May 31, 2023 – EthiopianReporter.com

ማኅበራዊ ዜጎችን ለውጭ ገበያ ዝግጁ የሚያደርጉ 77 የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች መለየታቸው ተነገረ
ዜጎችን ለውጭ ገበያ ዝግጁ የሚያደርጉ 77 የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች መለየታቸው ተነገረ
ቀን:
May 31, 2023
Share
በአበበ ፍቅር
ለውጭ ገበያ ዝግጁ የሚያደርጉ 77 የቴክኒክና ሙያ ማሠልጠኛ ኮሌጆች ተለይተው ሥልጠና በመስጠት ላይ መሆናቸው ተገለጸ፡፡
በየትኛውም የሥራ ዓይነት የሚሰማሩ ዜጎች ክህሎት መር የሥራ ሥምሪት እንዲያገኙ በማሰብ፣ የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ተለይተው በዓለም የገበያ ፍላጎት ላይ የተመሠረተ ሥልጠና ይሰጣሉ ነው የተባለው፡፡ የ21ኛው ክፍለ ዘመን ክህሎቶች የሚባሉትን ጭምር ያካተተ ብቃት ያለው ሥልጠና ሰጥቶ ለአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን፣ በአፍሪካና ከአፍሪካ ውጪ ያለውን ገበያ ለመጠቀም በበቂ ሁኔታ ሰው ማዘጋጀት አስፈላጊ በመሆኑ፣ ትኩረት ሰጥተው እየሠሩ መሆናቸውን፣ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ደኤታ አቶ ንጉሡ ጥላሁን ገልጸዋል፡፡
በየዓመቱ የሚካሄደውን ብሔራዊ የሥራ ጉባዔ በሐምሌ ወር 2015 ዓ.ም. በአፍሪካ ደረጃ ለማካሄድ ዝግጅት መደረጉን፣ ግንቦት 21 ቀን 2015 ዓ.ም. በተካሄደ ስብሰባ ላይ ተነግሯል፡፡
ጉባዔው በአፍሪካ ደረጃ መዘጋጀቱ በአኅጉሪቱ የሥራ ዕድልን በመፍጠር በኩል አስቸጋሪ የሆኑ ጉዳዮችን ለይቶ በጋራ ለመሥራት ጠቃሚ መሆኑን አቶ ንጉሡ አስረድተዋል፡፡
በተለይ በአኅጉሪቱ በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በኮንስትራክሽንና በሌሎች ዘርፎች የሥራ ዕድሎች እንዲጨምሩ አጋጣሚ ይፈጥራል ብለዋል፡፡
‹‹የሥራ ጉባዔውን ስናዘጋጅ የምንማርባቸውና የምናስተምራቸው ነገሮች ይኖራሉ፡፡ በዚህም ኢትዮጵያ ተጠቃሚ ትሆናለች ተብሎ ይጠበቃል፤›› ብለዋል፡፡
ሁሉም የአፍሪካ አገሮች ለሥራ ዕድል ፈጠራው ያላቸው ተነሳሽነት እያደገ ነው ያሉት ደግሞ፣ የአፍሪካ ኤሌክትሮኒክ ትሬድ ግሩፕ መሥራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሙሉዓለም ሥዩም ናቸው፡፡
ጉባዔው ላይ ሚኒስትሮች የድርጅት መሪዎች፣ ወጣት ኢንተርፕሩነሮችና ኢኖቬተሮች የሚያሳትፍ መሆኑንና በአጠቃላይ ከአንድ ሺሕ በላይ ተሳታፊዎች ይኖራሉ ብለዋል፡፡
ጉባዔውን ለየት የሚያደርገው የአፍሪካ ጋዜጠኞች በጉባዔው ላይ ተገኝተው በየቋንቋቸው የቀጥታ ሥርጭት እንዲያደርጉ ክፍት መሆኑ ነው ብለዋል፡፡ በዚህም ለ200 ሚሊዮን ሰዎች ተደራሽ እንደሚሆን ይጠበቃል ሲሉ አክለዋል፡፡
‹‹ኢንተርፕሩነሮችና ኢኖቬተሮች ከዚህ በፊት በአፍሪካ ኅብረት ምን እየሠተራ እንደሆነ አያውቁም ነበር፡፡ በቀጣይ ሐምሌ ወር የሚካሄደው ትልቅ መድረክ ለወጣቱ ጥሩ የግንዛቤ መፍጠሪያ ይሆናል፤›› ሲሉ አቶ ሙሉዓለም ተናግረዋል፡፡
‹‹እንደ አፍሪካ ካሉብን የጋራ ችግሮች ዋነኛው የሥራ አጥነት ችግር ነው፡፡ ነገር ግን የተለያዩ ፀጋዎች አሉን፡፡ ፀጋዎች እነዚህን በመጠቀም፣ በተለይ ደግሞ ለኢንተርፕራይዞች የገንዘብ አቅርቦት የሚመቻችበት የገበያ አማራጭና የቴክኖሎጂ ደረጃዎችን እንዲሻሻል አስተዋጽኦ በሚያደርጉ የጋራ ጉዳዮች ላይ በጋራ የምንሠራበት መድረክ ይሆናል፤›› ሲሉም አቶ ንጉሡ አስረድተዋል፡፡
ጉባዔው የሚካሄደው ከአፍሪካ ኅብረትና የአፍሪካ ኤሌክትሮኒክስ ንግድ በዳያስፖራ ማኅበረሰብ አነሳሽነት ሥራ ከጀመረ፣ በኢትዮጵያም መቀመጫውን ለማግኘት ከመንግሥት ጋር አብሮ የሠራ ድርጅት ጋር በመተባበር ነው ሲሉ ሚኒስትር ደኤታው አብራርተዋል፡፡
ኢትዮጵያም በአኅጉር ደረጃ ለመጀመሪያ ጊዜ በአዘጋጅነት ስትሳተፍ በርካታ ጥቅሞችን እንደምታገኝ፣ በተጨማሪም የአገር ውስጥ ኢንተርፕሩነሮች ከአፍሪካ ኢንተርፕሩነሮች ጋር ትውውቅ የሚያደርጉበት፣ እንዲሁም በሒደት ምርቶቻቸው በመላው ዓለም እንዲተዋወቁ ዕድል የሚያገኙበት ነው ብለዋል፡፡