃት ተከፍቶባታል። በርግጥም ቤተክርስቲያን ስደት ላይ ነች!!

እንደመቋጪያ

በአንድ በኩል፣ የቤተ-ክርስቲያኗን ፍሬ-ነገር የመጨፍለቅ፤ በሌላ በኩል፣ አንዳንድ አባቶች ከመንፈሳዊ ግብር ጎድለው ሲገኙ ከክርስትና እሴት ባፈነገጠ የስድብ መንጋ የሚያዘንቡ የማኀበራዊ ሚዲያ ጦር ሠራዊት በማሰለፍ፣ ቤተ-ክርስቲያኗን በአማኞቿ አዕምሮ ውስጥ የማፍረሱ ዘመቻ በርትቶ የቆየ ቢሆንም፤ ዐዲስ አገር አላሚው ኃይል የመዘዘው የመጨረሻው ካርድ ቤተ-ክርስቲያን ልጆቿን እንድትጠራ ምክንያት ሆኗታል። ልጆቿም ከየአቅጣጫው “አቤት” እያሉ ነው፡፡

ይህንን መንፈሳዊ ጥሪ በቤተ-ክርስቲያኗ ፈተናዎች (በዋናነት ከውጭ ወደ ውስጥ በሚገቡት) ላይ የማያዳግም ምላሽ የሚሰጥ እንዲሆን ማድረጉ ደግሞ የአባቶች ኃላፊነት ነው። ከቅዱስ ሲኖዶስ መንፈሳዊ መመሪያ ውጭ የሚኬዱ የትኞቹም የትግል መንገዶች ለቤተ-ክርስቲያኗም ሆነ አዕማድ ለሆነቻት ኢትዮጵያ ፈፅሞ አይጠቅሙምና!!

ስለዚህም፣ ሃይማኖ-ቲከኞች እጃቸውን ከቤተ-ክርስቲያኗ እንዲያነሱ ሊቃውንት ይምከሩ፣ መንፈሳዊ ልጆችም ያድምጡ! እኛም በምልአት የቅዱስ ሲኖዶሱን ጥሪ ብቻ እንተግብር።

በግልፅ ዐማርኛ፣ እውነተኛውን የቤተ-ክርስቲያናችንን ጥያቄ፣ ‘የፖለቲካ ነጋዴዎች’ እንዳይጠልፉት በብርቱ እንጠንቀቅ!!

የሀገረ-መንግሥቱ ህላዌ የሚወሰነው ኢትዮጵያን ዓለማዊ (secular) በማድረግ እንጂ፤ ግራ-ቀኝ ተሰልፈው በየሃይማኖታዊ ተቋማት እጃቸውን በነከሩ ሃይማኖ-ቲከኞች አይደለም፤ (ይህኛው መልዕክት ሁሉንም ሃይማኖቶች ይመለከታል።)

በዚህ አጋጣሚ የአማራም ሆነ የሱማሌ፤ የአፋርም ሆነ የሲዳማ፤ … የየትኞቹም ክልላዊ መንግሥታት ጉዳዮን በጥንቃቄ እንዲይዙት፣ ይልቁንም የእናት ቤተክርስቲያን ጥያቄ በሰላማዊ አግባብ እንዲፈታ ህላዌዋ እንዲጠበቅ በሚያስችል አግባብ መንግሥታዊ አመራራችሁን ከማረጋገጥ ውጭ የአፈና መዋቅር ለመጠቀም መሞከር መታነቂያ ገመድን እንደማቀበል ይቆጠራል። ይህ ለጥቃትና ጭፍለቃ ወሰን፣ ዘር፣ ኃይማኖት፣… የማይለይ ዋጭና ሰልቃጭ ቡድን ዛሬ ካልተገታ ነገ በሌላ አጀንዳ በራችሁን ንዶ መዝለቁ ተገማች ነውና እብደቱ ዛሬ ሊገታ ይገባል!!

(በዚህ አጋጣሚ፣ የቤተ-ክርስቲያን ፈተና አሳስቧቸው አጋርነታቸውን ያሳዩ የሌሎች ሃይማኖት ተከታዮች ምስጋና ይገባችኋል!)

መንግሥት ሆይ፣ የረከሰ እጅህን ከቤተ-ክርስቲያኒቷ ላይ ታነሳ ዘንድ በጨዋ ቋንቋ ትጠየቃል!!!

እናት ቤተክርስቲያን ከፊቴ ቅደም ባለችኝ ቦታ ሁሉ ለመገኘት እኔ ልጇ ወልደሰማይት በቃሌ እቆማለሁ!!

#አንዲትቤተክርስቲያን

#አንድሲኖዶስ

#አንድፓትርያሪክ