
የፌደራል መንግስት “ደመወዝ የመክፈል ጫና ውስጥ ለገቡ” ክልሎች፤ ከሰባት ቢሊዮን ብር በላይ ማበደሩን የገንዘብ ሚኒስትሩ ተናገሩ
የክልል መንግስታት ላጋጠማቸው የበጀት እጥረት፤ የፌደራል መንግስት ብድር መስጠት እንጂ ቀጥታ ድጋፍ ማድረግ እንደማይችል የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ ተናገሩ። የፌደራል መንግስት “ደመወዝ የመክፈል ጫና ውስጥ ለገቡ” ክልሎች፤ ከሰባት ቢሊዮን ብር በላይ ማበደሩንም ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
የገንዘብ ሚኒስትሩ ይህን የተናገሩት፤ ትላንት ረቡዕ ግንቦት 9፤ 2015 ከተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀት እና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ማብራሪያ ላይ ነው። የሚመሩት የሚኒስቴር መስሪያ ቤትን የዘጠኝ ወራት የስራ አፈጻጸም ሪፖርት ለማቅረብ በፓርላማ ለተገኙት አቶ አህመድ ከቀረቡ ጥያቄዎች መካከል፤ ክልሎች የገጠማቸውን የበጀት እጥረት የተመለከተው አንዱ ነበር።
ለዚህ ጥያቄ ምላሽ የሰጡት ሚኒስትሩ አቶ አህመድ፤ “ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አንዳንድ ክልሎች ደመወዝ የመክፈል ጫና” ውስጥ መግባታቸውን አረጋግጠዋል። ይህ ችግር በተለይም በአዲስ ክልሎች ውስጥ የሚታይ ቢሆንም “አንዳንድ ነባር ክልሎችም ጭምር” ተመሳሳይ ሁኔታ ውስጥ መሆናቸውን አንስተዋል። ሚኒስትሩ “ደመወዝ የመክፈል ጫና ውስጥ ገብተዋል” በሚል የጠቀሷቸው፤ ደቡብ፣ ሲዳማ እና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልሎችን ነው። የሶማሌ እና አፋር ክልሎችም ተመሳሳይ ችግር እንዳጋጠማቸው በገንዘብ ሚኒስቴር የትሬዠሪ ዳይሬክተር የሆኑት ወ/ሮ ነጠሩ ወንድወሰን ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል።
