May 3, 2023 – BBC Amharic 

ሞስኮ ውስጥ ተሞከረ የተባለውን የድሮን ጥቃት በተመለከተ ከቪዲዮ ላይ የተወሰደ ምስል
የምስሉ መግለጫ,ሞስኮ ውስጥ ተሞከረ የተባለውን የድሮን ጥቃት በተመለከተ ከቪዲዮ ላይ የተወሰደ ምስል

3 ግንቦት 2023, 16:28 EAT

ዩክሬን በፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን መኖሪያ ቤተ መንግሥት ላይ ጥቃት በመሰንዘር ልትገድላቸው ሞክራለች ስትል ሩሲያ ከሰሰች።

ማክሰኞ ምሽት የፕሬዝዳንት ፑቲን ቤተመንግሥትን ኢላማ ያደረጉ ሁለት ድሮኖችን ጥያለሁ ያለችው ሩሲያ፣ ዩክሬን ፑቲንን ለመግደል እየሞከረች ነው ስትል ከሳለች።

የክሬምሊን ቤተመንግሥት ባለሥልጣናት እንዳሉት ለጥቃት የተሰማሩት ድሮኖችን የፕሬዝዳንቱ ጥበቃ ኃይል በኤሌክትሮኒክ ራዳር ከጥቅም ውጪ አድርገዋቸዋል።

የፕሬዝዳንቱ ቃል አቀባይ ዲሜትሪ ፔስኮቭ ለአገሪቱ መንግሥት የዜና ወኪል እንደተናገሩት፣ ፑቲን በወቅቱ ክሬምሊን ውስጥ አልነበሩም፤ እንዲሁም በቤተመንግሥቱ ሕንጻዎች ላይ ምንም አይነት የደረሰ ጉዳት የለም ብለዋል።

ዩክሬን የቀረበባትን ክስ በተመለከተ ምንም አይነት አስተያየት ለመስጠት እንደማትፈልግ ገልጻለች።

ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን
የምስሉ መግለጫ,ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን

በሩሲያ ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተሰራጩ እና እውነተኛነታቸው ያልተረጋገጡ ቪዲዮዎች ዛሬ ረቡዕ ጠዋት ላይ ከማዕከላዊ የሞስኮ ክፍል የሚነሳ ጭስ አሳይተዋል።

ከክሬምሊን በተሰጠ መግለጫ ላይ “ባለፈው ምሽት የዩክሬን መንግሥት ሰው አልባ አውሮፕላኖችን በመጠቀም ክሬምሊን ውስጥ በሚገኘው የሩሲያ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት መኖሪያ ቤት ላይ ጥቃት ለመሰንዘር ሞክሯል።”

ጨምሮም “ፕሬዝዳንቱን ለመግደል የታቀደ የሽብር ተግባር በመሆኑ፣ ሩሲያ አስፈላጊ በሆነ በየትኛው ቦታ እና ጊዜ የአጸፋ እርምጃ የመውሰድ መብት አላት” ብሏል።

ከጥቅም ውጪ እንዲሆኑ ተደርገዋል የተባሉት ድሮኖች ስብርባሪ በክሬምሊን ቤተመንግሥት ግቢ ውስጥ የወደቁ ሲሆን፣ ምንም ጉዳት እንዳላደረሱ ተገልጿል።

መግለጫው በፕሬዝዳንት ፑቲን ላይ ምንም አይነት ጉዳት አለመድረሱን እና ያሏቸው መረሃ ግብሮች በሙሉ በተያዘላቸው ቅደም ተከተል መሠረት በተለመደው ሁኔታ ይካሄዳሉ ብሏል።

ይህ ጥቃት የተፈጸመው የውጭ አገራት እንግዶች የሚታደሙበት እና ከቀናት በኋላ ከሚከበረው ከሩሲያ የድል ቀን በዓል ቀደም ብሎ መሆኑን የፕሬዝዳንቱ ጽህፈት ቤት ጠቅሷል።

በሩሲያ የቀረበውን ክስ በተመለከተ ቢቢሲ የዩክሬን ፕሬዝዳንት ጽህፈት ቤትን አስተያየት የጠየቀ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት በጉዳዩ ላይ አስተያየት መስጠት እንደማይፈልጉ ገልጸዋል።