May 12, 2023 – Konjit Sitotaw 

አንጋፋዋ ድምጻዊት ሂሩት በቀለ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየች

በኢትዮጵያ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ ውስጥ የራሷን አሻራ ያስቀመጠችው አንጋፋዋ ድምጿዊት ሂሩት በቀለ ከዚህ ዓለም በሞት መለየቷ ተሰምቷል።

ድምጻዊት ሂሩት ከ1950 መጀመሪያ እስከ 1980ዎቹ መጨረሻ ድረስ፤ ሕይወት እንደሸክላን ጨምሮ በርካታ ድንቅ የሙዚቃ ሥራዎችን ለአድናቂዎቿ ያበረከተች ሲሆን፤ ባደረባት ሕመም ምክንያት በአገር ውስጥና በውጭ በሕክምና ስትረዳ ቆይታ በ80 ዓመቷ ካሳንችስ አካባቢ በሚገኘው መኖሪያ ቤቷ ዛሬ ግንቦት 04/2015 ከዚህ ዓለም በሞት መለየቷ ታውቋል፡፡

ሂሩት በቀለ ከክቡር ዘበኛ የሙዚቃ ክፍል ጀምሮ በብዙ መድረኮች ላይ ከመጫወት ባለፈ፤ የራሷን የሙዚቃ ካሴቶች በማሳተም ሥራዎቿን ለህዝብ ያደረሰች ሲሆን፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዘማሪነት ሥራዎችን ስትስራ እንደነበር ይታወሳል፡፡

ሂሩት በቀለ የ7 ልጆች እናት፣ የ10 ልጆች አያት እና የ7 ልጆች ቅድመ አያት ነበረች።