May 31, 2023 – EthiopianReporter.com — Comments ↓

መንግሥት የግብርና ዘርፎች ላይ ታክስ ለመጀመር ዕቅድ እንዳለው ተገለጸ
May 31, 2023

በአብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ የተሰማራበትና ትልቁን የአገሪቱን ኢኮኖሚ ድርሻ የሚይዘው የግብርና ዘርፍ ላይ ግብር ለመጀመር ዕቅድ እንዳለ የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ ተናገሩ፡፡
ሚኒስትሩ እንደተናገሩት ‹‹በአገሪቱ በጣም ብዙ የግብርና ምርትና ልውውጥ ይካሄዳል፣ ነገር ግን የግብርና ታክስ አይደረግም፣ ለአገራዊ ምርቱ ትልቅ አስተዋጽኦ ኖሮት እያለ ሌሎች አገሮች እንደሚያደርጉት ሁሉ ግብር እየተከፈለ አይደለም፤›› ብለዋል፡፡
በመሆኑም የግብርና ዘርፎች ታክስ እንዴት መደረግ አለበት? የሚለውን በቀጣይ ጥናት ተደርጎበት በጥናቱ ውጤት መሠረት መንግሥት በሚያስቀምጠው አቅጣጫ ወደ ሥራ ይገባበታል ብለዋል፡፡
በገንዘብ ሚኒስቴር የታክስ ፖሊሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሙላይ ወልዱ ለሪፖርተር ስለጉዳዩ ሲያብራሩ፣ አሁን ላይ ወደ ሥራ የተገባ ባይሆንም በተወሰኑ ክልሎች በሥራ ላይ ያለውንና በግብርናው ዘርፍ የሚከፈል ክፍያ ሁሉንም ክልሎች ተቀራራቢ በሆነ መልኩ እንዲያስከፈሉ የሚያደርግ ሕግ ሊዘጋጅ እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
በመሆኑም ክልሎች የአካባቢያቸውን ሁኔታ ግምት ውስጥ በማስገባት የክፍያ ምጣኔ ለመጣል የሚያስችል ወጥ የሆነ ሞዴል ሊሆን እንደሚችል የገለጹት አቶ ሙላይ ውጤቱ ግን በሚደረገው ጥናት ይወሰናል ብለዋል፡፡
አሁን ላይ ክልሎች እያስከፈሉ ያሉት የግብርና ክፍያ፣ አርሶ አደሮች በየዓመቱ ለመጠቀሚያ ወይም አርብቶ አደሩ የሚያረባውን የእንስሳት መጠን መሠረት አድርጎ መሆኑን የገለጹት አቶ ሙላይ፣ በቀጣይ ጊዜያት ጥናት ተደርጎበት የሁሉም ክልሎች ክፍያ ባይመሳሰል እንኳ ተመጣጣኝና ተቀራራቢ ክፍያ እንዲከፍሉ ካልተደረገ አርሶ አደሮችም ይሁን አርብቶ አደሮች በክፍያው ምክንያት ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ሊፈልሱ ይችላሉ ብለዋል፡፡